ከወር በፊት የኅትመት ብርሃን ያየው የውብሸት ጌታሁን (ኮሎላ ደ.) ‹‹ኮቱ – ዱፌ›› የተሰኘው መጽሐፍ ባለፈው ሳምንት መግቢያ ላይ በብሔራዊ ቤተ መጻሕፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ (ወመዘክር) ተመርቋል። ደራሲው በመግቢያቸው እንደገለጹት፣ በቀደምት አባቶች ተጀምሮ ዘመናትን ያስቆጠረው ወርቃማ የአስተዳደር፣ የግጭት አፈታትና የማኅበራዊ ተግባቦት ባህል በሰነድ መልክ ለማስተላለፍ እንዲቻል፣ የመልካም አስተዳደርና ዴሞክራሲ ባህል በአገር ደረጃ እንዲዳብር ዕገዛ ለማድረግ ነው መጽሐፉ የተዘጋጀው።
በኦሮሞ አገር በቀል ዕውቀት ላይ የሚያጠነጥነው መጽሐፉ በመግቢያው እንደተጠቀሰው፣ በኦሮሞ አባቶች መማክርት የስብሰባ ሥርዓት የ‹‹ኮቱ – ዱፌ›› የአማርኛ ትርጉም ከሌላው የዘልማድ የፍትሕ አሰጣጥ ሥርዓት ጋር ተመሳሳይ ቢመስልም ከቃል ትርጉም ጀምሮ በጣም ይለያል፡፡
ቃሉ በቁሙ በጥሬ ትርጉሙ ሲመለከቱት ‹‹በላ – ልበልሃ›› ከሚለው ባህላዊ የፍትሕ አሰጣጥ ሥርዓት ጋር ይመሳሰላል፡፡ ይሁን እንጂ በሚያቅፈው ጉዳይ ወሰን ክልልም ሆነ በጥልቁ እንዲሁም በማኅበረሰባዊ ፍትሕና ሰብዓዊ ፋይዳው ላይ ጠለቅ ብሎ የሚሄድ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች በተለይም ልሂቃን አባቶች/አባገዳዎች በሚሰበሰቡበት ወቅት ኮቱ – ዱፌ የሚለውን አጠራር /ኮቱ/ ኑ እንመካከር በሚል ትርጉም አዘውትረው ሲጠቀሙበት ይታያል፡፡ ኮቱ የሚለው በአፋን ኦሮሞ ቀጥተኛ የቃል ትርጉም ‹‹ና›› እንደማለት ሲሆን፣ ዱፌ የሚለው ደግሞ ‹‹መጣሁ›› እንደ ማለት ነው፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ መጽሐፉ አገባብ በቀረበበት ሁኔታ ግን ኮቱ – ዱፌ ማለት ‹‹ስማ – ሰማሁ›› የሚለውን የመጠራራት በሐሳብ የመቀራረብ፣ የመጠያየቅ፣ የመወያየትና የመመካከር ጥልቅ የመግባባት ትርጉም ይይዛል፡፡
ኮቱ ዱፌ በስድስት ክፍሎች የተከፈለ ሲሆን፣ እነሱም የአገር በቀል ዕውቀት ሥርዓት ማብራሪያዎች፣ የአባ ገዳ ሥርዓት መዋቅርና አሠራር ማሳያ፣ የገዳ ሥርዓትና ሕግጋት፣ የኮቱ ዱፌ (ስማ – ሰማሁ) ተሳትፎ መሥፈርቶች፣ በምርመራ ለመታየት የሚበቁ የኮቱ ዱፌ ሥርዓት የግጭት ደረጃዎች ናቸው፡፡ አባሪዎችና ተጨማሪ መረጃዎች በመጨረሻው ክፍል ተካትተዋል፡፡ በዚህ መጣጥፍ የመጽሐፉን አንዱን ሰበዝ መርጠን እንዲህ ቀምረነዋል።
