የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በአሸባሪነት ከሰየመው ግንቦት 7 ድርጅትና ከአርበኞች ግንባር ጋር ለመቀላቀል በጉዞ ላይ እያሉ አንገረብ ወንዝ ድልድይ ላይ፣ በፀጥታ ኃይሎች ተያዙ የተባሉ አምስት የሰሜን ጐንደርና የምዕራብ ጐጃም ወጣቶች ተከሰሱ፡፡
የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ ለፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ እንደሚያስረዳው ተጠርጣሪዎቹ ወርቁ ፈረደ፣ ሰጠኝ ቢልልኝና አብረሃም ሞገስ በአማራ ክልል ሰሜን ጐንደር የተለያዩ ቀበሌዎች ነዋሪዎች ሲሆኑ፣ ብርሃኑ ካሳሁንና ቢችል ቀረ ደግሞ በአማራ ክልል ምዕራብ ጐጃም ጐንጅ ወረዳ ነዋሪዎች ናቸው፡፡
ተከሳሾቹ ግንቦት ሰባትንና አርበኞች ግንባርን ተቀላቅለው ወታደራዊ ሥልጠና ለመውሰድ፣ የሁለቱም ድርጅት አባል ነው በተባለው አብርሃ መላኩ በተባለ ግለሰብ መመልመላቸውን ክሱ ያስረዳል፡፡
በመንግሥት ላይ ተፅዕኖ ለማሳደርና ኅብረተሰቡን ለማስፈራራት የአገሪቱን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተቋማትን ለማናጋትና ለማፈራረስ ከሚንቀሳቀሰውና ራሱን ‹‹አማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይሎች ንቅናቄ›› (አ.ዴ.ኃ.ን) እያለ በሚጠራው ድርጅት ውስጥ አባል ለመሆንና ለመሳተፍም አስበው እንደነበር ክሱ ያስረዳል፡፡
ብርሃኑ ካሳሁን የተባለው ተጠርጣሪ በ2006 ዓ.ም. መጨረሻ አካባቢ ገረገራ ከተባለው ቦታ ተነስቶ በባህር ዳር፣ በጐንደርና በሁመራ በማድረግ ማይካድራ (የኢትዮጵያና የኤርትራ አዋሳኝ ድንበር) በተባለ ቦታ ሲደርስ፣ የድርጅቱ አባላት አግኝተውት ወደ ሱዳን በመሄድ መቀላቀሉን ክሱ ይገልጻል፡፡ ቢችል ቀረ የሚባለውን ተከሳሽንም ብርሃኑ መመልመሉን ክሱ ያክላል፡፡ ሁሉም ተከሳሾች በተለያዩ ወራት በ2007 ዓ.ም. በፀጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ሥር ውለው ክስ ተመሥርቶባቸው ማረሚያ ቤት ሆነው እንዲከታተሉ፣ በክሱ ላይ ተቃውሞ ካላቸው እንዲያቀርቡ ለጥቅምት 8 ቀን 2008 ዓ.ም. ተቀጥረዋል፡፡