Thursday, March 23, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ዜናበከባድ ሙስና ተጠርጥረው የታሰሩት የኦሮሚያ የቀድሞ ባለሥልጣን የ500 ሚሊዮን ብር ኦዲት እየተጣራባቸው...

በከባድ ሙስና ተጠርጥረው የታሰሩት የኦሮሚያ የቀድሞ ባለሥልጣን የ500 ሚሊዮን ብር ኦዲት እየተጣራባቸው ነው

ቀን:

–  ያለመከሰስ መብታቸው ሳይነሳ መታሰራቸውን ተቃወሙ

የኦሮሚያ ክልል ገቢዎች ቢሮ ኃላፊ የነበሩትና በከባድ የሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በእስር ላይ የሚገኙት አቶ ወንድሙ ቢራቱ፣ ለፌዴራልና ለክልል መንግሥታት ገቢ ማድረግ የነበረባቸውን 500 ሚሊዮን ብር ለግል ጥቅማቸው አውለዋል የሚል ጥርጣሬ በመኖሩ ኦዲት እያስደረገ መሆኑን፣ የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን ለፍርድ ቤት ገለጸ፡፡

መርማሪ ቡድኑ ነሐሴ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ተረኛ ችሎት ተጠርጣሪውን ይዞ ቀርቦ እንዳስረዳው፣ ተጠርጣሪው ለግል ጥቅማቸው አውለውታል ከተባለው 500 ሚሊዮን ብር በተጨማሪ፣ በራሳቸውና በቤተሰቦቻቸው ስም የሚገኙ የቦታዎችና የቤት ሰነዶችን በማሰባሰብ ለፎረንሲክ ምርመራ መላኩን ገልጿል፡፡ ያልተያዙ ግብረ አበሮችን አድኖ መያዝ፣ የስምንት ምስክሮችን ቃል መቀበልና ሌሎች የምርመራ ሥራዎች እንደሚቀሩት በመግለጽ፣ ፍርድ ቤቱ ለተጨማሪ ምርመራ የ14 ቀናት ጊዜ እንዲፈቀድለት ጠይቋል፡፡

ተጠርጣሪው አቶ ወንድሙ በበኩላቸው ባቀረቡት መቃወሚያ እንደገለጹት፣ እሳቸው የኦሮሚያ ክልል ምክር ቤት አባል ናቸው፡፡ በሕገ መንግሥቱ የተሰጣቸው ያለመከሰስ መብት ሳይነሳ ሕገ መንግሥቱ ተጥሶ መታሰራቸው አግባብ አለመሆኑን በመግለጽ የዋስትና መብታቸው እንዲጠበቅላቸው ጠይቀዋል፡፡ እሳቸው የክልል ባለሥልጣን በመሆናቸው የማሰርም ሆነ የመጠየቅ መብት ያለው የክልሉ መንግሥት እንጂ የፌዴራል መንግሥት አለመሆኑን በመግለጽ ተቃውመዋል፡፡

ከሌሊቱ 7፡00 ሰዓት መያዛቸው ሕገወጥ ከመሆኑም በተጨማሪ፣ በተያዙበት ወቅት 22 ሺሕ ብርና መኪናቸው የት እንዳለ አለማወቃቸውን ለፍርድ ቤቱ አስረድተዋል፡፡ መርማሪ ቡድኑ በሰጠው ምላሽ ተጠርጣሪው ባቀረቡት ተቃውሞ ላይ ፍርድ ቤቱ ቀደም ባለው ችሎት ብይን የሰጠበት መሆኑን አስታውሷል፡፡

ፍርድ ቤቱም ተጠርጣሪው ፍርድ ቤት ቀርበው በነበሩ ጊዜ ተመሳሳይ ተቃውሞ አቅርበው ትዕዛዝ የተሰጠበት መሆኑን አስታውቋል፡፡ በድጋሚ እንደማይቀበልም ገልጾላቸዋል፡፡ መርማሪ ቡድኑ ምርመራውን በፍጥነት አከናውኖ እንዲያጠናቅቅ አሳስቦ፣ ለተጨማሪ ምርመራ አሥር ቀናት ፈቅዶለታል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...