‹‹የምግብ ዕርዳታ በወቅቱ ካልቀረበ ኢትዮጵያ ያስጠለለቻቸው 730 ሺሕ ስደተኞች ለረሃብ ይጋለጣሉ››
የስደተኞች ጉዳይ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ አያሌው አወቀ፣ እስከ ታኅሳስ መጨረሻ ድረስ ለስደተኞች የሚያስፈልገው 55 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጣ የምግብ ዕርዳታ አቅርቦትን አስመልክቶ ከሰጡት መግለጫ የተወሰደ፡፡ አሜሪካ የሰጠችው 20 ሚሊዮን ዶላር ጥቅም ላይ እንደሚውል ገልጸው፣ የሚፈለገው ዕርዳታ ካልደረሰ ግን ‘ከፍተኛ ቀውስ’ ይፈጠራል ማለታቸውን የተለያዩ ሚዲያዎች ዘግበዋል፡፡ በአፍሪካ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ስደተኞች በማስተናገድ ላይ ያለችው ኢትዮጵያ፣ በ30 ዓመታት ውስጥ ታይቶ የማይታወቅ ድርቅ የገጠማት በመሆኑ ምክንያት 8.2 ሚሊዮን ዜጐቿ ዕርዳታ ፈላጊ ናቸው፡፡ ይኼ የተረጂዎች ቁጥር ይጨምራል ተብሎም ይጠበቃል፡፡ በደቡብ ሱዳን የተፈጠረው ችግር የስደተኞችን ቁጥር በመጨመር፣ በኢትዮጵያ የምግብ ዋስትና ላይ ጫና መፍጠሩ ይወሳል፡፡ እነዚህ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች በተጠለሉባቸው አካባቢዎች ከአገሬው ሰው ጋር ጎን ለጎን መኖራቸውም ለችግሩ መባባስ ምክንያት ነው ተብሏል፡፡ በምሥሉ ላይ የሚታዩት ኢትዮጵያ ውስጥ የሚኖሩ የደቡብ ሱዳን ስደተኞች ናቸው፡፡