Friday, March 31, 2023
- Advertisement -
- Advertisement -
ማኅበራዊበሽብር ድርጊት ክስ የተመሠረተባቸው 18 ግለሰቦች ጥፋተኛ ተባሉ

በሽብር ድርጊት ክስ የተመሠረተባቸው 18 ግለሰቦች ጥፋተኛ ተባሉ

ቀን:

–  ውሳኔውን አንብቦ ለመጨረስ ሦስት ቀናት ፈጅቷል

ራሳቸውን የሙስሊሙ ኅብረተሰብ መፍትሔ አፈላላጊ ኮሚቴ በማለት ሃይማኖታዊና ፖለቲካዊ ዓላማዎችን ለማራመድ፣ ሕገ መንግሥቱንና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በኃይል ለመጣል፣ ኢስላማዊ መንግሥት ለመመሥረት፣ በህቡዕ በመደራጀትና የሽብር ድርጊት ለመፈጸም ሲንቀሳቀሱ ተደርሶባቸዋል ተብለው የሽብርተኝነት ወንጀል ክስ የተመሠረተባቸው 18 ግለሰቦች ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ጥፋተኛ ተባሉ፡፡

የፌዴራል ከፍተኛ ዓቃቤ ሕግ ጥቅምት 15 ቀን 2005 ዓ.ም. የሽብር ድርጊት ክስ የመሠረተባቸው ሁለት መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችና 29 ግለሰቦችን የነበረ ቢሆንም፣ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቦሌ ምድብ አራተኛ ወንጀል ችሎት ጥፋተኛ ያላቸው 18 ተከሳሾችን ብቻ ነው፡፡ የቀድሞ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ጁነዲን ሳዶ ባለቤት ወ/ሮ ሐቢባ መሐመድ መሐሙድን ጨምሮ 11 ግለሰቦችና ድርጅቶቹ ከክሱ በነፃ መሰናበታቸው ይታወሳል፡፡

ፍርድ ቤቱ ለሦስት ዓመታት ያህል ሲያከራክርና ሲመረምር የከረመውን የፍርድ ሒደት አጠናቆ የጥፋተኝነት ውሳኔ የሰጠው በአቶ አቡበከር አህመድ፣ አህመዲን ጀበል፣ ያሲን ኑሩ፣ ካሚል ሸምሱ፣ በድሩ ሁሴን፣ ሼክ መከተ ሙሔ፣ ሳቢር ይርጉ፣ መሐመድ አባተ፣ አህመድ ሙስጠፋ፣ ሙራድ ሽኩር፣ አቡበከር ዓለሙ፣ ኑሩ ቱርኪ፣ ሼክ ባህሩ ዑመር፣ ሙኒር ሁሴን፣ ሼክ ሰዒድ ዓሊ፣ ጋዜጠኛ የሱፍ ጌታቸው፣ ሙባረክ አደምና ካሊድ ኢብራሂም ላይ ነው፡፡

ከሳሽ ዓቃቤ ሕግ በሁሉም ተከሳሾች ላይ አራት ክሶችን ያቀረበ ቢሆንም፣ ሦስተኛና አራተኛ ክሶች የሚያተኩሩት መንግሥታዊ ባልሆኑት ድርጅቶች ላይ በመሆናቸው ድርጅቶቹ ነፃ በመሆናቸው ክሶቹም ቀሪ ሆነዋል፡፡ በአንደኛና በሁለተኛ ክሶች ላይ ተከሳሾቹ ድርጊቱን ክደው በመከራከራቸው ዓቃቤ ሕግ እንደ ክሱ ያስረዱኛል ያላቸውን የሰዎችና የሰነድ ማስረጃዎችን አቅርቧል፡፡ ከመቶ በላይ ምስክሮችንም አሰምቷል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ያቀረባቸውን የሰዎችና የሰነዶች ማስረጃዎች ጨምሮ፣ የተከሳሾች መስቀለኛ ጥያቄ የዓቃቤ ሕግን ክስና የምስክሮች ቃል ማፍረስ አለማፍረሱን መርምሮ ተከሳሾቹ እንዲከላከሉ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ተከሳሾቹም ከ400 በላይ መከላከያ ምስክሮችን አስመዝግበው 157ቱን በማሰማት ቀሪዎቹን ትተዋል፡፡ ዓቃቤ ሕግና ተከሳሾቹ በምስክሮቻቸው ያስረዱትን የምስክርነት ቃል ከክሱና ተገቢ ሕግ ጋር በመመርመር፣ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. የጥፋተኝነት ውሳኔ ሰጥቷል፡፡

