Friday, March 31, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊየቀድሞ ቴሌ ዋና መሐንዲስና ሁለት ሥራ አስኪያጆች በሙስና ተጠርጥረው ተከሰሱ

የቀድሞ ቴሌ ዋና መሐንዲስና ሁለት ሥራ አስኪያጆች በሙስና ተጠርጥረው ተከሰሱ

ቀን:

የቀድሞው የኢትዮጵያ ቴሌኮሙዩኒኬሽን ኮርፖሬሽን (ኢትዮ ቴሌኮም) ዋና መሥሪያ ቤት ዋና መሐንዲስና የደቡብ ምሥራቅ ሪጅን ሁለት ሥራ አስኪያጆች በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው፣ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ክስ ተመሠረተባቸው፡፡

የፌዴራል የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን ዓቃቤ ሕግ በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 18ኛ ወንጀል ችሎት ክስ የመሠረተባቸው ተጠርጣሪዎች፣ የዋናው መሥሪያ ቤት ዋና መሐንዲስ የነበሩት አቶ ተክለ ማርያም ለአከ ተክለ ማርያም፣ የኮርፖሬሽኑ የደቡብ ምሥራቅ ሪጅን ምክትል ሥራ አስኪያጅና የማርኬቲንግ ኃላፊ የነበሩት አቶ መስፍን ሙርጋና የደቡብ ምሥራቅ ሪጅን ሥራ አስኪያጅ የነበሩት አቶ ጌታቸው ተረፈ አየለ ሲሆኑ፣ በግል ሥራ የተሰማሩ አቶ ግርማ ተስፋዬ የተባሉ ግለሰብም በክሱ ተካተዋል፡፡

ተከሳሾቹ የማይገባ ጥቅም ለማግኘትና ለሌላ ሦስተኛ ወገን ጥቅም ለማስገኘት በማሰብ፣ በሕዝብና በመንግሥት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሳቸውን የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ በክሱ ዘርዝሯል፡፡ ክሱ እንደሚያስረዳው፣ አቶ ተክለ ማርያም ያላቸውን የቴክኖሎጂ ዕውቀት፣ ልምድና ክፍተት በመጠቀም በግል ሥራ ከሚተዳደሩት አቶ ግርማ ጋር ከአዲስ አበባ ወደ አዳማ (ናዝሬት) ይሄዳሉ፡፡ አዳማ እንደደረሱ ለሕገወጥ ዓላማ ማስፈጸማያ የሚውል ቤት በደላላ አማካይነት አቶ ታደሰ ጅማ ከሚባሉ ግለሰብ ይከራያሉ፡፡ የቤቱን ውል ከመፈጸማቸው በፊት ቤት አከራዩ አቶ ታደሰ ጂማ 30 ቀጥታ የስልክ መስመሮችን ከቴሌ ማስገባት እንዳለባቸው ይስማማሉ፡፡ አቶ ተክለ ማርያም አብረዋቸው የሚሠሩ የውጭ አገር ዜጎች እንዳሉም ለአከራዩ አቶ ታደሰ እንደነገሯቸው ክሱ ያብራራል፡፡

ከውጭ አገር የሚመጡት ኢንቨስተሮች በመሆናቸው ለስልኩ ወጪ ክፍያ ምንም ሥጋት እንዳይገባቸው ለአቶ ታደሰ ተነግሯቸው፣ የስልክ መስመሮቹ ከገቡ በኋላ ኅዳር 21 ቀን 1995 ዓ.ም. በንግድ ሥራ የሚተዳደሩት ሁለተኛ ተከሳሹ አቶ ግርማ ተስፋዬና አቶ ታደሰ የቤት ኪራይ ውሉን መፈጸማቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡ አቶ ተክለ ማርያም ሳተላይት መቀበያ መሆኑን እያወቁ ከአቶ ግርማ ጋር በመመሳጠር በተከራዩበት ቤት ዲሽ በመትከል፣ አገሪቱ ከዘርፉ ልታገኝ የሚገባትን ገቢ እንድታጣ በማድረግ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ መሞከራቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡

