ሁሉን አቀፍ አገራዊ የምክክር ውጥን (ማይንድ-ኢትዮጵያ) በጥቅምት ወር 2014 ዓ.ም. የውይይቶች ማስጀመርያ መርሐ ግብር እንደሚያደርግ ተገለጸ፡፡
በነሐሴ ወር 2012 ዓ.ም. በስምንት መንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ ተቋማትና የሙያ ማኅበራት ተዋጽኦ የተመሠረተው ይኼ ውጥን ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ ከተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍል ተወካዮች ጋር ውይይቶችን ሲያደርግና የውይይት አጀንዳዎችን ሲለይ የቆየ ሲሆን፣ በጥቅምት ወር 2014 ዓ.ም. ብሔራዊ ውይይት ማስጀመሪያ መርሐ ግብር እንደሚደረግ አስታውቋል፡፡
ማይንድ-ኢትዮጵያ ይኼንን ያስታወቀው ጳጉሜን 4 ቀን 2013 ዓ.ም. በስካይላይት ሆቴል ከተለያዩ ባለድርሻ አካላት ጋር በውጥኑ ዓላማ፣ አካሄድ፣ አሳታፊነት፣ አጀንዳና መሰል ጉዳዮች ላይ ውይይት ባደረገበት መድረክ ነው፡፡
እስካሁንም በዝግጅት ምዕራፍ በተደረጉ ውይይቶች ከ44 ሚሊዮን ዜጎች በላይ እንዲሳተፉ መደረጉንና ከእነሱም የተለያዩ የውይይት አጀንዳዎች እንደተሰበሰቡ፣ የማይንድ-ኢትዮጵያ አባል አቶ ንጉሡ አክሊሉ የተናገሩ ሲሆን፣ ይኼም የውጥኑ አንዱ ስኬት እንደሆነም አውስተዋል፡፡
ለብሔራዊ ውይይቱ ዓለም አቀፍ ድጋፍ የሚሰጥ የወዳጅ አገሮችና ድርጅቶች አምባሳደሮች ስብስብ ተመሥርቷል፡፡ ስብስቡም አየርላንድ፣ ዴንማርክ፣ ኔዘርላንድስ፣ ዩኤስኤአይዲ፣ ጀርመን፣ ስዊዲንና ስዊዘርላንድ የተካተቱበት ነው ተብሏል፡፡
የተሰበሰቡ አጀንዳዎች በርካታ እንደሆኑ የተናገሩት አቶ ንጉሡ፣ ከእነዚህ መካከልም የሕገ መንግሥት ጉዳዮች፣ የአስተዳደር ጉዳዮች፣ የዴሞክራሲ ተቋማት ጉዳዮች፣ የአገርና አገረ መንግሥት ግንባታ ብሎም ታሪክ ጠቀስ ጉዳዮች እንደተያዙም አስረድተዋል፡፡
ይሁንና እስካሁን ባለው ሒደት የግጭቶችና የአመፅ መኖር፣ ደረቅ የፖለቲካ ባህል መኖር፣ ውስብስብና ተለዋዋጭ የፖለቲካ ሁኔታ፣ እንዲሁም ብሔራዊ ዕርቅን በተመለከተ ተለያዩ አካላት የሚስተጋቡ ወጥ ያልሆኑና ግራ አጋቢ መልዕክቶች ፈተና ነበሩ ተብሏል፡፡