በበርካታ ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድሮች የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን ወክለው እንዲሁም በግል ውድድሮች ላይ ውጤታማ መሆን የቻሉ አትሌቶችን ማፍራት በቻለው በጉራጌ ዞን ዓመታዊ የጎዳና ውድድር ሊከናወን መሆኑ ተገለጸ፡፡
ከኬር ኦድ የልማትና ባህል ማኅበር ጋር በመተባበር በዞኑ ዋና ከተማ ወልቂጤ ግንቦት 8 ቀን 2013 ዓ.ም. የሚካሄደው የ15 ኪሎ ሜትር የጎዳና ሩጫ መሆኑን አዘጋጁ አስታውቋል፡፡
መጋቢት 22 ቀን 2013 ዓ.ም. ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጠው አዘጋጁ አካል፣ በአዲስ አበባና በደቡብ ክልል የሚገኙ ከሃያ በላይ ክለቦች የታቀፉ ከ300 በላይ አትሌቶችና ከአሥር ሺሕ በላይ ስዎች የሚሳተፉበት ውድድር መሪ ቃል ‹‹ሰላም እና አንድነት ለኢትዮጵያ ሕዝብ›› የሚል ነው።
ውድድሩም በርካቶች የሚሳተፉበት በመሆኑ፣ የኮቪድ-19 ወረርሽኝን ለመከላከል በጤና ሚኒስቴር የወጡትን መመርያዎች ሕግጋት በመተግበር የሚከናወን መሆኑን አዘጋጆቹ ገልጸዋል፡፡
ከኬሮድ የስፖርት ልማት ማኅበር ጋር በጋራ እየተንቀሳቀሱ የሚገኙትና በዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ውድድሮች ላይ ባለድል የሆኑት ሰለሞን ባረጋ፣ አንዱአምላክ በልሁ፣ ሙክታር እድሪስና ሌሎች አትሌቶች ውድድሩ መዘጋጀቱ ከዞኑ ተተኪ አትሌቶች ለማግኘትና ተስፋ የሚጣልባቸውንም አቅማቸውን ለማሳያ ዕድል እንደሚሰጥ አስረድተዋል፡፡
ውድድሩን ያዘጋጀው ኬሮድ ስፖርት በቀጣይ ዕቅዱ ውድድሮችን በዞኑ የተለያዩ ከተሞች በማዘጋጀት ለአትሌቶች ተደራሽነቱን እንደሚያሰፋና አዲስ አበባ ላይም ተመሳሳይ ውድድሮች የማዘጋጀት ዕቅድ እንዳለው አስታውቋል፡፡
በቅርብ ጊዜም በቡታጅራ የሴቶች የአምስት ኪሎ ሜትር የሩጫ ውድድር ለማዘጋጀት እንቅስቃሴዎችን መጀመሩ የዕቅዱ አንድ አካል ማሳያ ይሆናል ተብሏል፡፡
አካባቢው በዓለም አቀፍ ደረጃ በ1,500 ሜትር ክብረ ወስን መስበር የቻለው ሰለሞን ባረጋ፣ በዓለም ሻምፒዮናና በኦሊምፒክ ጨዋታ ላይ መሳተፍ የቻለው ሙክታር እድሪስና በተለያዩ ዓለም አቀፍ የጎዳና ውድድሮች ላይ ድል መጎናፀፍ የቻለውን አንዱአምላክ በልሁን ማፍራቱ ይታወሳል፡፡
የውድድሩ አባል የሆኑት እነዚህ አትሌቶች ዞኑ አቅም ያላቸው በርካታ ተተኪ አትሌቶች ለማፍራት ለሚያደርገው ጥረት እንደሚደግፉ ገልጸው፣ ተመሳሳይ ውድድሮችን በማሰናዳት፣ የውድድር ዕድሎችን ለመፍጠር እንደሚሠሩ በጋዜጣዊ መግለጫው አስታውቀዋል፡፡
በኬሮድ ስፖርት ማኅበር ፕሬዚዳንት ተሰማ አብሺሮ አገላለጽ ከሆነ ማኅበሩ ከየትኛውም ማኅበር ጋር በጋራ በመሆን ስፖርቱን ለማሳደግ ይሠራል፡፡