Thursday, March 23, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊከ62 ሚሊዮን ብር በላይ መጠን ያለው የውጭ ምንዛሪ በማጭበርበር የተጠረጠሩ የውጭ ዜጐች...

ከ62 ሚሊዮን ብር በላይ መጠን ያለው የውጭ ምንዛሪ በማጭበርበር የተጠረጠሩ የውጭ ዜጐች ተከሰሱ

ቀን:

የፕላስቲክ ቱቦዎችንና መገጣጠሚያ ማሽነሪዎችን ለማስመጣትና በአገር ውስጥ ለመገጣጠም ከኢትዮጵያውያን ጋር ባለድርሻ በመሆን ያቋቋሙትን ኩባንያ መጠቀሚያ በማድረግ፣ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ኤልሲ ከፍተው ካገኙት የውጭ ምንዛሪ ውስጥ ከ62.2 ሚሊዮን ብር በላይ በውጭ ባንክ በመደበቅ የተጠረጠሩ ሁለት የውጭ ዜጐች ተከሰሱ፡፡

የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ክስ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ክስ የመሠረተባቸው ተጠርጣሪ ተከሳሾች፣ በትውልድ አሜሪካዊና በዜግነት ደቡብ አፍሪካዊ መሆናቸው የተገለጸው ሚስተር ማይክል ማትሰንርና እንዲሁም ግብፃዊ መሆናቸው የተገለጸው ሚስተር አይመን አብድል ሞተልብ ሙሳ ኢሳ መሆናቸው በክሱ ተገልጿል፡፡

ግለሰቦቹ የተከሰሱት በከባድ የማታለል ወንጀልና በሕገወጥ መንገድ የተገኘን ገንዘብ ሕጋዊ አስመስሎ ማቅረብ ወንጀል መሆኑንም ክሱ ይጠቁማል፡፡

ተከሳሾቹ ድርጊቱን እንዴት እንደፈጸሙት ዓቃቤ ሕግ በክሱ እንደገለጸው፣ ኢትዮጵያውያንና ግብፃዊው ሚስተር አይመን በጋራ ባቋቋሙት ስታር ፓይፕና ፊቲንግስ ኩባንያ ውስጥ፣ ሚስተር ማትሰን ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው ይቀጠራሉ፡፡ ሚስተር አይመን ለብቻቸው ያቋቋሙት ጎልደን ትሬዲንግ ከሚባለው ኩባንያ በተጨማሪ ከሚስተር ማትሰን ጋር በጋራ ያቋቋሙት በዱባይ የሚገኝ ዋሶ ቴክኖሎጂ ግሩፕ የሚባል ኩባንያ አላቸው፡፡ በመሆኑም ተከሳሾቹ ከህንድና ከቻይና ወደ አገር ውስጥ እንደሚያስገቡ የገለጹትን የፕላስቲክ ቱቦና መገጣጠሚያ ማሽነሪዎችን፣ በኢትዮጵያ ንግድ መርከብ ለማጓጓዝ የተለያየ መጠን ያለው ዶላር ለማስጫኛ በመክፈል ዕቃዎቹን እንዳስገቡ መግለጻቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡

ተከሳሾቹ ከቻይናና ከህንድ ከ2004 ዓ.ም. እስከ 2005 ዓ.ም. ድረስ በኢትዮጵያ ንግድ መርከብ እያስጫኑ ዕቃውን ሲያስገቡ፣ ለማስጫኛ ያልተከፈለውን የገንዘብ መጠን፣ በሐሰተኛ የማስጫኛ ደረሰኝና የንግድ ሽያጭ ደረሰኝና በሐሰተኛ ማኅተም ተጠቅመው ወንጀሉን እንደፈጸሙ የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡

ተከሳሾቹ በቻይና የኢትዮጵያ ንግድ መርከብ ወኪል የሆነው ‹‹የቻይና የውቅያኖስ አጓጓዥ ኤጀንሲ ሻንጋይ›› የሚል ሐሰተኛ የጭነት ደረሰኝ በማዘጋጀት፣ ‹‹የመጫኛ መነሻ ወደብ ሻንጋይ ቻይና፣ ጭነት ማራገፊያ ጂቡቲ የባህር ወደብ፣ መድረሻ ሞጆ ደረቅ ወደብና አጓጓዥ የኢትዮጵያ ንግድ መርከብ›› የሚል ሐሰተኛ ሰነድ አዘጋጅተው የተለያየ መጠን ያለው ዶላር እንደተከፈለ በማስመሰል፣ ጠቅላላ ድምሩ 62,278,179 ብር ዱባይ ሚስተር ማይክልና ሚስተር አይመን በጋራ በዱባይ ማሽሩክ ባንክ በከፈቱት ‹‹ዋሶ ቴክኖሎጂ ግሩፕ›› ተብሎ በሚጠራው ድርጅታቸው አካውንት ውስጥ እንዲገባ ማድረጋቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡

