በኢትዮጵያ ቡና እግር ኳስ ክለብ ትልቅ ቦታና ስም ካላቸው ተጨዋቾች በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳል፡፡ ካሳዬ አራጌ በአጨዋወት ፍልስፍናውም በአገሪቱ ከሚገኙ በርካታ አሠልጣኞች እንደሚለይ የሚያምኑ አሉ፡፡ ካሳዬ ባለፈው ሐሙስ ነሐሴ 29 ቀን 2011 ዓ.ም. ቀጣይ የክለቡ ዋና አሠልጣኝ ተደርጎ መሾሙን የኢትዮጵያ ቡና ክለብ አስታውቋል፡፡
ኢትዮጵያ ቡና በርካታ የደጋፊ ቁጥር ካላቸው ክለቦች በግንባር ቀደምትነት መጠቀሱ ክለቡ በማንኛውም ጊዜ ጨዋታ ሲኖረው ስታዲየም የሚታደመውን የተመልካች ቁጥር መመልከቱ በቂ ይሆናል፡፡ ለክለቡ ደጋፊዎች መብዛት ዓይነተኛ ሚና ከተወጡ ተጨዋቾች የዛሬው ኢትዮጵያ ቡና አሠልጣኝ ሆኖ የተሾመው ካሳዬ አራጌ ቀዳሚው ስለመሆኑም የሚናገሩ አሉ፡፡
የአሠልጣኙን ቅጥር ይፋ ያደረገው ኢትዮጵያ ቡና፣ ካሳዬ ለእሱ አጨዋወት ይመቹኛል የሚላቸውን ተጨዋቾች እንዲያስፈርም፣ በሌላ በኩል ደግሞ የማይመቹትን ተጨዋቾች እንዲያሰናብት ማረጋገጫ መስጠቱን ጭምር አሳውቋል፡፡ ኢትዮጵያ ቡና ቀደም ሲል ለሌሎች አሠልጣኞች ሥልጠና ተብሎ ውል ካላቸውም ይሁን ከሌላቸው መካከል የዘጠኝ ተጨዋቾች ውል እንዲቋረጥ ተደርጓል ብሏል፡፡ በምትካቸው ለካሳዬ አጨዋወት ይሆናሉ ተብሎ የታመነባቸው፣ በራሱ በካሳዬ ይሁንታ ያገኙ ተጨዋቾች ቅጥርና ዝውውር እየተፈጸመ ስለመሆኑ ጭምር ክለቡ ተናግሯል፡፡
ኢትዮጵያ ቡና ያለፈውን የውድድር ዓመት የጨዋታ መርሐ ግብር ምንም እንኳን ያጠናቀቀ ቢሆንም፣ እንደ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሁሉ ላለፉት 21 ዓመታት የቀጠለውን የተዟዙሮ የጨዋታ ሥርዓት (ፎርማት) ለሚቀጥለው 2012 የውድድር ዓመት እንደማያምንበት ማሳወቁ ይታወሳል፡፡