Thursday, March 23, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናየጋምቤላን ክልል ለመገንጠል ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል የተባሉ ተጠርጣሪዎች ተከሰሱ

የጋምቤላን ክልል ለመገንጠል ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል የተባሉ ተጠርጣሪዎች ተከሰሱ

ቀን:

– በቁጥጥር ሥር የዋሉት ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ነው

የጋምቤላ ሕዝቦች ነፃነት ንቅናቄ (ጋሕነን) ተብሎ በሚጠራው የሽብር ቡድን ውስጥ አባል ከሆኑትና በካናዳ፣ በእንግሊዝ፣ በኤርትራና በተለያዩ አገሮች ከሚገኙ አባላት ጋር ግንኙነት በመፍጠር፣ የጋምቤላን ክልልን ለመገንጠል ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል የተባሉ ሦስት ተጠርጣሪዎች ጳጉሜን 2 ቀን 2007 ዓ.ም. ተከሰሱ፡፡

የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ተረኛ ችሎት ክስ የመሠረተባቸው ተጠርጣሪዎች ኦሞት አጉዋ ኦክዋይ፣ አሽኔ አስቲን ቲቶይክና ጀማል ዑመር ሆጃሌ የሚባሉ ናቸው፡፡ በቁጥጥር ሥር የዋሉት ከስድስት ወራት በፊት የሽብር ቡድን የተባለው ጋሕነን ኬንያ ናይሮቢ በሚያካሂደው ስብሰባ ላይ ለመካፈል ሲሄዱ፣ መጋቢት 6 ቀን 2007 ዓ.ም. ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ መሆኑን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡

አንደኛው ተከሳሽ ኦሞት አጉዋ ኦክዋይ ከ1996 ዓ.ም. ጀምሮ ‹‹የጋምቤላን ክልል ከፌዴሬሽኑ መገንጠል›› የሚል ፖለቲካዊ ግብ በማስቀመጥ፣ ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለማፈራረስ የአገር ውስጥ አስተባባሪ በመሆን ሲንቀሳቀስ እንደነበር በክሱ ተገልጿል፡፡ የሽብር ቡድኑ ከፍተኛ አመራር ከሆነውና በደቡብ ሱዳን ከሚገኘው ኡቺች ከሚባለው ግለሰብ ጋር ግንኙነት በመፍጠር፣ ኤርትራ ውስጥ ወታደራዊ ሥልጠና የወሰዱ አባላትን ወደ ጋምቤላ እንዲልክለት በማድረግ፣ የሽብር ቡድኑን ተልዕኮ እንዲያስፈጽሙ በጋምቤላ ልዩ የፖሊስ አባላት ውስጥ እንዲቀጠሩ ማድረጉንም አክሏል፡፡

ተከሳሹ በጋምቤላ ከተማ ውስጥም የቡድኑን አባላት በመሰብሰብና አመራር በመስጠት፣ እንግሊዝ ለንደን ውስጥ ከሚኖረውና ከፍተኛ አመራር ከሆነው ኝኬው አቡላ ከሚባል ግለሰብ ጋር በኢሜል በመገናኘት የአባላቱ ቁጥር እንዲጨምር መጠየቁን ክሱ ያስረዳል፡፡ ኝኬው አቦላ በውጭ አገር የሚገኙ ጋዜጠኞች አኝዋክ ዞን ሄደው መረጃ እንዳይሰበስቡ የኢትዮጵያ መንግሥት የከለከለ መሆኑን ለኦሞት ገልጾለት ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ አምስት ሰዎች፣ ከጋምቤላ አኝዋክ ዞን የቡድኑ አባላት፣ ከደቡብ ኦሞ አሥር ሰዎችን መልምሎ ኬንያ በሚደረገው የቡድኑ ስብሰባ ላይ እንዲሳተፉ እንዲያደረግ ባዘዘው መሠረት፣ መልዕክት በማስተላለፍና በማደራጀት ተግባር ላይ መሳተፉን ክሱ ያብራራል፡፡ ለሽብር ተግባር ማስፈጸሚያ 3,000 የእንግሊዝ ፓውንድ የተላከለት መሆኑንም አክሏል፡፡

