በብርሃኑ ፈቃደ፣ ከሻርም ኤል ሼክ፣ ግብፅ
በኢትዮጵያ፣ በሱዳንና በግብፅ መካከል የልማት ሥራዎችን አብሮ ለማስኬድ የሚረዳ የጋራ የልማት ፈንድ ለመመሥረት መስማማታቸውን በግብፅ የኢትዮጵያ አምባሳደር ማህሙድ ድሪር ገለጹ፡፡
ግብፅ የካቲት 12 እና 13 ቀን 2008 ዓ.ም. ባካሄደችውና ‹‹አፍሪካ 2016፣ ቢዝነስ ለአፍሪካ፣ ለግብፅና ለመላው ዓለም›› በሚል ስያሜ በአፍሪካ ንግድና ኢንቨስትመንት ላይ ባተኮረው ስብሰባ ላይ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝን ጨምሮ፣ የሰባት አገሮች መሪዎች በሻርም ኤል ሼክ ከተማ ተገናኝተዋል፡፡ በተለይ በኢትዮጵያ፣ በሱዳንና በግብፅ መሪዎች መካከል በተደረገ የጎንዮሽ ውይይት ወቅት አዲስ ነጥብ ሆኖ የተነሳው የልማት ፈንድ የመመሥረት ሐሳብ መሆኑን አምባሳደር ማህሙድ ገልጸዋል፡፡
ሦስቱ አገሮች ወደ ፊት ዝርዝሩን የሚያወጡ መሆናቸውና በመሠረተ ሐሳብ ደረጃ ግን የጋራ ፈንድ መመሥረት እንደሚገባቸው ተነጋግረዋል ተብሏል፡፡ ‹‹በሦስቱ አገሮች የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች የሚመራ አካል ሒደቱን ወደፊት በጋራ የሚያየውና አተገባበሩን የሚወስን ይሆናል፤›› ያሉት አምባሳደር ማህሙድ፣ ሦስቱ አገሮች በጋራ አዋጥተው በሚመሠርቱት ፈንድ የልማት ሥራዎች የሚያከናውኑበት እንደሚሆን ጠቅሰዋል፡፡
ግብፅ ባስተናገደችውና በፕሬዚዳንት አብዱልፈታህ አልሲሲ ከፍተኛ ክትትል ዝግጅቱ ሲከናወን ቆይቶ በተጠናቀቀው ስብሰባ ላይ፣ በመሪዎች ደረጃ ከተደረገው ውይይት ውስጥ በተለይ በግብፅ በኩል ሦስቱን አገሮች የሚያገናኝና ከአዲስ አበባ በካርቱም አድርጎ ወደ ካይሮ የሚዘረጋ መንገድ ለመገንባት ፍላጎት እንዳላት የገለጸችበት አንዱ ነው፡፡
በአጠቃላይ ከዲፕሎማሲ አንፃር በሕዝብ ለሕዝብ መቀራረብ ላይ ያተኮረ የዲፕሎማሲ ሥራ ለመሥራት፣ የኢትዮጵያ ፍላጎትም ቀና መሆኑን ለማስገንዘብ እየተሠራ መሆኑን ያብራሩት አምባሳደር ማህሙድ፣ በመሪዎች ደረጃ ያለውን ግንኙነት ወደ ተቋማዊነት ለማምጣት በሁሉም ደረጃ መጠናከር የሚስፈልገው ተግባር መሆኑን አስታውቀዋል፡፡
በስብሰባው ላይ የኢትዮጵያ ከፍተኛ ልዑካንን በመምራት የተሳተፉት ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም፣ በአገሮች መካከል የርስ በእርስ ጥቅም ላይ ያተኮረና ሌላውን የማይጎዳ ልማት ማምጣት የኢትዮጵያ አካሄድ መሆኑን ሲያብራሩ፣ ከአንድ ዓመት በፊት የተፈረመውን የመርህ መገለጫ ድንጋጌን ጠቅሰዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በባቡር፣ በመንገድና በኃይል አቅርቦት ኢትዮጵያ ከጂቡቲ፣ ከኬንያ፣ ከሱዳንና ከሌሎች ጎረቤት አገሮች ጋር እየተሳሰረች መምጣቷን በስብሰባው ወቅት ጠቁመዋል፡፡ ‹‹ከዋሻው በስተመጨረሻ ብርሃን ማየት ጀምረናል፤›› በማለትም ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ትስስርና የጋራ ልማት ትልቁን ድርሻ መወጣት እንደጀመረች አስረድተዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ስለዓለም ኢኮኖሚ መቀዛቀዝና በኢትዮጵያ ላይ ስላስከተለው ተፅዕኖና መንግሥት ስትራቴጂካዊ ስለሚላቸው ዘርፎች መከፈት ከመድረክ ተጠይቀው ነበር፡፡ ምንም እንኳ የዓለም ኢኮኖሚ በአብዛኛው በነዳጅ ዋጋ መቀነስ ምክንያት በርካታ አገሮችን ቢፈታተንም፣ ኢትዮጵያ በተለይ በነዳጅ ዋጋ መቀነስ ምክንያት ጊዜያዊ ጠቀሜታ ማግኘቷን አስታውቀዋል፡፡ ይሁንና አገሪቱ በአብዛኛው ወደ ውጭ የምትልካቸው ምርቶች የግብርና ጥሬ ምርቶች በመሆናቸው፣ በዓለም ገበያ የሸቀጦች ዋጋ መውደቅ በአገሪቱ ወጪ ንግድ ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩን አብራርተዋል፡፡ ከዚህ ይልቅ መንግሥታቸው የኢኮኖሚውን መዋቅር ለመቀየር የቀየሳቸውን ዕቅዶችና የአምስት ዓመት አካሄዱን አብራርተዋል፡፡
እንደ ባንክ፣ ቴሌኮም፣ ወዘተ. ያሉት ዘርፎችን ለውጭ ኩባንያዎች ክፍት ስለማድረግ ተጠይቀው በተለይ ባንኮችን በሚመለከት፣ ‹‹ለአገር ውስጥ ተበዳሪዎች 60 በመቶውን ገንዘባቸውን እንዲያበድሩ ስንደራደር ብንቆይም ፈቃደኛ ሳይሆኑ ቀርተዋል፤›› በማለት የውጭ ባንኮች እንዳይገቡ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ አለበለዚያ የመወዳደር አቅማቸው ደካማ የሆኑት የአገር ውስጥ ባንኮች በውጮቹ ተውጠው ስለሚቀሩ አደጋ ያለው በመሆኑ፣ አቅማቸው እስኪጠናከር የውጭ ባንኮች እንዳይገቡ መደረጉን አስረድተዋል፡፡