Thursday, March 23, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ማውጫ ጊዜ ላልተወሰነ ጊዜ መተላለፉ ተጠቆመ

የጋራ መኖሪያ ቤቶች ዕጣ ማውጫ ጊዜ ላልተወሰነ ጊዜ መተላለፉ ተጠቆመ

ቀን:

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰኔ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. 40/60ን ጨምሮ 40 ሺሕ የሚሆኑ የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ዕጣ እንደሚያወጣ የገለጸ ቢሆንም፣ የዕጣ ማውጫውን ቀን ላልተወሰነ ጊዜ ማስተላለፉ ተጠቆመ፡፡

ዕጣ ይወጣላቸዋል ከተባሉት የጋራ መኖሪያ ቤቶች በተለይ ለመጀመሪያ ጊዜ በዕጣ ይከፋፈላል የተባለው 40/60 የጋራ መኖሪያ ቤት፣ ከቃሊቲ ማረሚያ ቤት አለፍ ብሎ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ፊት ለፊትና ሰንጋ ተራ የሚገኙት ሕንፃዎች ግንባታ የተጠናቀቀ ቢሆንም፣ አብረው መጠናቀቅ የነበረባቸው መሠረተ ልማቶች ባለመጠናቀቃቸው የዕጣ መውጫው ጊዜ እንዲራዘም መደረጉን ምንጮች ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

የአስተዳደሩ ካቢኔና ቦርድ ተሰብስቦ ውሳኔ አለማሳለፉም ለዕጣው አለመውጣት ሌላው ምክንያት መሆኑን የጠቆሙት ምንጮች፣ የአስተዳደሩ ከፍተኛ ሹማምንት በሕዝብ መገናኛ ብዙኃን ሳይቀር ሰኔ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. የሚተላለፉ ቤቶች እንዳሉ ሲገለጽ ከርሞ፣ ቃላቸው አለመጠበቁ ‹‹ለምን?›› የሚል ጥያቄ እያስነሳ መሆኑንም አክለዋል፡፡

የመሠረተ ልማት አለመሟላት እንደ ምክንያት ሊወሰድ እንደማይችል የሚናገሩት ምንጮች፣ በአሥረኛው ዙር ዕጣ ከወጣባቸው 35 ሺሕ የጋራ መኖሪያ ቤቶች መካከል የአብዛኞቹ ሳይቶች መሠረተ ልማታቸው ገና ያልተጀመረ በመሆኑ ነው፡፡

ለሪፖርተር አስተያየት የሰጡ የተወሰኑ የ40/60 ተመዝጋቢዎች፣ ሙሉ በሙሉ ክፍያ የፈጸሙ ቅድሚያ እንደሚሰጣቸው ገልጸው፣ አሁን ግን ዋጋው በጣም ሊጨምር ስለሚችል ሙሉ በሙሉ የከፈሉም ቢሆኑ ተጨማሪ ክፍያ እንደሚጠየቁ መስማታቸው አሳስቧቸዋል፡፡ በሌላ በኩል ሁሉም በዕጣው ተካተው ዕድለኞች በዕጣ እንደሚያገኙ፣ የቤቶቹን መገንባት ያዩ ሌሎች ተመዝጋቢዎች በመሀል ሙሉ በሙሉ መክፈላቸውም ስላሳወቁ፣ ሲጀመር አጠናቀው ከከፈሉት ጋር ሊቀላቀሉ መሆኑንና ሌሎች ወሬዎችን እየሰሙ ግራ መጋባታቸውን ገልጸዋል፡፡ በተባለው ጊዜም ዕጣ አለመውጣቱ እንዳሳሰባቸው ይናገራሉ፡፡

የ20/80 ተመዝጋቢዎች በበኩላቸው ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ዕጣው ሰኔ 30 እና እስከ ነሐሴ መጨረሻ ድረስ ወጥቶ ዕድለኞች የቤት ባለቤት እንደሚሆኑ የተነገረበት ወቅት የምርጫ ጊዜ በመሆኑ፣ ሕዝቡን ለመያዝ ነው የሚል ግምታቸውን ዕውን እንዳደረገው ተናግረዋል፡፡ ይህ ባይሆን ኖሮ ዕጣው በተባለው ጊዜ መውጣት ነበረበት ሲሉም ይከራከራሉ፡፡

ሰኔ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. ዕጣ እንደሚወጣ በአስተዳደሩ ከፍተኛ ሹሞች ከገለጹ በኋላ ለምን ዕጣውን እንዳላወጡ ወይም ያልወጣበትን ምክንያት እንዲገልጹ፣ የአዲስ አበባ ቤቶች ግንባታ ፕሮጀክት ጽሕፈት ቤትንም ሆነ የቤቶች ልማትና አስተዳደር ኤጀንሲን ለማግኘት የተደረገው ጥረት አልተሳካም፡፡

ነገር ግን አንድ ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ የቤቶች ልማትና አስተዳደር ኤጀንሲ ባልደረባ እንደሚሉት፣ ዕጣው ያልወጣው በሁለት ምክንያቶች ነው፡፡ የመጀመሪያው የአስተዳደሩ ካቢኔና ቦርድ ተሰብስቦ ውሳኔ ባለማስተላለፉ ሲሆን፣ ሌላው በታሰበበት ወቅት ይጠናቀቃሉ የተባሉ መሠረተ ልማቶች ባለመጠናቀቃቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በዋናነት የ40/60 የቤት ፕሮግራም የመጀመሪያ ከመሆኑ አንፃር ሁሉም ነገር ተጠናቆ፣ ዕጣው በወጣበት ዕለት ለባለዕድለኞች ወዲያውኑ ቁልፍ ለማስረከብ በመታሰቡ መሆኑን አክለዋል፡፡

  

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]

አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላወራህ የፈለኩት ክቡር...

የትግራይ ክልል የሽግግር አስተዳደር ምሥረታና የሰላም ስምምነቱ ሒደት

በትግራይ ክልል ጊዜያዊ የሽግግር መንግሥት ለመመሥረት ደፋ ቀና እየተባለ...

ጥራዝ ነጠቅነት!

ከሜክሲኮ ወደ ጀሞ እየሄድን ነው፡፡ የተሳፈርንበት አሮጌ ሚኒባስ ታክሲ...