Thursday, June 1, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊኑሮ ከብርሃን ጮራ ጫካ በኋላ

ኑሮ ከብርሃን ጮራ ጫካ በኋላ

ቀን:

በተመስገን ተጋፋው

እሳቸው ካረጀ ወንበራቸው ላይ ቁጭ ብለዋል፡፡ የሚቀመስ ለመሥራት ደፋ ቀና የሚሉ በዕድሜያቸው ገፋ ያሉ አረጋውያንም ይታያሉ፡፡ ከፊታቸው ገፅታ ደስታን ማንበብ ቢቻልም፣ ኑሮን ለማሸነፍ ብዙ ውጣ ውረዶችን እንዳሳለፉ ለመገመት አይከብድም፡፡ ዕድሜያቸው ወደ 70ዎቹ ይጠጋል፡፡

ወ/ሮ አስቴር መንግሥቱ፣ ባለቤታቸው አቶ ተስፋዬ ሻንቆ በሞት ሳይለዩዋቸው በፊት፣ ኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 ሙስሊም መቃብር በሚባል አካባቢ የሰው ቤት በመጠበቅ ይተዳደሩ ነበር፡፡

የአራት ልጆች እናት የሆኑት ወ/ሮ አስቴር፣ ልጆቻቸውን ልብስ በማጠብና ሌሎች ሥራዎችን በመሥራት እንዳሳደጉ ይናገራሉ፡፡

ባለቤታቸውም ታታሪ እንደነበሩ፣ ኑሮን ለማሸነፍና የዕለት ጉርሳቸውን ለመሙላት የተለያዩ ሥራዎችን ይሠሩ እንደነበር በማስታወስ፣ የተደላደለ ሕይወት ባይኖሩም የከፋ እንዳልነበር፤ የባለቤታቸው ሞት ግን ሁሉን ነገር እንዳመሰቃቀለው ይናገራሉ፡፡

ከበፊት መኖሪያቸው ልቀቁ የተባሉትም የባለቤታቸውን ሞት ተከትሎ ነበር፡፡ ይህ ከባድ ጭንቀት ውስጥ የከተታቸው ወ/ሮ አስቴር፣ ኮልፌ አካባቢ በሚገኘው ብርሃን ጮራ ጫካ ውስጥ ገብተው መኖርን ይመርጣሉ፡፡

አብዛኛውን ጊዜ ከሚመለከተው አካል መጠለያ ለማግኘት ቢጠይቁም፣ ምንም ዓይነት ምላሽ እንዳላገኙና በዚህ ምክንያትም በመሰላቸት ኑሯቸውን በጫካ እንዳደረጉ፣ ይህ በሕይወታቸው ላይ ትልቅ እንግልትና ስቃይ እንደፈጠረባቸው ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ወ/ሮ አስቴር በጫካ ውስጥ ለዓመታት መኖራቸውን ይናገራሉ፡፡ ‹‹አካባቢው ለመኖር ከባድ ነበር፡፡ ጀንበር ጠለቅ በምትልባት ጊዜ ሥፍራው ላይ ከእንስሳት ውጪ ሰው አይገኝም፡፡ በፌስታል፣ በካርቶንና በሌሎች ነገሮች በተጠጋገነች ትንሽ ጎጆ ውስጥ ብዙ መከራን አሳልፌያለሁ፤›› ይላሉ፡፡

እግር ለመዘርጋት በማይመች ቤት ውስጥ ከልጃቸው ጋር ይኖሩ እንደነበር ለሚናገሩት ወ/ሮ አልማዝ፣ በመሸ ቁጥር ከአውሬ ጋር መጋፈጡም ቀላል አልነበረም፡፡

ሌት በጭንቅ ቀን በልመና ሲያሳልፉ፤ ልጃቸው ደግሞ ሸክም እየሠራ ያግዛቸዋል፡፡ ይህም ሆኖ የሚላስ የሚቀመስ የሚጠፋበት ጊዜ በርካታ ነበር፡፡ ሦስቱ ልጆቻቸው የተሻለ ኑሮ ቢኖራቸውም፣ ‹እናታችን የት ገባች› ብለው እንዳልፈለጓቸው አስረድተዋል፡፡ ‹‹የወላድ መካን ሆኛለሁ›› ብለዋል፡፡

ከብዙ ዓመታት ውጣ ውረዶች በኋላ በሕፃናትና በአረጋውያን ዙሪያ የሚሠራው ባዩሽ ኮልፌ በጎ አድራጎ ድርጅት ባደረገላቸው እገዛ ወረዳ 12 አካባቢ የቀበሌ ቤት ውስጥ መኖር ጀምረዋል፡፡

ወ/ሮ አስቴር በአሁኑ ሰዓት አካባቢን የማፅዳት ሥራ በመሥራት ላይ ሲገኙ፣ የባዩሽ ኮልፌ በጎ አድራጎ ድርጅትም በየወሩ ለቤት የሚሆኑ አስቤዛዎችን ገዝቶ እንደሚሰጣቸው ተናግረዋል፡፡

በተለያዩ ቦታዎች ላይ የወደቁ ሰዎች ላይ መንግሥት ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት ለችግረኞች ፈጥኖ መድረስ ይገባዋል ሲሉ ወ/ሮ አስቴር መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በአዲስ አበባ በድምቀት ተከበረ

የአዛርባጃን ኤምባሲ  የአዛርባጃንን ብሄራዊ ቀን በትላንትናው ዕለት አከበረ። ሰኞ...

የመንግሥትና የሃይማኖት ልዩነት መርህ በኢትዮጵያ

እንደ ኢትዮጵያ ባሉ አገሮች የሃይማኖት ተቋማት አዎንታዊ ሚና የጎላ...

ሐበሻ ቢራ ባለፈው በጀት ዓመት 310 ሚሊዮን ብር የተጣራ ትርፍ ማግኘቱን አስታወቀ

የአንድ አክሲዮን ሽያጭ ዋጋ 2,900 ብር እንዲሆን ተወስኗል የሐበሻ ቢራ...