የግልግል ሥርዓትና ገጽታው “ኮቱ ዱፌ” የኦሮሞ ልሒቃን አባቶች የሚጠቀሙበት የግልግል ዳኝነት ሥርዓት ነው ማለት ይቻላል፡፡ አባቶች ተራ ንግግር ካልሆነ በስተቀር ከሁለት ሰዎች በላይ የሚደረግ የሐሳብ ልውውጥና ውይይትን ጨምሮ ማንኛውንም ንግግር የሚያካሂደው በስብሰባ መልክ ነው፡፡ ስብሰባውም የራሱ የሆነ አካሄድ አለው፡፡
ኮቱ ዱፌ የሚባልበት ምክንያትም አንድ ሰው ከአንደኛው ቡድን “ኮቱ” ና ብሎ ስለሚጠራና ከሁለተኛው ቡድን አባላት መካከል አንድ ሰው “ዱፌ” –መጣሁ ብሎ ስለሚመልስለት ነው፡፡ በሌላ አነጋገር ከአንደኛው ወገን ኮቱ (ስማ) ሲለው፣ ከሌላኛው ወገን ዱፌ (ሰማሁ) ብሎ መልስ የሚሰጥበትና በመጠራራት የውይይት ሒደት የሚጀመርበትን የማኅበራዊና የፍትሕ ሥርዓት አካሄድ ያሳያል፡፡ መሠረታዊው አነጋገር በነጠላ ቁጥር ኮቱ (ስማ) ይበል እንጂ አጠቃላይ የቃላት አጠቃቀሙ እንደ ብዛቱና ሁኔታው ይለያያል፡፡ ለምሳሌ የሲኮመንዶ አባገዳዎች በኦዳሮ ባባሌ ጊንር ላይ የሥልጣን ሽግግርና ርክክብ ባደረጉበት ወቅት የተጠቀሙት “ኮታ” – ስሙ በሚለው የብዙ ቁጥር ስያሜ አጠራር ነበር፡፡
ባህሪውና ትርጉሙ
በኮቱ ዱፌ የስብሰባ ሥርዓት በአባላቱ መሀል ጨርሶ የማይበላለጥ (እኩል የሆነ) ሥልጣንና መብት ሰፍኖ ይካሄድበታል፡፡ በአባላቱ መካከል ያለው በተፈጥሮ ችሎታ መበላለጥ እንደ ተፈጥሮነቱ ተከብሮ ይካሄዳል፡፡ ይህ በተፈጥሮ ችሎታ መበላለጥ በስብሰባው ውስጥ ነገሮችን ለማቃናት ተግባር ላይ ውሏል፡፡ ለምሳሌ “ገሞና” – ብልህ ሰው ከስብሰባው ውስጥ “መከላዎች” – የሐሳብ ግትሮች የሚፈጥሩትን ስህተት ያርማል፡፡
ኮቱ ዱፌ ያለ ሰብሳቢ የሚካሄድ ስብሰባ ነው፡፡ በስብሰባው አባላት መካከል የሥልጣን ልዩነት የለም፡፡ በችሎታና በእምነት የታገዘ ዕውቀት ይኖራል፡፡ ይኼ ደግሞ ከዋቃ (እግዚአብሔር) የተሰጠ ፀጋና በረከት ነው ተብሎም ይታመናል፡፡ ረዥም ጊዜ ውይይት የተካሄደበት ስብሰባው በተሰብሳቢ ሙሉ ድምፅ ብቻ ውሳኔ ያገኛል፡፡ በመሀል አንድ ሰው ብቻውን ቀርቶ ሲከራከር ቢገኝ የስብሰባው ውይይት በውሳኔ አይደመደምም፡፡ ይህ ማለት መቶ ሰው በስብሰባ ላይ ቢሳተፍ መቶዎቹም በአንድ ሐሳብ ላይ ሳይግባቡ ውሳኔ አይሰጥም ማለት ነው፡፡
