በሔለን ተስፋዬ
በየዓመቱ ሴብቴምበር 27 ቀን በዓለም ዙርያ የሚከበረው የዓለም ቱሪዝም ቀን ዘንድሮ በኢትዮጵያ ደረጃ መስከረም 17 ቀን 2012 ዓ.ም. (ሴብቴምበር 28) የተከበረው በምሥራቃዊቷ ከተማ ድሬዳዋ ነው፡፡ የበዓሉ ቀን በዋናነት ሁሉንም አገሮች የሚያስተሳስረው ሴብቴምበር 27ን ባይለቅም እንደየአገሮቹ ፍላጎትና ዝግጅት ከዋዜማ እስከ ሳምንት ድረስ በልዩ ልዩ መሰናዶዎች ይከበራል፡፡
‹‹ቱሪዝም ለሥራ ዕድል ፈጠራና ለተሻለ ሕይወት›› የሚለውን መሪ ቃል የያዘውን የዘንድሮ በዓል ለማክበር የመንግሥት ባለሥልጣናትና የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎችን ከአዲስ አበባ ወደ ድሬዳዋ የተጓዙት እንደቀደሙት ዓመታት በአውቶቡሶች ሳይሆን በምድር ባቡር ነው፡፡
ዓርብ መስከረም 16 ቀን ረፋድ ላይ ከአዲስ አበባ ተነስቶ ቢሾፍቱን፣ አዳማን፣ ወለንጪቲ፣ መተሃራ፣ አዋሽ፣ ሜኤሶ፣ ጭሮ፣ ሂርናና ሌሎች ከተሞችን አቆራርጦ ድሬዳዋ የደረሰው ምሽት አራት ሰዓት ላይ ነበር፡፡
በማግሥቱ መስከረም 17 ቀን የበዓሉ መክፈቻ ሥነ ሥርዓት የተከናወነው ከ100 ዓመታት በላይ ዕድሜ ባስቆጠረው ኢትዮ አሊያንስ ግቢ በተዘጋጀው የፎቶ ዐውደ ርዕይ ነው፡፡ በተከታታይም የኢትዮ ጂቡቲ ምድር ባቡር ግቢ፣ ድሬዳዋ ሙዚየም ከመጎብኘታቸው ባለፈም እስከ ሽንሌ ድረስ ጉዞ ተደርጓል፡፡
የዘንድሮውን የዓለም ቱሪዝም ቀንን ለማዘጋጀት ድሬዳዋ ዕድሉን ማግኘቷ እንዳስደሰታቸው የተናገሩት የከተማዋ ምክትል ከንቲባ አቶ አህመድ መሐመድ ቡህ፣ የከተማዋን ባህላዊ እሴቶች፣ የቱሪስት መዳረጃዎችና አገልግሎት ሰጪ መሠረተ ልማቶችን ለማስተዋወቅ መልካም ዕድልን እንደሚፈጥር ገልጸዋል፡፡
በተከታታይ ቀናት ከነበሩት አከባበሮች አንዱ የድሬዳዋ ባህላዊ ጣፋጭ ምግቦች ፌስቲቫል ሲሆን በሚሊኒየም ፓርክ ተከናውኗል፡፡
ከድሬዳዋ ከተማ የብስክሌት ክለቦች በተወጣጡ ተወዳዳሪዎች መካከል የኮርዝ ብስክሌት፣ እንዲሁም በየዓመቱ የሚካሄደው የግመል ግልቢያ ውድድርም የበዓሉ ድምቀቶች ነበሩ፡፡
በኢትዮጵያ እግር ኳስና ብስክሌት ታሪክ ስመጥር ስፖርተኞችንና ክለቦችን፣ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮና ለመጀመርያ ጊዜ ኢትዮጵያን በተከታታይ የወከሉት ጥጥ ማኅበር (ጨርቃ ጨርቅ)፣ ስሜንትና ምድር ባቡርን ያፈራችው ድሬዳዋ ባዘጋጀችው የቱሪዝም ቀን፣ በተካሄደው የብስክሌት ውድድር በክብር ከታደሙት መካከል በሞስኮ ኦሊምፒክ በብስክሌት ተወዳዳሪ የነበሩት የኢትዮጵያ ሻምፒዮኑ ጀማል ሮጎራና ሰለሞን ተሰማ ይገኙበታል፡፡
ድሬዳዋ ከመስከረም 17 እስከ 21 የተከበረው የቱሪዝም ቀን የማጠቃለያ መርሐ ግብር ከመሪው ቃል ጋር የተያያዘ ዐውደ ጥናት እንደሚካሄድበት ታውቋል፡፡ ድሬዳዋ በ2003 ዓ.ም. ከሐረር ጋር የዓለም ቱሪዝም ቀንን በጋራ ማዘጋጀታቸው ይታወሳል፡፡
የተባበሩት መንግሥታት የዓለም ቱሪዝም ድርጅት ከ40 ዓመታት በፊት የዓለም ቱሪዝም ቀንን ማክበር የጀመረው፣ ቱሪዝም በዓለም አቀፍ ኅብረተሰብ ዘንድ ያለውን ጠቀሜታና የሚኖረውን ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ እሴቶችን ለማስገንዘብ ነው፡፡ እ.ኤ.አ. ሴብቴምበር 27 ቀን የሚከበረውን የቱሪዝም ቀን በኢትዮጵያ ከብሔራዊው በዓል ደመራና መስቀል ጋር በመግጠሙ ልዩ ድባብን ፈጥሮለታል፡፡ ጳጉሜን 5 በሚሆንበት ጊዜ በዓሉ መስከረም 17 ሲውል፣ ጳጉሜን 6 በሚሆንበት አራተኛ ዓመት ግን ወደ መስከረም 16 ያፈገፍጋል፡፡ በዚህም መሠረት የዘንድሮው በዓል በዓለም ዙሪያ ዓርብ መስከረም 16 ቀን 2012 ዓ.ም. (ሴብቴምበር 27 ቀን 2019) ሲከበር፣ ድርጅቱ በተለይ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያከበረው በህንድ ኒውዴልሂ ከተማ ነው፡፡