የአዲስ አበባ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን በመንገድ ሥራ ፕሮጀክት ምክንያት በፍሳሽ ማስወገጃ ቱቦ ላይ ጉዳት እንደደረሰ፣ ለከተማዋ መንገዶች ባለሥልጣን ቢያሳውቅም ምላሽ እንዳላገኘ አስታወቀ።
መነሻውን ከአባዶ አድርጎ ወደ ጣፎ፣ ሰሚት የጋራ መኖሪያ ቤትና አካባቢው በሙሉ፣ እንዲሁም ቦሌ አያት ኮንደምኒየም በከፊል፣ ፈረስ ቤትና ሌሎች ማኅበረሰቦች የሚለቁትን ፍሳሽ ሰብስቦ መድረሻውን ኮተቤ ማጣሪያ ጣቢያ የሚገባ ባለ ስድስት መቶ ሚሊ ሜትር የፋሳሽ ማስተላለፍያ መስመር ላይ ጉዳት መድረሱን፣ በአዲስ አበባ ውኃና ፍሳሽ ባለሥልጣን የከፍተኛ ፍሳሽ መስመር የሥራ ሒደት መሪ አቶ አቦነህ ባዩ ተናግረዋል።
ጉዳቱ በፍሳሽ ማሳለፊያ ጉድጓድ ላይም የደረሰ በመሆኑ፣ ከመስመር ውጪ ያሉ ማኅበረሰቦች ጨምሮ በግብርና ሥራ የሚተዳደሩ ቤተሰቦች ላይ ጉዳት ደርሷል ብለዋል።
ባለሥልጣኑ ኮንትራክተሮች ከተከሰተው የመሥሪያ መስመር ውጪ እየሠሩ እንደሆነና በፍሳሽ ማስወገጃው ላይ ጉዳት ሊያደርስ እንደሚችል ቢገለጽለትም፣ ማሳሰቢያውን ባለመቀበሉ የካቲት 29 ቀን 2014 ዓ.ም. አመሻሽ ላይ በቦሌ በሻሌ ኮንደሚኒየም ቱቦ መፈንዳቱን ገልጸዋል።
ይህንን ተከትሎም የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ማስተካከያ እንዲያደርግ በደብዳቤ ቢጠየቅም ምላሽ አለመስጠቱን አቶ አቦነህ ገልጸዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን በሚያሠራው መንገድ ምክንያት በተደጋጋሚ በውኃና በፍሳሽ መሠረተ ልማት ላይ እያደረሰ ያለው ጉዳት ሕዝቡ ላይ ጭምር ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ መሆኑን በመረዳት፣ የሚያሠራቸውን ተቋራጮች ተገቢውን ክትትል ማድረግ አለበት ሲሉም አሳስበዋል።
በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡ ከሪፖርተር ጥያቄ የቀረበላቸው የአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን የመንገድ ዲዛይን ዳይሬክተር ሜቲ ውድነህ (ኢንጂነር) ጥያቄው እንደደረሳቸው ገልጸው፣ በፕሮጀክቱ ላይ የተፈጠረ ስህተት መኖሩን ለማጣራት በሚቀጥለው ሳምንት ከባለሥልጣኑ ጋር እንደሚነጋገሩ ገልጸዋል።