Tuesday, March 28, 2023
- ማስታወቂያ -
- ማስታወቂያ -

አቶ ኤርሚያስ አመልጋ ከአክሰስ ቦርድ ሰብሳቢነታቸው ተነሱ

- ማስታወቂያ -

ተዛማጅ ፅሁፎች

‹‹መንግሥት አክሲዮን ማኅበሩን ለማፍረስ በሚደረግ እንቅስቃሴ ላይ ጥብቅ ዕርምጃ ይወስዳል›› አቶ ኑረዲን መሐመድ፣ የቴክኒክ ኮሚቴ ሰብሳቢ

በድንገት ከአገር ወጥተው በተባበሩት ኤምሬት ዱባይ ከተማ ለሁለት ዓመታት ከቆዩ በኋላ ከመንግሥት ጋር ባደረጉት ድርድር ከለላ ተሰጥቷቸው ወደ ኢትዮጵያ የተመለሱት አቶ ኤርሚያስ አመልጋ፣ አገር ውስጥ ከተመለሱ በኋላ ቀድሞ ወደነበሩበት የአክሰስ ሪል ስቴት አክሲዮን ማኅበር ቦርድ ሰብሳቢ ሆነው የተሾሙ ቢሆንም፣ ‹‹ምንም ዓይነት ሥራ አልሠሩም›› ተብለው ከሰብሳቢነታቸው ተነሱ፡፡

የቦርድ አባላት ነሐሴ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ባደረጉት አስቸኳይ ስብሰባ አቶ ኤርሚያስን ከቦርድ ሰብሳቢነታቸው ያነሷቸው፣ የቦርድ ሰብሳቢ ሆነው ከተሾሙ ከመጋቢት 26 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ በእሳቸው ሰብሳቢነት በርካታ ስብሰባዎችን ያደረጉ ቢሆንም፣ በሥነ ሥርዓት ጉዳዮችና አሉባልታ ወሬዎች ላይ ከመነታረክ ያለፈ ምንም ዓይነት ቁምነገር አለመሥራታቸውን የቦርዱ አስቸኳይ ስብሰባ ቃለ ጉባዔ ያስረዳል፡፡ አቶ ኤርሚያስ በሕግና በሥርዓት ሊሠሩ ባለመቻላቸው፣ ቦርዱ የኩባንያውን ችግር ለመፍታት በመንግሥት ለተቋቋመው የቴክኒክ ኮሚቴ በማሳወቁ ኮሚቴው መመርያ ሰጥቶ እንደነበርም በቃለ ጉባዔው ተገልጿል፡፡ ኮሚቴው በሰጠው መመርያ ቦርዱ ስለ አክሰስ ሪል ስቴት አካሄድ ፍኖተ ካርታ እንዲያቀርብ አዞ የነበረ ቢሆንም፣ ጥቃቅንና የትም የማያደርሱ ድርጅቱን ሥጋት ላይ የሚጥሉ ነገሮች ከመነሳታቸው ባለፈ ፋይዳ ያለው ነገር ሊሠሩ ባለመቻላቸው ከቦርድ ከኃላፊነታቸው እንዲነሱ በሙሉ ድምፅ መወሰኑን የቦርዱ ቃለ ጉባዔ አስታውቋል፡፡ አክሰስ ሪል ስቴት በአቶ ኤርሚያስ ሲመራ ወደ ድርጅቱ ካዝና መግባት ያለባቸውን ተሰብሳቢ ሒሳቦች ከማንሳት ይልቅ ዕዳ መቀበልን እንዲያስቀድም መደረጉን ቦርዱ ገልጿል፡፡ ድርጅቱን ከውድቀት ሊያነሳ የሚችል ብዙ ተሰብሳቢ በሕጋዊ ሰነድ የተያዘ ገንዘብ ቢኖርም፣ በእሱ ጉዳይ ላይ ውይይት አለመደረጉንም ጠቁሟል፡