ሁለተኛው ተከሳሽ አሜሪካ ሚኒሶታ ግዛት ውስጥ በሚኖረው የሽብር ቡድኑ ከፍተኛ አመራር በሆነውና በቅጽል ስሙ ኡጆ በሚባለው ግለሰብ አማካይነት በ2006 ዓ.ም. የሽብር ቡድኑ አባል ሆኖ መመልመሉን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡ ከዚያም እንግሊዝ አገር ከሚኖረው የሽብር ቡድኑ አባል ኝኬው አቡላ ጋር በኢሜል በመገናኘት፣ ‹‹የጋምቤላን ክልል ከሌሎች የኢትዮጵያ ክልሎች በመገንጠል ራሱን የቻለ ሉአላዊነት አገር መመሥረት›› በሚለው ሐሳቡ ተስማምቶ፣ በማጃንግ ዞን የሚኖሩ የማጃንግ ብሔርና ደገኞች መካከል በተፈጠረው አለመግባባት፣ የማጃንግ ብሔሮች ተጐድተው እያለ፣ መንግሥት ዕርምጃ የወሰደው በማጃንግ ከፍተኛ አመራሮችና በጋምቤላ ክልል የልዩ ኃይል ፖሊስ ላይ ብቻ እንደሆነ በመግለጽ፣ ሐሰተኛ መረጃ ለሽብር ቡድኑ ያቀብል እንደነበር በክሱ ተብራርቷል፡፡

ተከሳሹ የአገር ውስጥ ከፍተኛ አመራር ከሆነው አንደኛ ተከሳሽ ኦሞት ጋር በስልክ ግንኙነት በማድረግ ቀኑ በትክክል ባልታወቀበት የካቲት ወር 2007 ዓ.ም. አራት ኪሎ አካባቢ በመገናኘት፣ ኑዌሮች ከፌዴራል መንግሥት ጋር በመመሳጠር የሰብዓዊና የዴሞክራሲ መብት ጥሰት እያደረሱ መሆኑን፣ ለዓለም አቀፍ ማኅበረሰብ ለማዳረስ የጋሕነን ከፍተኛ አመራሮች በኬንያ ናይሮቢ በሚያደርጉት ስብሰባ ላይ እንዲገኝ መመካከራቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡ መንግሥት በጋምቤላ ነባር ብሔረሰቦች፣ በተለይም በማጃንግ ላይ ማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ችግሮችን እየፈጸመ መሆኑንና በክልሉ የመሬት ወረራ እያደረገ መሆኑን ለማስገንዘብ ‹‹Deforstation, Dis-Possission and Displacement of Gambella in General and Major People in Particular›› የሚል ጥናታዊ ጽሑፍ በስብሰባው ላይ እንዲያቀርብ ተሰጥቶት እንደነበር ክሱ ያብራራል፡፡

ሦስተኛው ተከሳሽ ደግሞ በጥቅምት ወር 2006 ዓ.ም. ‹‹የአካባቢ ግንኙነትና ጥበቃ›› በሚል ሽፋን በኬንያ ናይሮቢ የሽብር ቡድኑ በሚያደርገው ስብሰባ ላይ በመገኘት፣ መንግሥት የአካባቢው ተወላጆችን ከመሬታቸው በማፈናቀል ጉዳት እያደረሰ መሆኑን ለቡድኑ አመራሮች መረጃ በመስጠት 8,800 ብር መቀበሉን የተመሠረተበት ክስ ይገልጻል፡፡ በስብሰባው ላይ እንደሚገኝ ለአንደኛ ተከሳሽ ማረጋገጫ በመስጠቱና በመገኘቱ 6,039 ብር መቀበሉንም አክሏል፡፡

በአጠቃላይ ሁሉም ተጠርጣሪ ተከሳሾች የሽብር ቡድኑ በኬንያ ናይሮቢ በሚያደርገው ስብሰባ ላይ ለመሳተፍ ለመሄድ መጋቢት 6 ቀን 2007 ዓ.ም. ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ሲደርሱ በፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር ውለው፣ ላለፉት ስድስት ወራት ምርመራ ሲደረግባቸው ሰንብተው ጳጉሜን 2 ቀን 2007 ዓ.ም. በሽብርተኛ ድርጅት ውስጥ በአመራርነት፣ በማናቸውም መልኩ መሳተፍና ድጋፍ መስጠት ወንጀል እንደ ቅደም ተከተላቸው ክስ ተመሥርቶባቸዋል፡፡        

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...