ይህ ሁኔታ የሚያሳየውም በገዳ ሕግና ባህሉ ውስጥ የአንድ ብቸኛ ተከራካሪ መብት በጥብቅ እንደሚጠበቅ ነው፡፡ እስከነ ተረቱም ‹‹አንድ ብቻውን የሚከራከር ሰው ባለ ሁለት ዕድል ነው፡፡ ሁለት ዕድል ማለት በጥሩ ወይም በመጥፎው ሊጎዳ ይችላል ማለት ነው፡፡ አጠቃላይ የተቀመጠው መመርያ ‹‹ሰፉ/ያስኮንናል ወይም ያስቆጫል›› ይላል፡፡
የሰፉ ሥርዓት
ኦሮሞ የልቦና ሕግ ሥርዓት አለው። “ኦሮሞን ሰፉ ቀበ” ይባላል። ሰፉ የማይጣስ ነው። ያስኮንናል ሲል ምናልባት ተከራካሪ ብቻውን የሚከራከረው ግራ ገብቶት ጉዳዩን ያልተረዳ ሆኖ ይሆናል፡፡ የዚህን ጊዜ ይህን ደካማ ሰው በብዙኃን መመለስ ሲገባ “የት አባቱ” ብሎ መዝለፍ አሳዛኝና አስኮናኝ፣ በእግዚአብሔር ፊት የሚያስኮንን ነው ማለት ሲሆን፣ ደግሞ ተከራካሪ ከሁሉም ሰው በይበልጥ አውቆ ሲከራከርና እርሱ በግሉ ያወቀውን ሌሎች በብዙኃን አካትቶ ከእርሱ ጋር መከራከር ከፍተኛ ጥፋት ይሆንና ያስቆጫል የሚል ነው፡፡ ስለዚህም በኮቱ ዱፌ ሥርዓት ውስጥ ውይይቱ ተከራካሪ አልባ እስኪሆን ድረስ ሳይካሄድ ውሳኔ አይሰጥም፡፡
ስለዚህ የሚተላለፉት ውሳኔዎች ሁሉ ባለሙሉ ድምፅ ብቻ ናቸው፡፡ በየትኛውም ዓይነት የኮቱ ዱፌ ስብሰባ ላይ ተጀምሮ እስኪያበቃ ድረስ ውይይቱ በሙሉ እውነትን ምርመራና ፍለጋ ላይ ሲሾር ይቆያል፡፡ ማናቸውም የስብሰባው ንግግር ሁሉ በዚሁ ዙሪያ ያውጠነጥናሉ፡፡ ጠቅላላው ሥራ ራሱ እውነትን ፈልጎ አውጥቶ፣ መርምሮ አንጥሮ ለባለ እውነቱ መቸር ነው፡፡ ድብቅ እውነት በተከሰተበት ጊዜ ሁሉ በ“ሀቡለቱ” – ይደር ተብሎ በተለዋጭ ቀጠሮ ይዘጋል እንጂ፣ በየትኛውም ዓይነት መንፈስ ተቻኩሎ ውሳኔ ላይ አይደረስም፡፡ ከፍለጋው በኋላ እውነት በተገኘ ጊዜ የተገኘው እውነት ፈርጅ ይሰጠውና ለባለ እውነቱ ይሰጣል፡፡