አቶ ኤርሚያስ ወደ አገር ቤት የተመለሱበት ዓላማ እንዲያሳካ በሚል ቦርዱ ብዙ ነገሮችን እያየ እንዳላየ ማለፉን ጠቁሞ፣ አሁን ግን ሥጋው መሬት ላይ እያለ የደረቀ ቋንጣ እያወረደ መሆኑን በመገንዘብ ዕርምጃውን ለመውሰድ መገደዱን ገልጿል፡፡ አቶ ኤርሚያስ ያለ ቦርዱ ተሳትፎ በራሳቸው ለተለያዩ ድርጅቶች ደብዳቤ መጻፋቸው፣ ቅጥር ማካሄዳቸውና ‹ፒንግል ሪል ስቴት› ከተባለ የቻይና ኩባንያ ጋር የመግባቢያ ስምምነት መፈራረማቸውን ቦርዱ ጠቁሞ፣ ነገር ግን ኩባንያው በሕይወት ይኑር አይኑር የሚታወቅ ነገር እንደሌለ አስታውቋል፡፡ በአጠቃላይ አቶ ኤርሚያስ ከነሐሴ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ከቦርድ ሰብሳቢነታቸው ተነስተው ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ የነበሩት ወ/ሮ መብራት ወልደ ትንሳዔ በሰብሳቢነት እንዲመሩ በመስማማት መወሰኑን አስታውቋል፡፡

አቶ ኤርሚያስ መሥራችና የቦርድ ሊቀመንበር ከነበሩበት አክሰስ ሪል ስቴት፣ በአገር ውስጥና በተለያዩ አገሮች የሚኖሩ ከ2,000 በላይ የሚሆኑ ሰዎች የቤት ግዢ የፈጸሙ ቢሆንም፣ እስካሁን ድረስ ቤትም ሆነ ገንዘባቸውን አለማግኘታቸውን እየገለጹ ነው፡፡ አቶ ኤርሚያስ በድንገት ከአገር ሲወጡ ቤት ገዢዎቹ የተለያዩ ተቃውሞዎችን ሲያቀርቡ ከርመው፣ በመጨረሻ መንግሥት ጣልቃ ገብቶ ከአቶ ኤርሚያስ ጋር በመደራደር ለተለያዩ ግለሰቦች ቆርጠውት በነበረ ደረቅ ቼክ ምክንያት እንደማይታሰሩ ዋስትና ተሰጥቷቸው፣ በየካቲት ወር 2007 ዓ.ም. ወደ አገር ቤት ተመልሰዋል፡፡

አቶ ኤርሚያስ በወቅቱ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ ከየካቲት 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ሥራ እንደሚጀምሩና ማንኛውም ቤት ገዢ የፈለገውን ማለትም ቤቱን ወይም ገንዘቡን ከነወለዱ እንደሚመልሱ ቃል መግባታቸው በወቅቱ ተዘግቧል፡፡ ነገር ግን አንዳንድ ቤት ገዢዎች ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ አቶ ኤርሚያስ እንኳን ገንዘብ ሊመልሱና ስለቤት ሊያናግሯቸው ቀርቶ በአካል አይተዋቸው እንደማያውቁ እየገለጹ ነው፡፡ መንግሥት የሰጣቸውን ተስፋም ማየት ባለመቻላቸው ተስፋ እየቆረጡ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ በአጭር ጊዜ ተብሎ ላለፉት ስድስት ወራት ምንም ነገር አለማየታቸውን አስረድተዋል፡፡

የአቶ ኤርሚያስ ፍላጐት በተለያዩ መንገዶች ነገሮችን በማጓተት ድርጅቱ እንዲፈርስና ከተጠያቂነት ለመዳን ስለሆነ፣ ቃል የገባው መንግሥት በነገሩ ላይ ትኩረት እንዲሰጥ ጠይቀዋል፡፡

በቦርዱ ጽሕፈት ቤት ለሚሠሩ 13 ሠራተኞች የሰኔና የሐምሌ ወር ደመወዝ መክፈል ሳይቻል ቀርቶ ቴክኒክ ኮሚቴውና ከቤት ገዢዎች ለተለያዩ ወጪዎች ከሰበሰበው ገንዘብ አክሲዮን ማኅበሩ ተበድሮ መክፈሉን አስረድተዋል፡፡ ይኼ የሚያሳየው ድርጅቱ ችግር ውስጥ መሆኑን እንደሆነ አስረድተው መንግሥት አስቸኳይ ውሳኔ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል፡፡

የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ የንግድ ሚኒስትሩ አማካሪ አቶ ኑረዲን መሐመድ ግን በቤት ገዢዎቹም ሆነ በቦርዱ ሐሳብ አይስማሙም፡፡ እሳቸው እንደሚሉት ሰው የፈለገውን ቢያወራ ኮሚቴው መሥራት የሚችለውን እየሠራ እንደሆነና በሥራውም ውጤታማ መሆኑን ነው፡፡

