የወላይታ ዞንን በመወከል የደቡብ ክልል ምክር ቤት አባላት የሆኑ 38 ተወካዮች የክልሉ ምክር ቤት የሕዝቦችን ሕገ መንግሥታዊ መብት የማያከብር ነው በማለት ወቅሰው፣ ‹‹ድምፃችን በማይሰማበት ሥፍራ በስብሰባዎች ለመሳተፍ አንገደድም፤›› ሲሉ ራሳቸውን አገለሉ፡፡
ሰላሳ ስምንቱ የምክር ቤቱ አባላት በፊርማቸው አባሪ አድርገው ለክልሉ ምክር ቤት ባስገቡት ደብዳቤ፣ የወላይታ ብሔር በክልልነት ለመደራጀት ለምክር ቤቱ ያቀረበው ጥያቄ ምላሽ ሳያገኝና በተደጋጋሚ በተደረጉ ስብሰባዎች በአጀንዳነት እንዳይቀርብ መደረጉን በማውሳት፣ ይኼ ቅሬታ እንዲሰማን አድርጓል ብለዋል፡፡
የብሔሩ በክልል የመደራጀት ጥያቄ ለምክር ቤቱ ከቀረበ አንድ ዓመት ያለፈው ቢሆንም፣ ‹‹የክልሉ ምክር ቤት ለመረጠን ሕዝብ ጥያቄ በሕገ መንግሥቱ መሠረት ምላሽ መስጠት ሲገባው በጥናት ይመለሳል በማለት የሕግ የበላይነትን ባለማክበሩ፣ ሕዝቡ በሰላማዊ መንገድ የራሱን ብሔር ክልል ለመመሥረት ካለው ፍላጎት የተነሳ፣ በተደጋጋሚ መንገድ በሰላማዊ ሰልፍ መግለጹ ይታወሳል፤›› በማለት አስታውሰው፣ የምክር ቤቱ አባላትም ይኼ ጥያቄ የሕዝብ ጥያቄ መሆኑን ሲያስረዱና ሲወተውቱ ቆይተዋል በማለት በደብዳቤያቸው ጠቁመዋል፡፡
ይሁን እንጂ ምክር ቤቱ ጉዳዩን አጀንዳ አድርጎ ሕዝበ ውሳኔ ከማደራጀት ይልቅ በጥናት ይመለሳል በማለት እንቢተኝነትን መርጧል በማለት ወቅሰው፣ በዚህም የሕገ መንግሥት ጥሰት ተፈጽሟል ብለዋል፡፡
ስለዚህም ምክር ቤቱ ስህተቱን አርሞና ይቅርታ ጠይቆ አፋጣኝ ምላሽ እስካልተሰጠ ድረስ፣ የወላይታ ብሔር ተወካይ የሆኑ የክልሉ ምክር ቤት አባላት፣ ‹‹ሕገ መንግሥትና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን አክብሮ የሕዝባችን ጥያቄ በአግባቡ በማያስተናግድና የእኛ የምክር ቤቱን አባላት ድምፅ ለማስተናገድ ፈቃደኛ ባልሆነ ምክር ቤት የሕዝባችን ድምፅ ማስከበር በማንችልበት ሁኔታ፣ በምክር ቤቱ ለመቆየትም ሆነ በጉባዔ ለመገኘት የማንገደድ መሆኑን ለሕዝባችን ክብር፣ ሞገስና ሉዓላዊ የሥልጣን ባለቤትነት ስንል ለማሳወቅ እንወዳለን፤›› በማለት ከምክር ቤቱ ራሳቸውን ማግለላቸውን አስታውቀዋል፡፡