በአምስት ወራት መንግሥት በቀረጥ ነፃ ሳቢያ 18 ቢሊዮን ብር ማጣቱ ተገልጿል
ከቀረጥ ነፃ የሚገቡ ምርቶችን የሚያመጡ ነጋዴዎችን ለመቆጣጠር ያስችላል የተባለ አዲስ መመርያ ማዘጋጀቱን፣ የንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር አስታወቀ።
በኢትዮጵያ እየታየ ባለው ከፍተኛ የዋጋ ንረት ሳቢያ እንደ ስኳር፣ የምግብ ዘይት፣ ስንዴ፣ ፓስታና ማካሮኒ የመሳሰሉ መሠረታዊ ምርቶች ከቀረጥ ነፃ እንዲገቡ በነሐሴ ወር 2013 ዓ.ም. መፈቀዱ ይታወሳል።
ነገር ግን ነጋዴዎች የተሰጠውን ዕድል በሕገወጥ መንገድ እየተጠቀሙበት በመሆኑ አዲስ መመርያ ማዘጋጀት ማስፈለጉን፣ በንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር የንግድ ዕቃዎች ዋጋ ጥናት ክትትልና ቁጥጥር ዳይሬክተር ወ/ሮ መስከረም ባህሩ ለሪፖርተር ተናግረዋል።
‹‹ከቀረጥ ነፃ እንዲገቡ የተፈቀዱ የፍጆታ ምርቶች ታሪፍ የማይከፈልባቸው በመሆናቸው ኅብረተሰቡም በቅናሽ ዋጋ እንዲገዛ ለማድረግና የተከሰተውን የዋጋ ንረት ለመቀነስ ቢሆንም፣ አስመጪዎች ግን በከፍተኛ ዋጋ እየሸጡ መሆናቸውን ሚኒስቴሩ ማወቅ ችሏል፤›› ብለዋል።
ከቀረጥ ነፃ ዕድልን የሚጠቀሙ አስመጪዎች በተጠበቀው መሠረት እየሠሩ አይደለም ያሉት ወ/ሮ መስከረም፣ ምርቶቹን ያለ ደረሰኝና በከፍተኛ ዋጋ እየሸጡ እንደሆነ ገልጸዋል። ይህንን መሠረት በማድረግም አስመጪዎችን የሚቆጣጠር መመርያ መዘጋጀቱን አስረድተዋል።
አዲሱ መመርያ አስመጪዎች ያስመጡትን የምርት መጠን፣ ዓይነትና ያስመጡበትን ጊዜ ጉምሩክ ኮሚሽን መዝግቦ ለንግድና ቀጣናዊ ትስስር ሚኒስቴር፣ እንዲሁም ለክልል ንግድ ቢሮዎች የሚያስተላልፍበትን አሠራር የያዘ ነው።
ጉምሩክ ኮሚሽን በሚሰጠው መረጃ መሠረትም የክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ንግድ ቢሮዎች ምርቱ ለማን እንደተከፋፈለ፣ በምን ያህል ዋጋ እንደተሸጠና በሕጋዊ መንገድ መሸጡን ያረጋግጣሉ ይላል፡፡
እንደ ወ/ሮ መስከረም ገለጻ ከሁለት ሳምንት በኋላ ተግባራዊ እንደሚደረግ የሚጠበቀው አዲሱ መመርያ፣ አስመጪዎቹ ከቀረጥ ነፃ የገቡ ምርቶችን ለኅብረት ሥራ ማኅበራትና ለሸማቾች ማኅበራት ቅድሚያ ሰጥተው እንዲያቀርቡ ያዛል።
ከቀረጥ ነፃ ዕድሉን ተጠቅመው የፍጆታ ምርቶችን የሚያቀርቡ ነጋዴዎች 300 የደረሱ ሲሆን 80 በመቶ የሚሆኑት ምርቶቹን ከአዲስ አበባ ውጪ የሚያቀርቡ ናቸው። በዚህም መሠረት በአዲስ አበባ የሚጠበቀውን ያህል አስመጪ እየተሳተፈ አይደለም ያሉት ዳይሬክተሯ፣ ዕድሉን በመጠቀም ነጋዴዎች ምርቶቹን በማስመጣት ለአዲስ አበባ ከተማ ገበያ እንዲያቀርቡ ሚኒስቴሩ ጥሪ ያቀርባል ብለዋል።
የፍጆታ ዕቃዎች ከቀረጥ ነፃ እንዲገቡ ከተፈቀደበት ነሐሴ 2013 ዓ.ም. ጀምሮ ባሉት አምስት ወራት ውስጥ፣ መንግሥት ከቀረጥ ያገኘው ከነበረው ገቢ ውስጥ 18 ቢሊዮን ብር ማጣቱን አስረድተዋል።