- 28 ተከሰሾች ከ15 ዓመታት በላይ ፅኑ እስራት ተወስኖባቸዋል
የአማራ ክልል ፕሬዚዳንት የነበሩት አምባቸው መኮንን (ዶ/ር)፣ የፕሬዚዳንቱ አማካሪ የነበሩት አቶ እዘዝ ዋሴና የክልሉ ጠቅላይ ዓቃቤ ሕግ የነበሩት አቶ ምግባሩ ከበደን በመግደል ወንጀል ክስ ተመሥርቶባቸው ከነበሩት 31 ግለሰቦች ውስጥ ሦስቱ በዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት እንዲቀጡ፣ የአማራ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት 23ኛ ወንጀል ችሎት የካቲት 29 ቀን 2014 ዓ.ም. ውሳኔ ሰጠ፡፡ በክሱ ተካተው የነበሩ 28 ተከሳሾችም እያንዳንዳቸው በ15 ዓመታት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ውሳኔ አሳልፏል፡፡
ፍርድ ቤቱ በሌሉበት በዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት እንዲቀጡና በቀረበባቸው የሰውና የሰነድ ማስረጃ ጥፋተኛ የተባሉ ተከሳሾች ሻምበል አቶ በላይሰው ሰፊነውና አቶ ልቅናው ይሁኔ ሲሆኑ፣ እያንዳንዳቸው በዕድሜ ልክ ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ፍርድ ቤቱ ወስኖባቸዋል።
በባለሥልጣናቱ ግድያ ጥፋተኛ በተባሉና በእነ ሻምበል መማር ጌትነት የክስ መዝገብ የተካተቱት 28 ተከሳሾች፣ በ15 ዓመታት ፅኑ እስራት እንዲቀጡ ወስኗል፡፡
በአማራ ክልል ከፍተኛ ባለሥልጣናት ላይ ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. ግድያ በመፈጸም ተጠርጥረው ክስ ተመሥርቶባቸው የፍርድ ሒደታቸውን ሲከታተሉ ከቆዩ 55 ተከሳሾች መካከል፣ ቀደም ሲል 20 ግለሰቦች መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ እንዲሰናበቱ ተደርጓል። እንዲከላከሉ ከተባሉት መካከል ደግሞ አራቱ በነፃ እንዲሰናበቱ ፍርድ ቤቱ መወሰኑ ይታወሳል።
የክልሉ ዓቃቤ ሕግ ተከሳሾቹ በኅብረትና በማደም ሕገ መንግሥትና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል በመናድ፣ ከሕግ ውሊ ሥልጣን ለመያዝ በተደረገ ሙከራ ክስ መመሥረቱ አይዘነጋም፡፡
ሰኔ 15 ቀን 2011 ዓ.ም. በተቀራራቢ ሰዓታት በአዲስ አበባ ከተማም ምሽት ላይ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታ ማዦር ሹም ጄኔራል ሰዓረ መኮንንና ጓደኛቸው ሜጀር ጄኔራል ገዛዒ አበራም መገደላቸው ይታወሳል፡፡