ተከሳሾቹ የተጠቀሰውን ያህል ገንዘብ ዱባይ በሚገኘው የድርጅታቸው አካውንት ማሽሩክ ባንክ ያስገቡት፣ ለምሳሌ ዕቃውን ያስጫኑት በ19,000 ዶላር ከሆነ ኤልሲ ከፍተው የውጭ ምንዛሪ ከጠየቁት የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቃሊቲ ቅርንጫፍ በሚያቀርቡት ሐሰተኛ ሰነድ 40,000 ዶላር እየተቀበሉ፣ ልዩነቱን ለግላቸው ማድረጋቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡

ቻይናና ህንድ ውስጥ ላለው ስታር ፓይፕና ፊቲንግስ ፋብሪካ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ሲላክ ‹‹የተመረተበት አገር ቻይና፣ ለማሽነሪው ለአንዱ ብቻ የተከፈለ 385,370 ዶላር›› በማለትና ትክክለኛ ምርት ለማስመሰል ‹‹በስቴት ኦፍ ቴክሳስ ንግድ ምክር ቤት የተረጋገጠ›› የሚል ሐሰተኛ ሰነድ ማኅተም ተደርጐበት እንደቀረበ ክሱ ይገልጻል፡፡

በስቴት ኦፍ ቴክሳስ ንግድ ምክር ቤት በተመዘገበው የቻይና ኩባንያ የተመረተ እውነተኛ ምርት ለማስመሰል፣ ተከሳሾቹ ዋሶ ቴክኖሎጂ ግሩፕ ፕሮፎርማ ሰብስቦ እንዳረጋገጠ የሚያሳይ የንግድ ደረሰኝ በማቅረብ፣ እውነተኛ አስመስለው በሐሰተኛ ሰነድ እየተገለገሉ፣ ከዘጠኝ ጊዜያት በላይ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የውጭ ምንዛሪ በመውሰድ የተጠቀሰውን ገንዘብ ዱባይ ወደሚገኘው አካውንታቸው ለማሸሽ መቻላቸውን ክሱ ያብራራል፡፡

ተከሳሾቹ ‹‹ለኢትዮጵያ ንግድ መርከብ በቻይና ውቅያኖስ ጉዞ ኤጀንሲ የተከፈለ የውጭ ምንዛሪ›› በማለት በሐሰት ባዘጋጁት የተለያየ ሰነድ ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ያወጡትን የውጭ ምንዛሪ፣ ወደ ዱባይ ማሽሩክ ባንክ በመላክ ከባድ የማታለል ወንጀል መፈጸማቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡

ሚስተር ማትሰን በቁጥጥር ሥር ሲሆን፣ በዋስትናው ላይ ብይን ለመስጠትና የክሱን ሒደት ለማስቀጠል ለኅዳር 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ተቀጥሯል፡፡ ሚስተር አይመን ሊገኙ ባለመቻላቸው በጋዜጣ ጥሪ እንዲደረግላቸው ትዕዛዝ ተሰጥቶ ለመጠባበቅ ለታኅሳስ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

ከሁለቱ የውጭ ዜጎች ጋር ክስ የተመሠረተባቸውና በ100,000 ብር ዋስ በውጭ ሆነው ክሳቸውን እንዲከታተሉ ትዕዛዝ የተሰጠባቸው ደግሞ አቶ ወሰንዓለም ገብረ እግዚአብሔር ይባላሉ፡፡

አቶ ወሰንዓለም የተጠረጠሩት ሚስተር ማትሰን የስታር ፓይፕና ፊቲንግስ ሥራ አስኪያጅ ሆነው ሳሉ፣ ከድርጅቱ መተዳደሪያ ደንብ ውጪ ድርጅቱ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ቃሊቲ ቅርንጫፍ ካስቀመጠው ገንዘብ ውስጥ፣ ሦስት ሚሊዮን ብር ‹‹ለሚመለከተው ሁሉ›› ተብሎ በተሰጣቸው ውክልና በድርጅቱ ስም በማውጣታቸው መሆኑን ክሱ ያብራራል፡፡ በዋና ወንጀል አድራጊነት በፈጸሙት በሌላ ሰው ጥቅም ላይ የሥራ አመራር ጉዳት ማድረስ ወንጀል መከሰሳቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያብራራል፡፡     

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...