ከየአቅጣጫው እየጮሁ የሚገኙት ከቤት ገዢዎቹ አሥር በመቶ የማይሆኑትና አቶ ኤርሚያስ ሲነኩ የሚነኩ ሰዎች መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ አቶ ኤርሚያስ የሕግ ከለላ የተሰጣቸው ሥራዎች ተስተካክለው እንዲሄዱ እንጂ ከሕግ ተጠያቂነት ለማዳን አለመሆኑን የገለጹት አቶ ኑረዲን፣ በአቶ ኤርሚያስ በኩል ስላሉ ሰዎች መረጃ መጠየቅ ሲጀመር የእሳቱ ወላፈን የሚነካቸው ሰዎች ብዙ ነገር ለማድረግ እየጣሩና እየተወራጩ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ ከአንድ ወይም ሁለት ሳምንት በኋላ በተለይ አምቼ አካባቢ ያለው ፕሮጀክት ይፋ እንደሚደረግና ሥራ እንደሚጀመር የጠቆሙት ሰብሳቢው ቦርዱ፣ የቦርዱ አባላትና አስፈጻሚው የየራሳቸው አጀንዳ ስላላቸው ምንም ነገር እንዳልተሠራ የሚያስወሩት ወሬ እንደሚቆም ተናግረዋል፡፡ ሁሉም የሚሮጠው የራሱን መብት ለማስከበር መሆኑን ጠቁመው መንግሥት ግን ተረጋግቶና ሁሉንም ነገር በአግባቡ በመሥራት እያንዳንዷን ነገር ማስተማሪያ ማድረግ እንደሚፈልግ ገልጸዋል፡፡

አክሲዮን ማኅበሩ ከፈረሰ ተጠያቂነት ስለማይኖር በንግድ ሚኒስቴር የአክሲዮን ማኅበራት ክትትልና ድጋፍ ዳይሬክቶሬት የመጀመሪያ የቤት ሥራው ጥንቃቄ አድርጐ ጅምሩን ዳር ማድረስ መሆኑንም አቶ ኑረዲን አስረድተዋል፡፡ አክሲዮን ማኅበሩን ለማፍረስ የሚደረግ እንቅስቃሴ ከታየ መንግሥት ጥብቅ ዕርምጃ እንደሚወስድም አስረድተዋል፡፡ የሆነ ያልሆነ መረጃ ወጥቶ ቤት ገዢውን ተስፋ የሚያስቆርጥ ወሬ እንደሚሰማ የገለጹት አቶ ኑረዲን፣ መንግሥት አቶ ኤርሚያስ ሳይኖሩ ኃላፊነት መውሰዱን ቤት ገዢው መዘንጋት እንደሌለበት አስታውሰዋል፡፡

አቶ ኤርሚያስ ወደ አገር ቤት እንዲመጡ የተደረገው ሥራ እንዲሠሩ፣ ሚስጥሮችን እንዲያወጡና ሦስተኛ ወገኖችን እንዲታገሉ መሆኑን የገለጹት አቶ ኑረዲን፣ ቦርዱ ራሱ ሾሞ ራሱ እንዳወረዳቸው መግለጹ አግባብ አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሌላ መሾምም ሆነ መነሳት ካለባቸው በሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ጽሕፈት ቤት የፀደቀ ሰነድ መኖር እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ ይኼ ባልሆነበት ሁኔታ ስለሚካሄደው ነገር የሚያውቁት ነገር እንደሌለ ገልጸዋል፡፡ አሁን በቦርዱም ሆነ በጥቂት ቤት ገዢዎች እየተደረገ ያለው ነገር ሥራውን የሚያስትና የሚያደናቅፍ አለመሆኑን አቶ ኑረዲን ተናግረዋል፡፡     

ቦርዱ ባሳለፈው ውሳኔና ቤት ገዥዎች እያቀረቡት ስላለው ተቃውሞ ምላሽ እንዲሰጡ አቶ ኤርሚያስን ሪፖርተር ቢሮቸአው ድረስ በመሄድና በስልክ ጭምር ለማግኘት ያደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡    

spot_img
- Advertisement -spot_img

የ ጋዜጠኛው ሌሎች ፅሁፎች

- ማስታወቂያ -

በብዛት ከተነበቡ ፅሁፎች