በኢትዮጵያና በአፍሪካ ኅብረት የካሜሩን አምባሳደር የነበሩት ጃስዮ አልፍሬድ፣ ሰኞ ነሐሴ 6 ቀን 2011 ዓ.ም. በኤምባሲው መኖሪያ ቤታቸው ሞተው ተገኙ፡፡
አምባሳደሩ እ.ኤ.አ. ከ2008 ጀምረው አገራቸውን ወክለው በአምባሳደርነት በኢትዮጵያ ሲሠሩ እንደነበር ይታወቃል፡፡
ተቀማጭነታቸው ካሜሩን የሆነ የተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን፣ ለአምባሳደሩ ሕልፈት ምክንያት የተፈጥሮ ሕመም ሊሆን እንደሚችል ዘግበዋል፡፡
እ.ኤ.አ. በ1957 የተወለዱት አምባሳደር አልፍሬድ አገራቸውን በተለያዩ ዘርፎች ያገለገሉ መሆናቸውን፣ ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣታቸው አስቀድሞ በአውሮፓ በተለይም በቤልጅየም በተመሳሳይ የዲፕሎማሲ ሥራ ላይ እንደነበሩ ግለ ማኅደራቸው ያሳያል፡፡
የአምባሳደሩን ድንገተኛ ሕልፈት ከተሰማ በኋላ በአዲስ አበባ የሚገኘው የካሜሩን ኤምባሲ፣ ለኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሪፖርት ማድረጉ ታውቋል፡፡
የአምባሳደሩ አስከሬን ለምርመራ ወደ ሆስፒታል መላኩን ከምንጮች ለማወቅ ተችሏል፡፡