በአልሸባብ ተመልምለው የሕዋስ (ሴል) አባላት ናቸው የተባሉ ኢትዮጵያ ውስጥ በተመረጡ ቦታዎችና በመንግሥታዊና መንግሥታዊ ባልሆኑ ተቋማት ላይ የሽብር ጥቃት ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ በፀጥታ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር የዋሉ የተባሉ አምስት ተጠርጣሪዎች፣ ኢትዮጵያውያን፣ ሐምሌ 6 ቀን 2007 ዓ.ም. ክስ ተመሠረተባቸው፡፡
የፌዴራል ዓቃቤ ሕግ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 32 (1/ሀ)ን በመተላለፍ በዋና ወንጀል ተካፋይ በመሆን፣ የወንጀል ሕግ አንቀጽ 38 (1 እና 2) በመተላለፍ ወንጀል ለመፈጸም አድማ በማድረግና የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652/2001 አንቀጽ (4)ን በመተላለፍ የሽብር ድርጊት ለመፈጸም የማቀድ፣ የመዘጋጀት፣ የማሴርና የማነሳሳት ሙከራ ለማድረግ ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል ብሎ ክስ የመሠረተባቸው፣ በድሪ የሱፍ ሮባ፣ አነስ ኡስማን ዑመር፣ አህመድ ኑር ሳኒ፣ መሐመድ አህመድ ኡስማንና እስማኤል አደም መሐመድ ናቸው፡፡
ዓቃቤ ሕግ ለፌዴል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት ያቀረበው ክስ እንደሚያስረዳው፣ ሁሉም ተጠርጣሪዎች በኦሮሚያ ክልል ውስጥ የሚገኙ ናቸው፡፡
ተከሳሾቹ ከአልሸባብ ጋር በመስማማትና አባል በመሆን ከሶማሊያ ግዛት ወደ ኢትዮጵያ የሚላኩ ተቀጣጣይ ፈንጂዎች መሥራት የሚችሉ የአልሸባብ የፈንጂ ሥራ ባለሙያዎችን ለመቀበል፣ ለፈንጂ መሥሪያ የሚሆን ቤት ለመከራየት ሲንቀሳቀሱ እንደነበር ክሱ ያስረዳል፡፡
በድሪ የሱፍ ሮባ የተባለው ተጠርጣሪ በሽር ቱሬ በሚባል የአልሸባብ አመራር በ1999 ዓ.ም. በአባልነት ከተመለመለ በኋላ፣ ሞቃዲሾ ውስጥ በሚገኘው አቡሐረሬ ተብሎ በሚጠራው መስጊድ ውስጥ ለስድስት ወራት ወታደራዊና የፖለቲካ ትምህርት ሥልጠና መውሰዱን ክሱ ያስረዳል፡፡ ተጠርጣሪው በ2002 ዓ.ም. ወደ መቋዲሾ በመሄድ ለአልሸባብ አባል የሚሆኑ ወጣቶችን በመመልመል ለሥልጠና እዚያ እንዲሄዱ ሲያዘጋጅ እንደነበርም በክሱ ተጠቁሟል፡፡
ግለሰቡ ጥቃት ለመፈጸም ከሞቃዲሾ ወደ ኢትዮጵያ ግዛት የሚመጡትን የህዋስ አባላት መኖሪያ ቤት ተከራይቶ ለማስቀመጥ፣ የተመለሱትን ወጣቶች በኃላፊነት ለመምራት፣ መረጃ እየሰበሰበ ለአልሸባብ አባላት እንዲልክ የተሰጠውን ተልዕኮ ለመፈጸም ሲንቀሳቀስ እንደነበር ዓቃቤ ሕግ በክሱ ዘርዝሯል፡፡
አብዱልአዚዝ አልዩ (አቡ ያሲን) የተባለ የአልሸባብ አመራርና የፈንጂ ባለሙያ በ2006 ዓ.ም. ኢትዮጵያ ገብቶ ባሌ ሮቤ ከተማ ውስጥ መልምሎ በህዋስ ያራጃቸውን ስድስት አባላት፣ አንደኛ ተከሳሽ እንዲመራቸው ኃላፊነት መውሰዱንም ክሱ ያስረዳል፡፡
ሻሸመኔ ከተማ ውስጥ ‹‹ቁርዓን አስተምራለሁ ወይም የቁርዓን መምህር ነኝ›› በሚል ሽፋን አባላትን መመልመልና ማደራጀት እንዳለበት በሽር ቱሬ ከሚባለው የአልሸባብ አመራር ተልዕኮ መቀበሉንም ዓቃቤ ሕግ በክሱ ጠቅሷል፡፡ አገር ውስጥ ባሉ የተለያዩ ባንኮችም ገንዘብ ይላክላቸው እንደነበር የገንዘቡን መጠንና የባንኮቹን ስም ጠቅሶ ዓቃቤ ሕግ በክሱ አካቷል፡፡
በኅዳር ወር 2007 ዓ.ም. በጊኒር በኩል ወደ ኢትዮጵያ ይገባል ለተባለው የአልሸባብ አመራር አብዱላዚዝ፣ በነገሌ ቦረና በኩል በታኅሳስ ወር 2007 ዓ.ም. ፈንጂ ይዘው የሚገቡትን አባላት አንደኛ ተከሳሽ ሻሸመኔ በሚገኘው ቤቱ አሳርፏቸው ፈንጂ የሚሠራበትን ማቴሪያል እንዲያዘጋጅና የማፈንጃ ዒላማዎችን እንዲያጠና ተልዕኮ ተቀብሎ ይንቀሳስ እንደነበር ዓቃቤ ሕግ በክሱ ገልጿል፡፡ ሻሸመኔ፣ አሰላና ባሌ ሮቤ ከተሞች ውስጥ ባንክ ቤትና ፖስታ ቤት መኖር አለመኖሩን አጥንቶ እንዲቆይም ትዕዛዝ ተሰጥቶት እንደነበር አክሏል፡፡ ተጠርጣሪው የሽብር ቡድኑ አደራጅና አመራር በመሆን ተሳታፊ እንደነበር ዓቃቤ ሕግ በዝርዝር ገልጿል፡፡
ሁለተኛው ተጠርጣሪ ተከሳሽ አነሰ ኡስማንም እንደ አንደኛ ተከሳሽ በተለይ ባሌ ዞን ሮቤ ከተማ ውስጥ በመንቀሳቀስ አባላት በመመልመል፣ በተለይም አራተኛና አምስተኛ ተከሳሾችን መልምሎ ወደ ሶማሊያ ሥልጠና ሊልክ ሲል በቁጥጥር ሥር መዋሉን የዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡ ሦስተኛ፣ አራተኛና አምስተኛ ተከሳችም በሁለተኛ ተከሳሽ ከተመለመሉ በኋላ ወታደራዊና ፖለቲካዊ ሥልጠና ለመውሰድ ወደ ሶማሊያ ለመሄድ በመንቀሳቀስ ላይ እያሉ በቁጥጥር ሥር መዋላቸው በክሱ ተገልጿል፡፡
ተከሳሾቹ ክሱ በችሎት ከተነበበላቸው በኋላ በራሳቸው ጠበቃ ማቆም እንደማይችሉ በመግለጻቸው፣ የተከላካይ ጠበቃ ጽሕፈት ቤት ጠበቃ እንዲመደብላቸው ትዕዛዝ በመስጠት ፍርድ ቤቱ ለሐምሌ 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