Thursday, March 23, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ ለተሿሚዎች መኖሪያ ቤት ማቅረብ ተቸግሯል

የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ ለተሿሚዎች መኖሪያ ቤት ማቅረብ ተቸግሯል

ቀን:

የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ በተለይ ሰሞኑን ለተሾሙ ሚኒስትሮችና የተወካዮች ምክር ቤት አባላትን ጨምሮ፣ ከምክትል ዋና ዳይሬክተር በላይ ሹመት በሚሰጣቸው የመንግሥት ተሿሚዎች የሚሰጠው በቂ ቤት እንደሌለው አስታወቀ፡፡

በሌላ በኩል ላለፉት 24 ዓመታት አዳዲስ መኖርያ ቤቶችን እንዳይገነባ የተደረገው የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ፣ ለተሿሚዎች የሚያቀርበው መኖርያ ቤት በማጣቱ ነባር ነዋሪዎችን ለማስለቀቅ መዘጋጀቱን ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ የተቋሙ ከፍተኛ ባለሙያ ገለጹ፡፡

ከ600 በላይ የመንግሥት ተሿሚዎች የመኖርያ ቤት ጥያቄ አቅርበው ምላሽ እየተጠባበቁ ቢሆንም፣ ኤጀንሲው ለተሿሚዎች የሚያቀርበው መኖርያ ቤት በማጣቱ ሦስት አማራጭን ለከተማ ልማትና ቤቶች ሚኒስቴር አቅርቧል፡፡

የመጀመርያው አማራጭ ለዘመናት በኪራይ ቤት ውስጥ ይኖሩ የነበሩ ግለሰቦችን ማፈናቀል ነው፡፡ ሁለተኛው አማራጭ በቤት ልማት ፕሮግራሞች እየተገነቡ ያሉ ኮንዶሚኒየሞችና ከግለሰቦች ደግሞ ሪል ስቴት ቤቶችን መግዛት ነው፡፡ ሦስተኛው አማራጭ በራሱ አቅምና በጀት መኖርያ ቤቶችን መገንባት የሚሉት መሆናቸው ታውቋል፡፡

ነገር ግን የተሿሚዎቹ የመኖርያ ቤት ፍላጎት አጣዳፊ በመሆኑና የመኖርያ ቤት ግዢም ሆነ ግንባታ አማራጮች ወቅታዊ ምላሽ ለመስጠት የማያስችሉ በመሆናቸው፣ ኤጀንሲው ትኩረቱን ተከራዮችን ማፈናቀል ላይ ማድረጉ እየተነገረ መሆኑን ጥቅምት 2 ቀን 2008 ዓ.ም. በግዮን ሆቴል በተደረገ ስብሰባ ላይ የተገኙ ተሳታፊዎች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

ኤጀንሲው ‹‹የተሻሻለው የቤቶች አስተዳደር በግል ርዕስ ባወጣው መመርያ ቁጥር 41/2007 አንቀጽ 3 ለመንግሥት ተሿሚዎች (ብቻ) ቤቶች እንደሚሰጥ አስቀምጧል፡፡ ከእነዚህ ውስጥም ለፌዴራል መንግሥት፣ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት፣ ከኃላፊነት ለሚነሱ ባለሥልጣናት መኖርያ ቤት ይሰጣል ይላል፡፡ በመመርያው ለነዋሪዎች መኖርያ ቤት እንደሚሰጥ የሚገለጽ አንቀጽ አልተቀመጠም፡፡

በዚህ መሠረት ከመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ በግለሰብ ደረጃ ቤት መከራየት የሚታሰብ አለመሆኑን በርካታ ነዋሪዎች እየተናገሩ ነው፡፡ ከዚህ ባሻገርም የኤጀንሲው ነባር ተከራዮች የመፈናቀል አደጋ እያንጃበበብን ነው በማለት ሥጋታቸውን እየገለጹ ይገኛሉ፡፡

