ጊዜው እንዲህ እንደ ዛሬው የተለያዩ አገሮች ውድድር በማዘጋጀት የተንበሻበሹበት ጊዜ አልነበረም፡፡ አገርን ወክሎና ባንዲራ አንግቦ በውጭ አገር መወዳደር ትልቅ ኩራትና ክብር አለው፡፡ በባዶ እግር ሮጦ ለመላው አፍሪካዊ ኩራት የሆነውን የአበበ ቢቂላ ፈር ቀዳጅነት ተከትለው በዓለም አቀፍ ውድድሮች መሳተፍ ብቻ ሳይሆን ድል አድርጎ መመለስ እንደ ባህል ተወስዶ በርካታ ኢትዮጵያውያን በዛው ጎዳና ተጉዘው ስኬታማ ሆነዋል፡፡
እ.ኤ.አ. 1989 በሁለተኛው የዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ላይ በአትሌቲክስ ከተሳተፉት 373 አትሌቶች ወስጥ ኢትዮጵያ በዚህ ውድድር ላይ በ200 ሜትር ርቀት በዓለማየሁ ጉደታ ተወክላ ነበር፡፡ በሀንጋሪው ቡዳፔስት የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ዓለማየሁ በ400 ሜትርም ተሳትፎ ነበር፡፡
ዓለማየሁ በ400 ሜትር ውድድር 46.96 ሲገባ፣ የ200 ሜትር ርቀቱ ደግሞ 21.90 በመግባት እስከ ዛሬ ድረስም ከብረ ወሰኑን ማስጠበቅ ችሏል፡፡ በዚህ ርቀት ተወዳድሮ ክብረ ወሰኑን ማስጠበቅ የቻለ አትሌት አይደለም፣ በርቀቱ የሚሳተፍ አትሌት አልተገኘም፡፡ ከሦስት አሠርታት በላይ መሻገር የቻለው የኢትዮጵያውያን የረዥም ርቀት ውጤት ባሻገር በአጭር ርቀቱ እንደ ገድል የሚነገር አለመኖሩ እሙን ነው፡፡
እ.ኤ.አ. 2009 ላይ በአፍሪካ ወጣቶች ሻምፒዮና ላይ ብቅ ያለውና ከዚያም በግል ውድድሮች እየደመቀ የመጣውን የ800 ሜትር ተወዳዳሪ መሐመድ አማንን ማስታወስ ይቻላል፡፡ መሐመድ በመካከለኛ ርቀቱ የ2012 ዓለም የቤት ውስጥ ሻምፒዮናን ጨምሮ በ2013 ሞስኮ እንዲሁም በ2014 በፖላንድ ላይ ያስመዘገባቸው ውጤቶችን መጥቀስ ይቻላል፡፡
ኢትዮጵያ በተለይ በ5,000 ሜትር፣ 10,000 ሜትር፣ በግማሽ ማራቶንና እንዲሁም በማራቶን በታሪክ ሲዘከሩ የሚኖሩ አትሌቶች ቢኖሯትም በአጭር ርቀቱ ግን እምብዛም አልታደለችም ማለት ይቻላል፡፡
በአንፃሩ ባለፉት ጥቂት ዓመታት በ800 ሜትር፣ 1,500 ሜትር እንዲሁም 3,000 ሜትር ርቀት የበርካታ አትሌቶችን ፊት ከመመልከት ባሻገር አዲስ ክብረ ወሰኖች ማስመዝገብ የቻሉ አትሌቶችን ስም መጥቀስ ይቻላል፡፡ በዘንድሮው የመካከለኛ ርቀት የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ላይ እየተሳተፉ ያሉት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በተሳተፉበት የዙር ውድድር ወጤት መሠረት ከወዲሁ ለቀጣዩ ዓመት ውድድር ስኬታቸውን ሊቆርጡ የቻሉበትን ነጥብ መሰብሰብ ችለዋል፡፡
በተለይ በሁለቱም ጾታ 1,500 ሜትር፣ በ800 ሜትር እና በ3,000 ሜትር ርቀቶች ላይ አዲስ ክብረ ወሰን ጨምሮ የራሳቸውን ጥሩ ሰዓት ማስመዝገብ ችለዋል፡፡
ጉዳፍ ፀጋይ 1,500 ሜትርን 3፡53.09 በማጠናቀቅ ከምንጊዜም ምርጥ አሥር የርቀቱ ሰዓት ሆኖ ተመዝግቦላታል፡፡ የጉዳፍ አዲስ ክብረ ወሰን በቤት ውስጥ ብቻም ሳይሆን ማሪያ ሞቶላ በ800 ሜትር ካስመዘገበችው 1፡55.19 ክብረ ወሰን ቀጥሎ ከአፍሪካ ሁለተኛው ደረጃ ላይ እንድትቀመጥ ያስቻላትን፣ 1:57.52 የዓመቱ ፈጣን ሰዓትና የኢትዮጵያን ክብረ ወስን በፈረንሣይ ማስመዝገብ ችላለች፡፡
ሌላኛዋ ኢትዮጵያዊት ለምለም ኃይሉ በ3,000 ሜትር ርቀቱን 8፡31.24 ስታጠናቅቅ የርቀቱ የረዥም ጊዜ ባለክብረ ወሰን ገንዘቤ ዲባባ ገና 200 ሜትር ላይ አቋርጣለች፡፡
በተለያዩ ከተሞች ላይ ሲከናወን የነበረው የቤት ወስጥ ውድድሩ ላይ ሰለሞን ባረጋ 1,500 ሜትር 3፡32.97 በመግባት፣ እንዲሁም ሀብታም ዓለሙ በ800 ሜትር 1፡58.19 በማጠናቀቅ የራሳቸውን ምርጥ ሰዓት ማምጣት ችለዋል፡፡
የዘንድሮ ተዘዋዋሪ አትሌቲክስ የቤት ውስጥ ሻምፒዮና ወርቅ፣ ብርና ነሐስ የሚል ስያሜ ተስጥቶታል፡፡ ከወራት በፊት የጀመረው ውድድሩ ጥሩ ነጥብ የሰበሰቡ አትሌቶች እ.ኤ.አ. 2022 በቤልግሬድ በሚከናወነው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ መሳተፍ የሚችሉ 11 አትሌቶችን ይፋ አድርገዋል፡፡ ከነዚህም ውስጥ በሴቶች 800 ሜትር ሀብታም ዓለሙ፣ በ3,000 ሜትር ለምለም ኃይሉ እንዲሁም በወንዶች 1,500 ሜትር ሰለሞን ባረጋ ከወዲህ መቀላቀል የቻሉ ኢትዮጵያውያን ናቸው፡፡