በተመስገን ተጋፋው
የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝን ተከትሎ በወጣው የትራንስፖርት አገልግሎት ታሪፍና የመጫን አቅም መመርያ ላይ ማሻሻያ መደረጉን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ትራንስፖርት ባለሥልጣን አስታወቀ፡፡
ባለሥልጣኑ ማሻሻያውን አስመልክቶ ጳጉሜን 2 ቀን 2012 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ፣ የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ ሚዲባስ፣ የአንበሳ አውቶቡስ፣ ሸገርና ሃይገር ባሶች በወንበር ልክ እንዲጭኑ፣ የሚኒባስ ታክሲዎች ከኋላ ባለው መቀመጫ ላይ ከሁለት ሰው በላይ መጫን እንደማይችሉ ተገልጿል፡፡
ባለሦስትና ባለአራት እግር (ባጃጅ) ተሽከርካሪዎች ከነሹፌሩ ሦስት ሰው መጫን እንደሚችሉ፣ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መመርያ መሠረት 25 በመቶ የመጫን አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው ቀላል ባቡር ወደ 75 በመቶ ከፍ እንዲል መደረጉ ታውቋል፡፡
የሚኒባስ ታሪፍ ማስተካከያ ላይ ብር 1.50 የነበረው 2 ብር፣ 3 ብር የነበረው 4 ብር፣ 4፡50 የነበረው 6 ብር፣ 6 ብር የነበረው 8 ብር፣ 7.50 የነበረው 10 ብር፣ 9 ብር የነበረው 12 ብር፣ 10.50 የነበረው 13 ብር፣ 12 ብር የነበረው 15 ብር፣ 13.50 የነበረው 17 ብር፣ 15 ብር የነበረው 19 ብር፣ 16.50 የነበረው 20 ብር፣ 18 ብር የነበረው 22 ብር ሆኖ ማሻሻያ መደረጉ ተገልጿል፡፡
የአንበሳ የከተማ አውቶቡስ፣ የሸገር ባስ፣ የመንግሥት ሠራተኞች ሰርቪስ፣ አውቶቡሶችና ቀላል ባቡር ላይ ማሻሻያ አለመደረጉንና በፊት በነበረው ታሪፍ እንደሚያስከፍሉ ታውቋል፡፡
ከተፈቀደው ሰው በላይ የጫነ አሽከርካሪ ከአንድ ሺሕ ብር ጀምሮ እንደሚቀጣ፣ ከታሪፍ በላይ የሚያስከፍሉ አሽከርካሪዎች ደግሞ 1,500 ብር ቅጣት እንደሚጠብቃቸውም ተገልጿል፡፡
ይህንንም ለመቆጣጠር የትራፊክ ፖሊስና የፀጥታ አካላት በጋራ ተቀናጅተው እንደሚሠሩ፣ ለማኅበረሰቡም ከታሪፍ በላይ የሚያስከፍሉና ትርፍ የሚጭኑ አሽከርካሪዎችን ለመጠቆም የሚያገለግል የስልክ ቁጥር በቅርቡ ይፋ ይሆናል ተብሏል፡፡
ማንኛውም የትራንስፖርት ተጠቃሚ የአፍና የአፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል ያላደረገ ከሆነ አገልግሎት ማግኘት እንደማይችልም ባለሥልጣኑ አስታውቋል፡፡