ጃፓን ከጅማ – ጭዳ ድረስ ለሚገነባው መንገድ 89 ሚሊዮን ዶላር ብድር ፈቀደች፡፡
ጃፓን ለዚህ የመንገድ ፕሮጀክት የሚውለውን ብድር መፍቀዷን የሚያረጋግጠው ስምምነት፣ ማክሰኞ ኅዳር 16 ቀን 2012 ዓ.ም. በአምባሳደርዋ ማትሱንጋ ዳኡሲኤና በገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታው አቶ አድማሱ ነበበ ተፈርሟል፡፡
የጃፓን መንግሥት የፈቀደው የብድር ስምምነት የተደረገው የኢትዮጵያ መንግሥት በቅርቡ በአፍሪካ ጃፓን የጋራ ልማት ትብብር ጉባዔ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር)፣ የጃፓን ዕርዳታ ከፍ እንዲል በጠየቁት መሠረት የተሰጠ አዎንታዊ ምላሽ ነው ተብሏል፡፡
የሚገነባው የጅማ – ጭዳ መንገድ ፕሮጀክት 80 ኪሎ ሜትር ርዝማኔ እንዳለው፣ የኦሮሚያንና የደቡብ ክልሎችን የሚያካትት ትልቅ ፕሮጀክት መሆኑ ተገልጿል፡፡
በገንዘብ ሚኒስቴር በተካሄደው የብድር ስምምነት ፊርማ ላይ እንደተገለጸው፣ የብድሩ መገኘት የመንገድ ፕሮጀክቱን በቶሎ ለማስጀመር ያግዛል፡፡