– የህንዱ ኩባንያ ሥራ ሊያቆም ቀናት እንደቀሩት ተጠቆመ
በመላ አገሪቱ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልና አገልግሎት አመራሮች ለአራት ቀናት የሚቆይ የሥራ አፈጻጸም ግምገማ፣ ነሐሴ 5 ቀን 2007 ዓ.ም. በሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ አዳራሽ ጀመሩ፡፡
በመላ አገሪቱ የሚገኙ ዲስትሪክት ኃላፊዎች፣ ምክትል ሥራ አስፈጻሚዎችና በተለያዩ የኃላፊነት ቦታ ላይ የሚገኙ የሁለቱ መሥሪያ ቤቶች አመራሮች የሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን ካቀረቡ በኋላ፣ ሪፖርቱን መነሻ በማድረግ ግምገማ እንደሚያደርጉ ተሳታፊዎቹ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
በምክትል ጠቅላይ ሚኒትርነት ማዕረግ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ክላስተር አስተባባሪ፣ የመገናኛና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትርና የሁለቱ መሥሪያ ቤቶች ሥራ አመራር ቦርድ ሰብሳቢ ዶ/ር ደብረ ጽዮን ገብረ ሚካኤል የተጀመረው የአመራሮቹ ግምገማ እስከ ፊታችን ዓርብ ነሐሴ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ እንደሚቆይ ተጠቁሟል፡፡
ዶ/ር ደብረ ጽዮን ትናንትና ውይይቱን ከፍተው ለግማሽ ቀን መድረኩን መምራታቸውን ተሳታፊዎቹ ጠቁመው፣ ሁሉም አመራሮች የሥራ አፈጻጸም ሪፖርታቸውን እንደሚያቀርቡም አስታውቀዋል፡፡
የቀድሞው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ኮርፖሬሽን ለሁለት ከተከፈለ ሁለት ዓመታት ያለፉት ሲሆን፣ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል በኩል የተጋነነ ችግር ቀርቦ ባያውቅም፣ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት ላይ ግን ከፍተኛ ሮሮ ሲቀርብ የነበረ ከመሆኑ አንፃር በግምገማው ላይ ትኩረት የሚደረገው በአገልግሎቱ ዘርፍ እንደሚሆን ተሳታፊዎቹ ግምታቸውን ተናግረዋል፡፡
የሥራ አመራር ቦርዱ ሰብሳቢ ዶ/ር ደብረ ጽዮን ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን እንደገለጹት፣ የአገልግሎቱን ዘርፍ እየመራ የሚገኘው የህንዱ ፓወር ግሪድ ኮርፖሬሽን ኦፍ ኢንዲያ ኮንትራቱ አይራዘምለትም፡፡ በዚህም ምክንያት በግምገማው ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እነማን በቦታው ላይ እንደሚተኩና እንደሚሾሙ ሐሳብ ሊቀርብ እንደሚችልም ጠቁመዋል፡፡ ዶ/ር ደብረ ጽዮን እንደገለጹት ከሆነ፣ የህንዱ ኩባንያ ከቀናት በኋላ ኮንትራቱን አጠናቆ ወደ አገሩ ይመለሳል፡፡