ፍርድ ቤቱ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ምክትል ፕሬዚዳንት ሰብሳቢ ዳኛ በሆኑበት ችሎት የጥፋተኝነት ውሳኔ ከመስጠቱ በፊት፣ አምስት ጭብጦችን ይዞ የክስ መዝገቡን መመርመሩን ገልጿል፡፡ ፍርድ ቤቱ የያዛቸው ጭብጦች፣ ‹‹መንግሥት በሙስሊሙ ጉዳይ ጣልቃ ገብቷል ወይስ አልገባም? መንግሥት የሙስሊሙን ማኅበረሰብ ከፋፍሏል  ወይስ አልከፋፈለም? የመጅሊሱ ምርጫ በቀበሌ እንዲሆን መደረጉ አግባብ ነው ወይስ አይደለም? ተከሳሾችን ለመያዝ የተደረገው የብርበራ ሒደት የኢትዮጵያን ሕግና ሕገ መንግሥት እንዲሁም ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ስምምነቶችን የተከተለ ነው ወይስ አይደለም? እና ተከሳሾች የቀረበባቸውን ክስ ተከላክለዋል ወይስ አልተከላከሉም?›› የሚሉ ናቸው፡፡

ፍርድ ቤቱ የሰጠው የጥፋተኝነት ውሳኔ ከመቶ ገጾች በላይ በመሆኑ ማንበብ የተጀመረው ሰኔ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ቢሆንም የተጠናቀቀው ከሦስት ቀናት በኋላ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ነው፡፡ ሰኔ 26 ቀን 2007 (ዕለተ ዓርብ) ችሎት አልነበረም፡፡ ሰኔ 29 ቀን 2007 ዓ.ም. ፍርድ ቤቱ ተከሳሾች ያቀረቡት በርካታ ገጾች ያሉት የሰነድ መከላከያ መስረጃ ማቅረባቸውን ገልጾ፣ ከክሱ ጋር የሚዛመዱትንና ፍሬ ነገር ያለባቸውን ሰነዶች መውሰዱን ገልጾ ባጭሩ አሰማ፡፡

ተከሳሾቹ ከመቀመጫቸው ተነስተው ‹‹ጥያቄ አለን›› በማለት ሲያመለክቱ፣ ‹‹ፍርድ ቤቱ ውሳኔ እየተነበበ ጥያቄ ማቅረብ አይቻልም፤›› ቢልም መናገራቸውን ቀጠሉ፡፡ እስካሁን መታፈናቸውን (የጥፋተኝነት ውሳኔው እስከተሰጠበት ቀን) ተናግረው ያቀረቡት 20,000 ገጽ ማስረጃ ሆኖ ሳለ አራት ገጽ እንኳን የማይሞላ ማስረጃ ተደርጎ መወሰዱን እንደሚቃወሙ ገለጹ፡፡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን እንዳልሠራው በመናገር ይኽንን ሊያስብላቸው የቻለው በውሳኔው ውስጥ የተፈቱ ሰዎች ስም ዝርዝር ሲጠቀስ በመስማታቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ውሳኔውን ሠርቶት ቢሆን ኖሮ የተፈቱ ሰዎች ሊካተቱ እንደማይችሉ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም በተነበበላቸው ውሳኔ ውስጥ በርካታ ስህተቶች እንዳሉም አክለዋል፡፡

ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ በመግባት በተለይ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስትሩ ዶ/ር ሽፈራው ተክለ ማርያምና ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሙስሊሙን ኅብረተሰብ በመሰብሰብ እየከፋፍሉትና የሐሰት ፕሮፓጋንዳ በመንዛትና ሙስሊሙን ሊከፋፈሉ እንደሆነ በመግለጽ የሃይማኖት ተከታዮችን ማነሳሳታቸውን የዓቃቤ ሕግ ማስረጃዎች እንደሚያረጋግጡ ገልጿል፡፡ የወሃቢያ አስተምህሮ መጥቶ ሃይማኖታቸውን ሊያስቀይራቸው መሆኑን የፌዴራል ጉዳዮች ለሙስሊሞች መንገሩን፣ የአወሊያ ተማሪዎች በመጅሊሱ መባረራቸውን፣ የወሃቢያ አስተምህሮ ሕገ መንግሥቱን ለማፈራረስ የሚንቀሳቀስ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትሩ መናገራቸውን፣ ሙስሊሞች በጨለማ ውስጥ መታሰራቸውን፣ መንግሥት ከአወሊያ ላይ እጁን ያላነሳና መጅሊሱ ያወጣው መተዳደሪያ ደንብ ሙስሊሙን የሚያከብር እንዳልሆነ በመናገር መንግሥት አስቸኳይ መልስ ካልሰጠ፣ በሌላው ዓለም የሚታየው አክራሪነት በኢትዮጵያም የማይታይበት ምንም ምክንያት እንደሌለ፣ ምርጫ ከመስጊድ ውጪ መደረግ እንደሌለበት በመንገርና በመቀስቀስ አመፅ ማነሳሳታቸውን ዓቃቤ ሕግ ካቀረበው የሰነድና የሰው ምስክሮች መረጋገጡን ፍርድ ቤቱ አብራርቷል፡፡

ተከሳሾቹ በተለያዩ ቦታዎች ባደረጉዋቸው ንግግሮች የፖለቲካ አጀንዳ እንደሌላቸው፣ ኢስላማዊ መንግሥት የመመሥረት ዓላማ እንደሌላቸውና ሞኝ አለመሆናቸውን፣ የሚፈልጉት ጥያቄያቸው እንዲመለስላቸው ማለትም የመጅሊስ ምርጫ በመስጊድ እንዲሆንና ታዛቢ እንደማያስፈልግ፣ ሕዝበ ሙስሊሙን የሚወክለው መፍትሔ አፈላላጊው ኮሚቴ ብቻ ምርጫውን የማድረግ ኃላፊነት እንዲወስድ፣ ወዘተ እንዳሉ የገለጹ ቢሆንም፣ ሃይማኖቱን ሽፋን በማድረግ ሙስሊም ኅብረተሰቡን ለአመፅ ማነሳሳታቸውን ዓቃቤ ሕግ በሰነድና በምስክሮች ማረጋገጡን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡

ተከሳሾቹ ሰላማዊ መሆናቸውን፣ በሕገ መንግሥቱ የተረጋገጠላቸውን የሃይማኖት እኩልነትና መንግሥት በሃይማኖት፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጣልቃ አይገቡም የሚለውን ለማረጋገጥ ስለእምነታቸው ከመጠየቃቸው ባለፈ፣ ምንም ወንጀል አለመፈጸማቸውን የሚያስረዱላቸው የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች ማቅረባቸውን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡

ሁሉም ተከሳሾች ከአንደኛ ተከሳሽ አቶ አቡበከር በስተቀር ዓቃቤ ሕግ ፈጽመዋል ያለውን የወንጀል ድርጊት ፖሊስ በወንጀል ሕግ 27 መሠረት በግዳጅ ቃላቸውን እንዲሰጡ ያደረጋቸው መሆኑን መናገራቸውን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡ ነገር ግን ዓቃቤ ሕግ በምስክሮቹና በሰነድ ማስረጃዎቹ ተከሳሾቹ በፖሊስ ጣቢያ አምነው የተናገሩትን በማረጋገጡ፣ ተከሳሾቹ ያቀረቡት የመከላከያ ማስረጃ የዓቃቤ ሕግን ክስ ከማረጋገጥ ባለፈ ከተጠያቂነት የሚያድናቸው አለመሆኑን ገልጿል፡፡

ፍርድ ቤቱ ተከሳሾቹ የተመሠረተባቸውን ክስ ማስተባበል አለመቻላቸውን አንድ በአንድ ሲገልጽ፣ መጀመርያ አቶ አቡበከር ከመቀመጫቸው በመነሳት ‹‹አሏህ አክበር፣ ነፃነቴን ያረጋገጥኩበት ፍርድ በመሆኑ ደስተኛ ነኝ፤›› ሲሉ፣ ሁሉም እጅ ለእጅ ታይዘው ‹‹አሏህ አክበር›› በማለታቸው ፍርድ ቤቱ ፖሊስ አስፈላጊውን ዕርምጃ እንዲወስድ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡

ተከሳሾቹ መደብዳባቸውንና ከፍተኛ በደል እንደደረሰባቸው በመከላከያ ምስክሮች ቢያስረዱም፣ በተለይ እርስ በርስ (እስረኞቹ) ከመመሰካከራቸው አንፃር ምስክርነቱ ተዓማኒ ሊባል እንደማይችል ፍርድ ቤቱ በመግለጽ ውድቅ አድርጎታል፡፡ በአጠቃላይ ተከሳሾቹ የኢትዮጵያን ሕግ፣ ሕገ መንግሥትና ኢትዮጵያ የተቀበለቻቸውን ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችን የሚጥስ ድርጊት የፈጸሙ መሆናቸውን በመግለጽ ሁሉንም ጥፋተኛ ብሏቸዋል፡፡ ተከሳሾቹ የቅጣት ማቅለያቸውን፣ ዓቃቤ ሕግ ደግሞ የቅጣት ማክበጃውን እስከ ሐምሌ 10 ቀን 2007 ዓ.ም. ድረስ በጽሕፈት ቤት በኩል እንዲያስገቡ በማዘዝ ፍርድ ለመስጠት ለሐምሌ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ቀጥሯል፡፡

spot_img
- Advertisement -

ይመዝገቡ

spot_img

ተዛማጅ ጽሑፎች
ተዛማጅ

ተወግዘው የነበሩ ሦስቱ ሊቀጳጳሳትና 20 ተሿሚ ኤጲስ ቆጶሳት ውግዘት ተነሳ

_ቀሪዎቹ ሦስት ህገወጥ ተሿሚዎች የመጨረሻ እድል ተሰጥቷቸዋል ​ ጥር 14...

በሕወሓት አመራሮች ላይ ተመስርቶና በሂደት ላይ የነበረው የወንጀል ክስ ተቋረጠ

በቀድሞ የትግራይ ክልል ፕሬዚደንት ደብረጽዮን ገብረሚካኤ,(ዶ/ር)ና ባለፈው ሳምንት በተሾሙት...

[የምክር ቤቱ አባል ላቀረቡት ጥያቄ በተሰጣቸው ምላሽ አቤቱታቸውን ለክቡር ሚኒስትሩ እያቀረቡ ነው]

ክቡር ሚኒስትር እየሆነ ያለው ነገር ትክክል ነው? ምነው? ምክር ቤቱም ሆነ...

የጉራጌ የክልልነት ጥያቄ ትኩሳት

ቅዳሜ መጋቢት 16 ቀን 2015 ዓ.ም. በጉራጌ ዞን ወልቂጤ...