አቶ ግርማ የተባሉት ተከሳሽ ቤት አከራዩን አቶ ታደሰን በዜግነት ጥቁር አሜሪካዊ እንደሆኑ በመግለጽ ከተዋወቋቸው በኋላ፣ አብረዋቸው ከነበረ ኤም ዴቪድ ከሚባል ነጭ አሜሪካዊ ጋር ያስተዋውቋቸዋል፡፡ ወደ ተከራዩት ቤት በመውሰድ በአከራይ ተከራይ ውል ላይ ካስፈረሟቸው በኋላ፣ ስልክ ላስገቡበት 16,500 ብር ለቴሌ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት እንደከፈላቸው ክሱ ይገልጻል፡፡

ለሕገወጥ ድርጊት የሚውሉ ዘመኑ ያፈራቸውን ዕቃዎች በኤርፖርት ታክሲ ጭነው አዳማ በመውሰድ፣ በታኅሳስ ወር 1995 ዓ.ም. ዲሹን መትከላቸውንም ክሱ አክሏል፡፡ በመሆኑም በወንጀሉ በመሳተፍ በሕዝብና በመንግሥት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ መሞከራቸውን የዓቃቤ ሕግ ክስ ይገልጻል፡፡

የቅርንጫፍ መሥሪያ ቤቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅና የማርኬቲንግ ኃላፊ የነበሩት አቶ መስፍን ሙርጋም፣ ቤት ያከራዩት አቶ ታደሰ 30 ቀጥታ መስመር እንዲገባላቸው ጥያቄ ሲያቀርቡ፣ የቅርንጫፉ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ተረፈ ማኅተም ሳያደርጉ የመሩትን ደብዳቤ ‹‹ለምን?›› ብለው ምክንያቱን ሳያረጋግጡ የቀረበውን ጥያቄ በማፅደቃቸው፣ በሕዝብና በመንግሥት ጥቅም ላይ ጉዳት ለማድረስ መሞከራቸውን ክሱ ይገልጻል፡፡ አቶ ጌታቸውም ኮርፖሬሽኑ ያወጣውን የደንበኞች አገልግሎት አፈጻጸም መመርያ በመጣስ፣ ስልኮቹ ለምን ዓላማ እንደሚውሉ ሳይጠይቁና ሳያጣሩ በተዋረድ ላሉ ኃላፊዎች በመምራትና በማፅደቃቸው፣ በሕዝብና መንግሥት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት በማድረስና አላግባብ ሥልጣንን መገልገል ወንጀል እንደተከሰሱ የኮሚሽኑ ዓቃቤ ሕግ ክስ ያስረዳል፡፡

ሁሉም ተጠርጣሪዎች በሕዝብና በመንግሥት ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት ለማድረስ በግብረ አበርነት በፈጸሙት ሥልጣንን ያላግባብ መገልገል የሙስና ወንጀል ክስ ተመሥርቶባቸዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በሌሉበት ስለተከሰሱ፣ ኮሚሽኑ ተከሳሾቹን አፈላልጎ ለሐምሌ 21 ቀን 2007 ዓ.ም. እንዲያቀርብ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 18ኛ ወንጀል ችሎት አዟል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ተወግዘው የነበሩ ሦስቱ ሊቀጳጳሳትና 20 ተሿሚ ኤጲስ ቆጶሳት ውግዘት ተነሳ

_ቀሪዎቹ ሦስት ህገወጥ ተሿሚዎች የመጨረሻ እድል ተሰጥቷቸዋል ​ ጥር 14...

በሕወሓት አመራሮች ላይ ተመስርቶና በሂደት ላይ የነበረው የወንጀል ክስ ተቋረጠ

በቀድሞ የትግራይ ክልል ፕሬዚደንት ደብረጽዮን ገብረሚካኤ,(ዶ/ር)ና ባለፈው ሳምንት በተሾሙት...

[የምክር ቤቱ አባል ላቀረቡት ጥያቄ በተሰጣቸው ምላሽ አቤቱታቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር ትክክል ነው? ምነው? ምክር ቤቱም ሆነ...

የጉራጌ የክልልነት ጥያቄ ትኩሳት

ቅዳሜ መጋቢት 16 ቀን 2015 ዓ.ም. በጉራጌ ዞን ወልቂጤ...