Wednesday, June 7, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናየአገር መከላከያ ሠራዊት ፖለቲካ ውስጥ ጣልቃ እንዲገባ ግፊት እንደሚደረግበት ተገለጸ

የአገር መከላከያ ሠራዊት ፖለቲካ ውስጥ ጣልቃ እንዲገባ ግፊት እንደሚደረግበት ተገለጸ

ቀን:

የኢትዮጵያ አገር መከላከያ ሠራዊት የውጭ ግንኙነት ጉዳዮች ዳይሬክተር፣ ሠራዊቱ በፖለቲካው ውስጥ ጣልቃ እንዲገባ በ‹‹ጽንፈኛ ቡድኖች›› ግፊት እየተደረገበት እንደሚገኝ ተናገሩ፡፡

ዳይሬክተሩ ብርጋዴር ጄኔራል ቡልቲ ታደሰ ሰኞ ኅዳር 7 ቀን 2013 ዓ.ም. ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ኮማንድ ፖስት ቃል አቀባይ ሬድዋን ሁሴን (አምባሳደር) ጋር በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ‹‹ምንም እንኳን በሕገ መንግሥቱና በሠራዊቱ መተዳዳሪያ ደንብ መከላከያ በፖለቲካ ጣልቃ እንደማይገባ የተደነገገ ቢሆንም፣ ጽንፈኛ ቡድኖች ሠራዊቱ በፖለቲካ ጉዳዮች ጣልቃ እንዲገባ እየገፉት ነው፤›› ብለዋል፡፡

ባለፉት ሁለት ዓመታት መንግሥት ይኼንን የሠራዊትና የፖለቲካ መቀላቀልን ለማስቀረት በርካታ ጥረቶችን ያደረገ ቢሆንም፣ በዚህ ግፊትና ፍላጎት ሳቢያም ሠራዊቱን እጅግ ያሳዘነና ያስቆጣ ግጭት እንዲፈጠር ተደርጓል ሲሉ አክለዋል፡፡

በዓለም አቀፍ ልምድና አሠራር መሠረት የመከላከያም ሆነ የፖሊስ ኃይል ፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት ሊኖረው እንደማይገባ እየታወቀ፣ ‹‹ጽንፈኛው ቡድን›› ይኼንን በመፈለጉ በሠራዊቱ ላይ ተኩስ ከፍቷል ሲሉም አምርረው ተናግረዋል፡፡ ይኼም ያልታሰበና ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰ ክስተት በመሆኑ፣ እንዲሁም ሠራዊቱ አካባቢውን በእርሻና በተለያዩ የልማት ሥራዎች እያገዘ ሳለ በመፈጸሙ እጅግ ያሳዝናል ሲሉ አስረድተዋል፡፡

‹‹በኢትዮጵያ ታሪክ ያልታየና ድንገተኛ ክስተት በመሆኑ እኛን እጅግ ያናደደና ያስቆጣ ጉዳይ ነው፤›› ሲሉም ገልጸዋል፡፡

ምናልባት እንዲህ ያለ ጥቃት ከውጭ ኃይሎችና ወራሪዎች ሊመጣ ይችላል ተብሎ ሊጠበቅ ቢችልም ቅሉ፣ ‹‹እነዚህ ጽንፈኛ ኃይሎች አብረዋቸው በሚበሉ፣ በሚጠጡና በሚተኙ ላይ ይፋዊ ጦርነት ይከፍታሉ ብለን አልገመትንም ነበር፤›› ብለዋል፡፡

ይኼ የተከሰተው በእርሻ ወቅት ድጋፍ ሲያደርግ በነበረ፣ ለምሥጋና በተዘጋጀ ድግስ ላይ የተሳተፈ ሠራዊት ላይ እንደሆነ፣ የሠራዊቱ አባላትና አዛዦች እንደታገቱ ገልጸው ይሙቱ ይኑሩ እንደማይታወቅም ተናግረዋል፡፡

‹‹ኮማንደሮች እስር ቤት ናቸው፣ ምናልባትም በሕይወት ላይኖሩ ይችላሉ አናውቅም፤›› ሲሉ ብርጋዴር ጄኔራል ቡልቲ አስረድተዋል፡፡

ሠራዊቱ ላደረገው መልካም ሥራ ያገኘው ምላሽ ይኼ ነው በማለትም፣ ክስተቱን ‹‹አሳፋሪ›› ሲሉ ገልጸውታል፡፡

በመግለጫው ላይ ማብራሪያ የሰጡት ሬድዋን (አምባሳደር) በበኩላቸው፣ ግጭቱ በአገር ደረጃ እንዲሰፋና ሌሎችም የአገሪቱ አካባቢዎች ተመሳሳይ ሁኔታዎች እንዲፈጠሩ ፍላጎት እንዳለ ጠቁመው፣ በማይ-ካድራ  የተከሰተው ጭፍጨፋ በሌሎች አካባቢ የሚኖሩ ሰዎችን በማናደድ በትግራይ ተወላጆች ላይ ጥቃት እንዲፈጸምና ጉዳዩ እንዲባባስ በማለም የትግራይ ልዩ ኃይል በተሰጠው ትዕዛዝ መሠረት ያደረሰው ጥፋት ሊሆን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡ ግጭቱ እንዲሰፋም ሲሉ ባህር ዳርንና ጎንደርን በሮኬት አጥቅተዋል ብለዋል፡፡

ስለዚህ መንግሥት ግልጽ ባደረገው መሠረት በሕወሓት እጅ የሚገኙ መሣሪያዎች ካልጠፉ ወይም ካልተወረሱ፣ በሌሎች አካባቢዎች ጥቃት ከማድረስ ወደኋላ እንደማይሉና ወደ እርስ በርስ ጦርነት የሚያስገባ ብጥብጥና ሁከት ለመፍጠር ፍላጎት አላቸው በማለት ኮንነዋል፡፡

ሬድዋን (አምባሳደር) አክለውም በብርጋዴር ጄኔራል ቡልቲ እንደተገለጸው የት እንደገቡ የማይታወቁ የመከላከያ ሠራዊቱ አባላት መኖራቸውን በማረጋገጥ፣ በተለይ በመቀሌ የሠራዊቱ ተዋጊዎች ጥቂት ስለነበሩ በቶሎ መጠቃቸውንም አስታውሰዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

አወዛጋቢው የሕገ መንግሥት ማሻሻያ ጉዳይ

በኢትዮጵያ የሕገ መንግሥት ማሻሻል ጉዳይ ከፍተኛ የፖለቲካ ውዝግብ የሚቀሰቀስበት...

 መፍትሔ  ያላዘለው  የጎዳና  መደብሮችን  ማፍረስ

በአበበ ፍቅር ያለፉት ስድስት ዓመታት በርካቶች በግጭቶችና በመፈናቀሎች በከፍተኛ ሁኔታ...

የተናደው ከቀደምቱ አንዱ የነበረው የአዲስ አበባ ታሪካዊ ሕንፃ

ዳግማዊ አፄ ምኒልክ በ19ኛው ክፍለ ዘመን መገባደጃ መናገሻ ከተማቸውን...

የአከርካሪ አጥንት ሕክምናን ከፍ ያደረገው ‘ካይሮፕራክቲክ’

በአፍሪካ ከጀርባ ሕመም ጋር በተያያዘ በርካታ ሰዎች ለከፍተኛ የአካል...