ታዋቂው ዘ ኢኮኖሚስት መጽሔት በዓለም ከሚያካሂዳቸው የተለያዩ ስብሰባዎች መካከል የኢትዮጵያ ጉባዔ በሚል የሚካሄደው ጉባዔ፣ በመጪው ዓመት ጥቅምት ወር እንደሚካሄድ ሲታወቅ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ በጉባዔው ላይ ንግግር እንደሚያደርጉ ይፋ ተደርጓል፡፡
ኢትዮጵያን በመተቸት ይታወቅ የነበረው ዘ ኢኮኖሚስት መጽሔት፣ በከፍተኛ ባለሥልጣናት ዘንድ በተለይም በሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ዘንድ ተባቢነት እንደነበረው ይታወቃል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ መጽሔቱን እንደሚያነቡ በሚዲያ መግለጻቸውም ይታወሳል፡፡ ሆኖም መጽሔቱ በመንግሥት ላይ ይሰነዝር በነበረው የሰላ ትችት ሳቢያ ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ጉባዔውን ለማካሄድ ያቀረበው ጥያቄ ውድቅ ተደርጎበት እንደነበርም አይዘነጋም፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ በሕይወት በነበሩበት ወቅት ሊካሄድ ከጫፍ ደርሶ የነበረው ጉባዔም፣ በአጀንዳ አለመግባባት ሳቢያ መታጠፉ አይዘነጋም፡፡
ከጊዜ በኋላ የአቋም ለውጥ ያደረገ የሚመስለው ዘ ኢኮኖሚስት፣ የአገሪቱን ኢኮኖሚያዊ ዕድገትና የመንግሥት አሠራር ሲያወድስ ይታያል፡፡ ዘ ኢኮኖሚስት በ251 ኮሙኒኬሽንስ ኩባንያ አማካይነት ባሠራጨው መግለጫ መሠረት፣ በመጪው ጥቅምት ወር ለሁለት ቀናት ‹‹ቀጣይነት ያለውን ዕድገት ማስቀጠል›› ወይም ‹‹ድራይቪንግ ኮንቲኒዩድ ግሮውዝ›› በሚል ርዕስ ላይ የሚያካሂደው ጉባዔ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያምን ጨምሮ፣ የአሜሪካው ብላክ ራይኖ ኩባንያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብሪያን ኸርሊ፣ የእንግሊዙ ፒታርድስ ኩባንያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሬግ ሃንኪ ንግግር እንደሚያደርጉ ሲታወቅ፣ 150 የተመረጡ ተሳታፊዎችም ይታደማሉ ተብሏል፡፡
ብላክ ራይኖ ኩባንያ የብላክ ስቶን እህት ኩባንያ ሲሆን በአፍሪካ ኢነርጂ መስኮች ላይ የተሰማራ ነው፡፡ በኢትዮጵያም እስከ ጂቡቲ ወደብ ይዘረጋል ለተባለው የነዳጅ ማስተላለፊያ መስመር ስሙ እየተነሳ ይገኛል፡፡ ፒታርድስ በኢትዮጵያ የቆዳ ኢንዱስትሪውን ከተቀላቀለ ሰንበትበት ያለና የኢትዮጵያ ቆዳ አክሲዮን ማኅበርን ከመንግሥት ከመግዛት ባሻገር፣ በእጅ ጓንት ምርቶች ኤክስፖርት ስሙ የሚጠቀስ ግዙፍ ኩባንያ ነው፡፡
በኢትዮጵያ ጉባዔ ዘ ኢኮኖሚስት ከሚያወያይባቸው ነጥቦች መካከል የአገሪቱ የሕዝብ ብዛትና ያስገኘው ጥቅም፣ የአገሪቱ ቴሌኮም ዘርፍና አሁን በሚገኝበት ይዞታ የሚኖረው የዕድገት አቅም፣ እንዲሁም የውጭ ኩባንያዎች ይሳተፉበት ዘንድ ዘርፉ ክፍት ስለመደረጉ ይነሳሉ ከተባሉት ነጥቦች ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡ የአገሪቱ የመሠረተ ልማት ወጪና ከአጠቃላይ ኢኮኖሚ አኳያ ሲታይ ከአፍሪካ ትልቁ ሊያስብለው ስለመቻሉ የመወያያ ርዕሶች ሲሆኑ፣ ከዚህም በሻገር በመንግሥት የሚመራው የኢኮኖሚ ልማት ቀጣይነትና ዘላቂነት፣ የግሉ ዘርፍ እያጋጠሙት ስላሉት ፈተናዎች፣ በመንግሥት ቁጥጥር ሥር ከሚገኘው የፋይናንስ ዘርፍ የፋይናንስ አቅርቦት ችግሮችን እንዴት መፍታት እንደሚቻልና መጪዎቹ አምስት ዓመታት ለኢትዮጵያ የሚኖራቸውን ፋይዳ ዘ ኢኮኖሚስት እንደሚያወያይ ይፋ አድርጓል፡፡