ስብሰባው ፀብ (ግጭትን) በሚመረምርበት ጊዜ ለፀቡ ደረጃ ሰጥቶ ከፋፍሎ ያያል እንጂ ጨፍልቆ አይመለከትም፡፡ የግጭት አፈታት ሥርዓቱ እንደዚሁ ለግጭቶች/ፀቦች ፈርጅ ሳይሰጥ ወደ ዕርቅ ወይም መግባባት ሒደት አይገባም፡፡ ኮቱ ዱፌ የፀብ ዓይነቶችን ፀቦችን በዘርፍና በዓይነት፣ በደረጃ በመመደብ የሚያስተናግድ የስብሰባ ዓይነት ነው፡፡ ባለ አንድ አውታር ሁለት ግራና ቀኝ ተደራዳሪ ወገኖች የሚወያዩበት ሥርዓት ነው፡፡
እንዲሁም ባለ ሁለት አውታር ሦስት ወገኖች፣ ባለ ሦስት አውታር አራት ወገኖች አንድን ጉዳይ ለማየት የሚሳተፉበት፣ ባለአራት አውታር፣ አራትና ከዚያ በላይ ወገኖችም ጭምር የሚሳተፉበት የስብሰባ ሥርዓት አለው፡፡
ትዕይንታዊ እንቅስቃሴ
የኮቱ ዱፌ ስብሰባ ሲካሄድ ትዕይንታዊ (በድራማ ዓይነት) አካሄድ ይጠቀማል፡፡ እጅ ይወራጫል፣ ራስ ይነቀነቃል፣ አለንጋ ይዞራል/ይወናጨፋል፡፡ አፍ ያወራል/አንደበት ይናገራል፡፡ በአጠቃላይ ተናጋሪ ሁለ መናዊ መልዕክት ለማስተላለፍ ይናገርበታል፡፡ ኮቱ ዱፌ ሐሳብ ለመስጠት ወይም ጥያቄ ለመጠየቅ ጣት የማይቀሰርበት ስብሰባ ነው፡፡ አንድ ሰው ሐሳብ ለመስጠት ወይም ጥያቄ ለመጠየቅ ቢፈልግ “ናቀብ” (ያዝልኝ) የሚል ድምፅ ያሰማል፡፡ በዚሁ ድምፅ እንዲናገር ዕድል ይሰጠዋል እንጂ እጅ ማውጣት አያስፈልገውም፡፡ ሌላኛው “ሲቀቤ” ይዤልሃለሁ ሲል መናገሩን ያቆምና እንዲናገር ዕድል ይሰጠዋል፡፡ በዚሁ ሁኔታ ላይ የሰው ልዩነት ሳይደረግበት ለአዋቂም ለአላዋቂም እኩል መብት ይሰጠዋል፡፡ አባላት በስብሰባው ውስጥ ፍፁም እኩል የሆነ ዴሞክራሲያዊ መብት አላቸው፡፡ በማናቸውም የተፈጥሮ ሁኔታ መበላለጥ መናናቅ ሳይደረግ ሁሉም እንደፈለገው የኮቱ ዱፌ ሥርዓትን ተከትሎ በመጠቀም መናገር ይችላል፡፡
የኮቱ ዱፌ ስብሰባ በሐሳብ አሰጣጥ ላይ የራስ ሕግጋት አሉት፡፡ የአለባበስ፣ አቀማመጥ፣ የአለንጋ አያያዝና አቀማመጥ ሥርዓት አለው፡፡ ልብስ ተከናንቦ መናገር አይቻልም፡፡ የተለመደው የአለባበስ ሥርዓት መጠበቅ አለበት፡፡ በማንኛውም ሁኔታ ተኝቶ መናገር አይቻልም፡፡ እግርን ዘርግቶ ወይም አንፈራጥቶ መናገር ክልክል ነው፡፡ በአለንጋ አያያዝም ላይ የራስ ሕግና ሥርዓት አለው፡፡ ለምሳሌ በነጠላ አለንጋ ውሳኔ አይሰጥም፡፡ በቆራጣ አለንጋ ውሳኔ አይሰጥም፡፡ ተተብትቦ በታሰረ አለንጋ ውሳኔ አይሰጥም፡፡ ኮቱ ዱፌ ለየት ያለ የእውነት አሰጣጥም ሥርዓት አለው፡፡
