በሽብር ድርጊት ወንጀል ክስ ተመሥርቶባቸው ዓቃቤ ሕግ የሰውና የሰነድ ማስረጃዎችን ካቀረበባቸው በኋላ መከላከል ሳያስፈልጋቸው በነፃ የተሰናበቱት የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች፣ ዓቃቤ ሕግ ያቀረበባቸው ይግባኝ ተመርምሮ እንደሚያስቀርብና እንደማያስቀርብ ለመንገር በድጋሚ ተቀጠሩ፡፡
የሥር ፍርድ ቤት ውሳኔን በመቃወም የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ያቀረበውን ይግባኝ ተከትሎ ውሳኔው እንዳይፈጸም ዕግድ የሰጠው የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ ጥቅምት 22 ቀን 2008 ዓ.ም. የውሳኔ መዝገቡን መርምሮ ዓቃቤ ሕግ ባቀረበው የይግባኝ አቤቱታ ላይ ‹‹ያስቀርባል ወይም አያስቀርብም›› ብሎ ብይን ለመስጠት ቀጠሮ ሰጥቶ የነበረ ቢሆንም፣ ዓቃቤ ሕግ የተቃወመው የሥር ፍርድ ቤት የውሳኔ መዝገብ እንዳልቀረበለት ገልጿል፡፡ በመሆኑም ውሳኔውና ዝርዝር ማስረጃዎቹ ተያይዘው እንዲቀርቡለት ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በዕለቱ ይግባኝ የተጠየቀባቸው የአንድነት አመራር የነበሩት አቶ ሀብታሙ አያሌውና አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የአረና ፓርቲ አመራር የነበሩት አቶ አብረሃ ደስታና የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የነበሩት አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ እንዲሁም አብረዋቸው ይግባኝ የተባለባቸው አቶ አብረሃም ሰለሞን በችሎት አልተገኙም፡፡ ፍርድ ቤቱ በችሎት በሰጠው ትዕዛዝ መዝገቡን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለጥቅምት 29 ቀን 2008 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