ከተጀመረ ሦስተኛ ሳምንቱን የያዘው የ2013 ዓ.ም. የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ውድድር የኮቪድ ፕሮቶኮልን በማጓደሉ ሊግ ካምፓኒው ከጤና ሚኒስቴር ማስጠንቂቄያ ደርሶታል፡፡ የውድድሩ አምስት ቅድመ ጨዋታዎች በአዲስ አበባ ስታዲየም እያደረገ የሚገኘው ሊግ ካምፓኒው፣ በጨዋታ ወቅት ከኮቪድ-19 ጋር ማድረግ ስለሚገባቸው ጥንቃቄዎች ላይ መዘናጋት በማሳየቱ ጥንቃቄ አዘል ማስጠንቀቄያ እንደደረሰው የሊግ ካምፓኒው አስታውቋል፡፡
እሑድ ታኅሣሥ 10 ቀን 2013 ዓ.ም. በሁለተኛ ሳምንት የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ መርሐ ግብር ሀዲያ ሆሳዕና ከባህር ዳር ከተማ ጋር ባደረጉት ጨዋታ የሀዲያ ሆሳዕና አጥቂ ዳዋ ሆጤሳ ግብ ካስቆጠረ በኋላ ወደ ተመልካቾቹ በማምራት ያደረገው ያልተገባ መነካካትና መተቃቀፍ ሊግ ካምፓኒውን አስተችቶታል፡፡
የዘንድሮ የፕሪየምር ሊግ ውድድር ከመጀመሩ አስቀድሞ የኮቪድ-19 ወረረሽኝን ለመከላከል ፕሮቶኮል አውጥቶ ከሊግ ካምፓኒው ጋር የተወያየው ጤና ሚኒስቴር፣ እነዚህ ፕሮቶኮሎች ካልተጠበቁ ሊጉ ሊሰረዝ የሚያስችል ውሳኔ ላይ ሊደረስ እንደሚችል አስጠንቅቋል፡፡
በዚህም መሠረት ክለቦች መሠረታዊ የሆኑ ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ ጋር በተያያዘ መደረግ ስላለባቸው ጥንቃቄዎች መዘናጋት እንደሌለባቸው ጤና ሚኒስቴሩ አሳስቧል፡፡ ታኅሣሥ 3 ቀን የተጀመረው የቤት ኪንግ ፕሪሚየር ሊግ ውድድር ያለምንም ተመልካች እየተከናወነ ሲሆን ስታዲዮሞች ለተመልካች ክፍት ይሆኑ የሚል አስተያየት ቢኖርም ሊግ ካምፓኒው ግን አሁን ላይ እንዲገቡ የተፈቀደላቸው የአሥር ተመልካቾች ቁጥር ቢቀንስም ምርጫቸው እንደሆነ የሊግ ካምፓኒው ሥራ አስኪያጅ አቶ ክፍሌ ሰይፈ ለሪፖርተር አስረድተዋል፡፡
እንደ ሥራ አስኪያጁ አስተያየት ከሆነ ክለቦችን ለመደገፍ የሚገቡ ተመልካቾች ጥንቃቄ ከማድረግ አንፃር ክፍተኛ የሆነ ጉድለት እንደሚስተዋልባቸውም አስረድተዋል፡፡ ከዚህም አንፃር ቀጣይ ጨዋታዎች ላይ ተመልካቾችን ወደ ስታዲየም እንዳይገቡ የሚል ውሳኔ ላይ ሊደረስ እንደሚችልም አቶ አክሊሉ አክለዋል፡፡
ጤና ሚኒስቴር የሰጠውን ማስጠንቀቂያ ተከትሎ ክለቦች ከወዲሁ ተጫዋቾቻቸውን ማስጠንቀቅ እንደሚገባቸው ተገልጿል፡፡ ቀጣይ የቤት ኪንግ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎች በአዲስ አበባ ስታዲየም የሚከናወኑ ሲሆን ከአምስት ጨዋታ በኋላ ባህር ዳር ወይም ጅማ ስታዲየም አምስት ጨዋታዎችን የሚያስተናግዱ ይሆናል፡፡