እውነት በተገኘበት ሁኔታና ፍጥነት ሁሉ ይሰጣል፡፡ እውነት እንደ ተገኘ ሲባል በመጀመር ከተገኘ ወዲያው፣ በውይይቱ መሀል ላይም ከተገኘ በመሀል በመጨረሻም ላይ ከተገኘ በመጨረሻ ላይ ይሰጣል ማለት ነው፡፡ ስብሰባው ሁሉም ውሸትን እያጣጣለ እውነትን እየሰጠ ይጓዛል፡፡ በመሀል እውነት ከተገኘ “ጄቻን ዱጋአ” ለማለትህ ትክክል ነው ይላል፡፡ እውነት ላገኘው ሰው እውነት ለተሰጠውም ሰው “ዱጋት ቡሊ” በእውነት ተዳደር ይለዋል፡፡ እውነት ሰጪ በመሀል ውሸት ገብቶበታል ለማለት ሲፈልግ “ሃታኡ መሌ” (ይሁንና) ይልና ስህተቱን ይጠቁማል፡፡ ስህተቱን የጠቆመ ስህተት መሆኑን ከተረዳ “ገሌ” ተግባባን ሲል ስህተቱን ይቀበላል፡፡ እውነት ሰጪውም ‹‹አላ ነጋን ገላ›› – ከደጅ በሰላም ግቡ ሲል ይመልስለታል፡፡
በእንደዚሁ ዓይነት ሒደት እየተግባቡ ሲጓዙ ተናጋሪ እውነትን በተናገረ ጊዜ ሁሉ “ዱጋ” –እውነት ነው እያለ ተቀባዩ ይቀበለዋል፡፡ ያም መልሶ “ዱጋ ቁፋ” – ጠጥተው ይርኩ ሲል ይመልስለታል፡፡ እውነት ጣሽ የሆነ ነገር በመሀል ሲፈጠር “ዱጋን ሲዲዴ” – እውነት አይደለም፣ ትታገዳለህ ይለዋል፡፡ ኮቱ ዱፌ በእንደዚሁ ዓይነት ሁኔታ በእውነት አሰጣጥ ልዩ ሥነ ሥርዓት ውስጥ ራሱን እያስገባ እየጠበቀ የሚመራ ስብሰባ ነው፡፡
በኮቱ ዱፌ ሥነ ሥርዓት ውስጥ የአባላት አቀማመጥ የራሱ ሥርዓት አለው፡፡ ሰዎች እንዳስፈለጋቸው መቀመጥ አይችሉም፡፡ በማኔጅመንት በሳይንሱም በተመሳሳይ መልኩ ያለውን የሚከተል ነው፡፡ የተሰብሳቢዎቹ አቀማመጥ ሥርዓት በአባላት መካከል ያለውን የሥልጣን አልባነት በሚያሳይ መልክ መሆን አለበት፡፡ የሸንጎ ተሳታፊ አባላት አቀማመጡ ዙሪያ ክብ ሆኖ መቀመጫ ቦታው እንዳስፈላጊነቱ መሬት ላይ ነው፡፡ ከአልጋ ላይ ወይም ከወንበር ላይ እግርን አንጠልጥሎ መቀመጥም አይቻልም፡፡ ሁሉም ተሰብሳቢ መቀመጫውን መሬት አስነክቶ ይቀመጣል፡፡ እግርን አንፈራጥጦ ወይም ዘርግቶ መቀመጥ አይቻልም፡፡ በእግር ላይ ቁጥጥ ብሎ መቀመጥ አይፈቅድም፡፡ ይህ ሁሉ የሚሆነው በተሰብሳቢ አባላት መሀል ሰው ሠራሽ መበላለጥ እንዳይኖር ለመከልከል ነው፡፡ ትክክለኛ አቀማመጥ መቀመጫን መሬት አስነክቶ በጫማ እግር ሙሉ ለሙሉ መሬት ተቆጣጥሮ ጉልበትን ቆም አድርጎ ነው፡፡