ግምታቸው ከአንድ ሚሊዮን ዶላር በላይ የሆኑ ከውጭ የሚገቡ ማናቸውም ዕቃዎች ዓለም አቀፍ ጨረታ ወጥቶባቸው መገዛት እንደሚኖርባቸው፣ ባንኮችም ለግዥ የሚሆን የውጭ ምንዛሪ ከመፍቀዳቸው በፊት ይህንን ማረጋገጥ እንደሚኖርባቸው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አስታወቀ፡፡
ባንኮች የውጭ ምንዛሪ ለማግኘት ለባንኮች የሚቀርበው የግዥ ፕሮፎርማ የጨረታው አሸናፊ ኩባንያ መሆኑን ሳያረጋግጡ፣ ሌተር ኦፍ ክሬዲት መክፈት የማይችሉ መሆኑን መመርያው ያስታውቃል፡፡
የመንግሥት የልማት ድርጅቶች በመንግሥት ግዥ አዋጅ ወይም ሌሎች ሕጎች መሠረት ዕቃዎቻቸውን መግዛት እንደሚችሉ፣ በውጭ አገር የባንክ ሒሳብ የሚጠቆሙም መመርያው እንደማይመለከታቸው በመመርያው ተጠቁሟል፡፡
መመርያው በተመለከተ ሪፖርተር ያነጋገራቸው የባንክ ባለሙያዎች እንደገለጹት፣ መመርያው ባለፈው ሳምንት ለባንኮች እንዲደርስ እየተደረገ ነበር፡፡ ሆኖም ባንኮች ከውጭ የሚገቡ ዕቃዎች ግዥ ትክክለኛነት ላይ በተወሰነ ደረጃ ማጣራት ያደርጉ እንደነበር አስታውሰው፣ በብሔራዊ ባንክ በኩልም እንዲህ ያለው አሠራር ተግባራዊ ሲደረግ ነበረ ብለዋል፡፡ ነገር ግን እንዲህ ባለው ደረጃ በመመርያ በግልጽ የተቀመጠ እንዳልነበር ጠቁመዋል፡፡
ብሔራዊ ባንክ ያወጣው ይህ መመርያ በተለይ ከውጭ የሚገቡ ዕቃዎች በጨረታ ተገዝተው እንዲገቡ ቢደረግ፣ በተሻለ ዋጋ ምርቶችን ማግኘት የሚያስችልና የውጭ ምንዛሪ ወጪን ለመቀነስ ያስችላል ከሚል እምነት ሊሆን እንደሚችል ባለሙያዎቹ ያምናሉ፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በአሁኑ ወቅት እያደገና አገርንም እየጎዳ ነው የተባለውን የውጭ ምንዛሪ ማሸሽን ለመቆጣጠር ዕገዛ ያደርጋል ተብሎ መመርያው እንዲወጣ ተደርጓል የሚል እምነት እንዳላቸው፣ የባንክ ባለሙያዎቹ ገልጸዋል፡፡