– ዓቃቤ ሕግ ክስ እንዲመሠርት ቀን ተቆርጦለታል
ሥልጣናቸውን ያላግባብ በመጠቀም ከፍተኛ የሆነ ጉቦ በመቀበል አገራዊ ጠቀሜታ ያላቸውን ከቀረጥ ነፃ ተሽከርካሪዎችን በማስገባት፣ በዘመዶቻቸውና በጓደኞቻቸው ስም ሀብት በማስቀመጥ፣ እንዲሁም ለመንግሥት መግባት የነበረበትን ታክስና ቀረጥ ለግላቸው በማድረግ ከባድ የሙስና ወንጀል የተጠረጠሩት አቶ ወንድሙ ቢራቱ፣ ማረሚያ ቤት እንዲወርዱ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰጠ፡፡
ፍርድ ቤቱ ትዕዛዙን የሰጠው፣ በተጠርጣሪው ላይ የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን ምርመራውን ማጠናቀቁን ካስታወቀ በኋላ ነው፡፡ ቡድኑ ምርመራውን ጨርሶ ለዓቃቤ ሕግ ማስተላለፉን ገልጾ፣ ዓቃቤ ሕግ አቶ ወንድሙን ጨምሮ በአራት ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ ለመመሥረት የሚያስችለውን በወ/መ/ሕ/ሥ/ሥ/ቁ 109 (1) መሠረት የ15 ቀናት ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡
የአቶ ወንድሙ ጠበቃ የተጠየቀውን ጊዜ በመቃወም፣ ደንበኛቸው ዋስትና እንዲፈቀድላቸው ጠይቀው ነበር፡፡ ዓቃቤ ሕግ ተጠርጣሪውን ዋስትና በሚያስከለክል ወይም በማይከለክል አንቀጽ ስለመክሰሱ ማወቅ እንደማይቻል ፍርድ ቤቱ ገልጾ፣ የዋስትናውን ጥያቄ ውድቅ በማድረግ በማረሚያ ቤት እንዲቆዩ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡
በመሆኑም ዓቃቤ ሕግ በአቶ ወንድሙና በሦስት ተጠርጣሪዎች ላይ ጥቅምት 19 ቀን 2008 ዓ.ም. ክስ እንዲያቀርብ ታዟል፡፡