በአሁኑ ወቅት ይህ አደጋ ሊያንዣብብ የቻለው ለመንግሥት ባለሥልጣናት አዲስ ሹመት ከመሰጠቱ በተጨማሪ፣ ለአምስት ዓመታት ያገለገሉ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት የሥራ ጊዜያቸውን ጨርሰው በአዲስ መተካታቸው ነው፡፡ ይህ ሁኔታ አሳሳቢ ሊሆን የቻለው በርካታ አዳዲስ ተሿሚዎች የመኖርያ ቤት ጥያቄ እያቀረቡ ሲሆን፣ ከነባሮቹ የፓርላማ ነዋሪዎች መኖርያ ቤቶች ውስጥ 155 የሚሆኑት አገልግሎት ለመስጠት የማይችሉ በመሆናቸው ልዋጭ ያስፈልጋል በመባሉ ነው፡፡

ይህ ጉዳይ ገኖ ባይወጣም የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ በ2008 የሥራ ዕቅድ ላይ ከተከራይ ደንበኞቹና ከባለድርሻ አካላት ጋር ጥቅምት 2 ቀን 2008 ዓ.ም. በግዮን ሆቴል ባደረገው ውይይት በተወሰነ ደረጃ ተነስቷል፡፡

ውይይቱን በንግግር የከፈቱት የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ኃይለ ማርያም ዓለም ሰገድ፣ ‹‹የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ ከዚህ በኋላ ቤት የሚያቀርበው ለመንግሥት ተሿሚዎች ብቻ ነው፤›› ካሉ በኋላ፣ ኤጀንሲው 17 ሺሕ ቤቶችን እንደሚያስተዳድር ገልጸዋል፡፡ ከእነዚህ ቤቶች ውስጥ የሲኤምሲ አፓርታማዎችን ጨምሮ የተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች የሚኖሩባቸው 141 አፓርትመንቶች ሲኖሩት፣ እነዚህ አፓርትመንቶች 5,294 ቤቶች አሏቸው፡፡ ኤጀንሲው እነዚህን አፓርትመንቶች ለማስተዳደር አዲስ መመርያ ማዘጋጀቱን አቶ ኃይለ ማርያም አስታውቀዋል፡፡

የአፓርትመንት አስተዳደር፣ አጠቃቀምና አጠባበቅ ረቂቅ መመርያ ላይ፣ በኤጀንሲው ደንበኞች በተቋቋሙ የአፓርታማ ነዋሪዎች ማኅበራት ተወክለው ከተገኙና ከተለያዩ አካላት ከተወከሉ ባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት ተደርጓል፡፡

ተከራዮች የተከራዩትን ቤት እንዴት መያዝ እንዳለባቸው ማለትም የንፅህና አጠባበቅ፣ በየሕንፃዎቹ ላይ የተከራዩ ደንበኞች አንዱ የሌላውን መብት ሳይነካ የሕንፃውን ደኅንነት ጠብቀው መኖር እንዳለባቸውና ችግር የሚፈጥር ካለ ቤቱን እስከማስለቀቅ የሚደርስ ቅጣት እንደሚጣልበት በዝርዝር በረቂቅ መመርያው ተካተዋል፡፡

ኤጀንሲው፣ ‹‹የደንበኞቼን ደኅንነት ለመጠበቅ የቤቴን ደኅንነት መጠበቅ ግዴታ አለብኝ›› በማለት የሕንፃዎቹን ውበትና ንፅህና ለመጠበቅ ያዘጋጀውን ረቂቅ መመርያ ለተወያዩ ካስተዋወቀ በኋላ፣ መድረኩን ለተሳታፊዎች ክፍት አድርጓል፡፡

የውይይቱ ተሳታፊዎች የመመርያው መዘጋጀት ጥሩ መሆኑን በጥቅሉ ከተናገሩ በኋላ ትኩረት የሰጡት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ፣ ‹‹የመንግሥት ቤቶች ኤጀንሲ ከዚህ በኋላ የሚሠራው ለመንግሥት ተሿሚ ኃላፊዎች ብቻ ነው፤›› ለሚለው ጉዳይ ነው፡፡ ‹‹ቤት የምንሰጠው ለመንግሥት ባለሥልጣናት ብቻ ነው መባሉ ያሠጋናል፡፡ እናንተ ከቤታችን ልትወጡ ነው የሚል አባባል ይመስላል፤›› ያሉት ተሳታፊዎቹ ምን ማለት እንደሆነ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ጠይቀው፣ ኤጀንሲው ልብ ሊል የሚገባው የቤት ተከራዮች ታክስ እየከፈሉ አገልግሎት ማግኘት እንዳለባቸው አሳስበዋል፡፡

