በኦሮሞ ሕዝብ ዘንድ በየዓመቱ የሚከበረው የኢሬቻ በዓል ለመጀመርያ ጊዜ በአዲስ አበባ ከተማ ቅዳሜ መስከረም 24 ቀን 2012 ዓ.ም. ተከብሯል፡፡ ክብረ በዓሉ በአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ፓርክ ውስጥና በመስቀል አደባባይ አባ ገዳዎችና የመንግሥት ሹማምንት ጨምሮ በርካታ የበዓሉ ታዳሚዎች ተገኝተውበታል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) በዓሉን አስመልክቶ በዋዜማው ባስተላለፉት መልዕክታቸው፣ ኢሬቻ የኦሮሞ ሕዝብ በሃይማኖትና በፖለቲካ አመለካከት ሳይለያይ አንድነቱን የሚያሳይበት በዓል ነው ብለዋል፡፡ የኦሮሞ ሕዝብ ሰማይና ምድር፣ ወንዞችና ሐይቆች፣ ክረምትና በጋ፣ ሌሊትና ቀን፣ ሕይወትና ሞትን ለፈጠረው ፈጣሪ ምስጋና የሚያቀርብበት ቀን ነው ሲሉም አክለዋል፡፡ ኢሬቻ በመንግሥታቱ ድርጅት የትምህርት፣ ሳይንስና ባህል ድርጅት (ዩኔስኮ) ተመዝግቦ ያለው የገዳ ሥርዓት አካል መሆኑን ያስታወሱት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ የገዳ ሥርዓት ከሥርዓትነትም አልፎ ዘመናዊ የአመራር ስልትን ለዓለም ያበረከተ ነው በማለት “ዛሬም ለችግራችን መፍትሔ የሚሆነው ወደ ቀደመው ባህላችን ተመልሰን ከዘመናዊ ሥርዓት ጋር በማስተሳሰር የገዳ ሥርዓትም መጠቀም ነው፤” ሲሉ አስምረውበታል፡፡ በዋዜማው በመስቀል አደባባይ የተከናወነው ዝግጅት በአባ ገዳዎች ምርቃት የተጀመረ ሲሆን፣ ባህላዊና ትውፊታዊ መሰናዶዎች ቀርቦበታል፡፡ በሥነ ሥርዓቱ ላይ የኦሮሚያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ሽመልስ አብዲሳና የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ (ኢንጂነር) ጨምሮ ከፍተኛ የመንግሥት ኃላፊዎች ተገኝተዋል፡፡ ለክብረ በዓሉ መስቀል አደባባይ ውኃ የተሞላባቸው ሁለት ገንዳዎች፣ እንዲሁም ከቅዱስ እስጢፋኖስ ቤተ ክርስቲያን ጀርባ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን ፓርክ ውስጥም ሦስት ገንዳዎች በውኃ ተሞልተው ተዘጋጅተዋል፡፡ ለዚሁ አገልገሎት 50 ያህል የውኃ ቦቲ ተሽከርካሪዎች ተሳትፈዋል፡፡ በዋዜማው መስከረም 23 ቀን ወደ አዲስ አበባ የሚያስገቡ ዋና ዋና መንገዶችና በመሃል ከተማ አብዛኞቹ መተላለፊዎች ለትራፊክ ዝግ በመሆናቸው ኅብረተሰቡ በትራንስፖርት እጥረት ሲቸገር ተስተውሏል፡፡ የኢሬቻ በዓልን ምክንያት በማድረግም መስከረም 19 ቀን በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል የተከፈተው ኤግዚቢሽንና ባዛር ለ10 ቀናት ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