የጥንታዊት ኢትዮጵያ ጀግኖች አርበኞች ማኅበር ፕሬዚዳንት የነበሩት ሊቀ ትጉሃን አስታጥቄ አባተ፣ በማታለል ወንጀል ተጠርጥረው ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
ክሱ ቀደም ብሎ በ1998 ዓ.ም. ተመሥርቶባቸው የነበረ ቢሆንም፣ እንዲቋረጥ ተደርጎ ከቆየ በኋላ የፍትሕ ሚኒስትር ዴኤታ በነበሩት አቶ ልዑል ወልዱ (አሁን የትግራይ ክልል ፍትሕ ቢሮ ኃላፊ ሆነው ተሹመዋል) ትዕዛዝ ተቋርጦ የነበረው ክሱ እንዲቀጥል ተደርጓል፡፡
ተከሳሹ የተጠረጠሩበት የማታለል ወንጀል ‹‹አርበኛ ሳይሆኑ አርበኛ ነኝ›› በማለት፣ የማይገባ ጥቅም ለማግኘት በማሰብ የተሳሳተ መረጃና ማስረጃ አቅርበዋል የሚል መሆኑን የዓቃቤ ሕግ ክስ ይገልጻል፡፡
ተከሳሹ በ1938 ዓ.ም. ቢወለዱም በ1922 ዓ.ም. እንደተወለዱ፣ ጣሊያን ከ1928 ዓ.ም. እስከ 1933 ዓ.ም. ድረስ ኢትዮጵያን በወረረበት ጊዜ መሳተፋቸውንና ‹‹አርበኛ ነኝ›› ማለታቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡
ሊቀ ትጉሃን አስታጥቄ አርበኛ ሳይሆኑ እንደሆኑ በመግለጽና አሳሳች ነገሮችን በመናገር የራሳቸውን ማንነት መደበቃቸውን የሚገልጸው የዓቃቤ ሕግ ክስ፣ በ1937 ዓ.ም. በወጣው አዋጅ ቁጥር 4/1937 አንቀጽ 33 ላይ በተደነገገው መሠረት አርበኝነታቸውን እንዳስመሰከሩ መናገራቸውንም ክሱ ያስረዳል፡፡ በመሆኑም ከግንቦት 25 ቀን 1993 ዓ.ም. እስከ 1994 ዓ.ም. ድረስ የኢትዮጵያ አርበኞች ማኅበር ምክትል ፕሬዚዳንት በመሆን የአንድ ሺሕ ብር ደመወዝተኛ ሆነው መሥራታቸውን ክሱ ይጠቁማል፡፡ ከ1998 ዓ.ም. ጀምሮ ደግሞ ፕሬዚዳንት በመሆን 4,000 ብር ደመወዝና የተለያዩ ጥቅማ ጥቅሞችን እያገኙ በመሆኑ፣ በፈጸሙት የማታለል ወንጀል መከሰሳቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡ ኅዳር 2 ቀን 2008 ዓ.ም. ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ መጥሪያ እንደተላከላቸውም ለማወቅ ተችሏል፡፡