ኤጀንሲው ተከራዮችን ሊያዳምጥና ያለባቸው ችግርም ሊመለከት እንደሚገባ ተናግረው፣ ፅዳትንና ዕድሳትን በሚመለከት በረቂቅ መመርያው ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ መቀመጡ ተገቢ በመሆኑ፣ ከኤጀንሲው ጋር ተባብረው ለመሥራት ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

አንዳንዶቹ ሕንፃዎች ለተለያዩ አገልግሎቶች እየዋሉ በመሆናቸው፣ ኤጀንሲው በጥቃቅን ሥራዎች ላይ ማተኮሩን ተወት አድርጎ የትኛው ሕንፃ ለንግድ፣ የትኛው ለመኖሪያና ለቢሮ መዋል እንዳለበት በመለያየት ሥርዓት እንዲያሲዝላቸው ጠይቀዋል፡፡ ኤጀንሲው ከደንበኞቹ በሚቀርቡለት ጥያቄዎች ላይ ተገቢና አፋጣኝ ምላሽ እንደማይሰጥ የተናገሩት የውይይቱ ተካፋዮች፣ በምርኩዝ የሚሄዱ ጥበቃዎችን ቀጥሮ ሁሉም ነገር የተሟላለት ሕንፃ እንዳከራየ አድርጎ የሚናገረው ተገቢ እንዳልሆነ አስረድተዋል፡፡

በውይይቱ ተሳታፊዎች ለተነሱት ጥያቄዎችና አስተያየቶች ምላሽ የሰጡት የኤጀንሲው የተለያዩ ክፍሎች ኃላፊዎች እንደገለጹት፣ ቤቶች ለመንግሥት ተሿሚዎች ይሰጣሉ ማለት፣ ነባር ተከራዮች ይፈናቀላሉ ማለት አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡ በአንድ አፓርትመንት ውስጥ ብዙ ተከራዮች ስላሉ፣ ወደ ሕንፃዎቹ ማን እንደሚገባ፣ ማን እንደሚወጣና ማን ነዋሪ እንደሆነ ለይቶ ለማወቅ፣ እንደሁም በዓለም ደረጃ ሥጋት እየፈጠሩ ያሉ አንዳንድ ችግሮች በዚህም እንዳይከሰቱ የደንበኞቹንም ደኅንነት ለመጠበቅ ጭምር መሆኑን፣ የኤጀንሲው ምክትል ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋዬ ይገዙ አስረድተዋል፡፡

ኤጀንሲው ያስጨነቀው የደንበኞቹን ደኅንነት እንዴት መጠበቅ እንዳለበት መሆኑን የሚያሳየው ለ40 ዓመታት በነበረው የኪራይ ተመን አከራይቶ እንደሚገኝ ገልጸው፣ ደንበኞች የሕንፃዎችን ደኅነነት ጠብቀው እንዲኖሩና በአብዛኛው መታደስ ያለባቸው ሕንፃዎች ስላሉ ተባብሮ ለማደስ እንዲቻል ለማድረግ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ዝቅ ባለ የኪራይ ዋጋ የተከራየ ደንበኛ የቤቱን፣ የግቢውንና የአካባቢውን ንፅህና መጠበቅ እንዳለበትም አክለዋል፡፡

ለዜጎች ነፃነት ለመታገል ከመኖሪያ ቤታቸው ወደ ትግል ቦታ ወጥተው የነበሩ ታጋዮች በመንገድና በቱቦ ሥር እየኖሩ ባለበት ሁኔታ፣ በአራትና በስድስት ብር የተከራዩ የኤጀንሲው ደንበኞች የቤቱን ንፅህና አለመጠበቃቸው አሳዛኝ መሆኑን የገለጹት ምክትል ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ኃይለ ማርያም፣ ከኤጀንሲው ባከራዩት ቤት አሥር ሕንፃ የሚያስገነባ ሀብት ያገኙ ነጋዴዎች አንድ ጋሎን ቀለም መግዛት አቅቷቸው ሕንፃው ቆሽሾ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡

ታምሩ ጽጌ እና ውድነህ ዘነበ

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...