‹‹ይህ ራስን ማታለልና አገርን ማዋረድ ነው›› የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር
‹‹ቅጣቱ የተሰጠው በፖሊስ ከተጣራና ፍርድ ቤቱም በምስክሮች ካረጋገጠ በኋላ ነው›› የአማራ ክልል መንግሥት
በአማራ ክልል በምሥራቅ ጎጃም ደብረ ማርቆስ ከተማ ውስጥ ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. የተገደለው የሰማያዊ ፓርቲ የዞን አመራርና የሕግ ባለሙያው የአቶ ሳሙኤል አወቀ ገዳይ ነው የተባለ ግለሰብ፣ በ19 ዓመታት ጽኑ እሥራት እንዲቀጣ ሰኔ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ፍርድ ተሰጠ፡፡
ፍርዱን የሰጠው የምሥራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ማርቆስ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሲሆን፣ ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም. ከምሽቱ 1፡30 ሰዓት አካባቢ ግድያውን መፈጸሙ በምስክሮች ተረጋግጧል የተባለው ፍርደኛ ተቀበል ገዱ ይባላል፡፡
የፓርቲው የዞን አመራር አቶ ሳሙኤል በተገደለበት ወቅት የክልሉ መንግሥት በሰጠው መግለጫ፣ አቶ ሳሙኤል የተገደለው ጥብቅና ቆሞለት ከነበረ አርሶ አደር ጋር በፈጠሩት አለመግባባት እንደነበር ቢሆንም፣ ፍርድ ቤቱ ገዳዩ የቅጣት ማቅለያ እንዲያቀርብ ሲጠይቀው፣ በደብረ ማርቆስ ከተማ ቤት ተከራይቶ የቀን ሥራ እየሠራ ቤተሰቦቹን የሚያስተዳድር መሆኑን በመግለጽ ቅጣቱ እንዲቀልለት ማመልከቱ ተነግሯል፡፡ በመሆኑም ገዳይ መሆኑ የተረጋገጠበት ፍርደኛ፣ ከአርሶ አደርነት እንዴት የቀን ሠራተኛ ሊሆን እንደቻለ የሰማያዊ ፓርቲ አመራሮች ግራ መጋባታቸውን ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ በዕለቱ በችሎት ከተገኙት ቤተሰቦቹና የችሎቱ ታዳሚዎች እንደተረዱት፣ የወንጀሉ አፈጻጸም አልተገለጸም፡፡ ገደለ የተባለው ግለሰብ ሟችን አያውቀውም ብለው፣ በወቅቱ ወንጀሉን አብረው የፈጸሙ ተባባሪዎች እንዳልተያዙ የተገለጸ ቢሆንም፣ ክትትል ተደርጎ የእነሱ መያዝና አለመያዝ ሳይረጋገጥ፣ በጥድፊያ የቅጣት ውሳኔ መስጠቱ በራሱ የሚያሳየው ነገር እንዳለ አስረድተዋል፡፡
የፓርቲያቸው አባል የተገደለበት ሁኔታ የተቀነባበረና ሊድበሰበስ የማይችል መሆኑን የሚገልጹት ሊቀመንበሩ፣ የወንጀል ሒደቱ በትክክል እንዳልተጣራ ፍርድ ቤቱ እንኳን ከሰጠው ፍርድ መረዳት እንደሚቻል ተናግረዋል፡፡
ሟች አቶ ሳሙኤል አወቀ እነማን እየተከታተሉት እንደሆነ፣ ሊገደል እንደሚችል፣ እሱ ቢሞትም ትግሉ እንደሚቀጥል ጽፎና አሳውቆ መሞቱን የጠቆሙት ኢንጂነር ይልቃል፣ አንድ ሰው የማያውቀውን ሰው ሊገድል እንደማይችል ገልጸዋል፡፡ ‹‹የተፈጸመው ድርጊት ራስን ማታለልና አገርን ማዋረድ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ቤተሰቦቹና ሕዝቡ በጣም ማዘናቸውንም አክለዋል፡፡
ገዳይ ተቀበል ገዱ ወንጀሉን ሲፈጽም የአካባቢው ነዋሪዎች ጮኸው እጅ ከፍንጅ እንደያዙት የገለጹት ደግሞ፣ የአማራ ብሔራዊ ክልል መንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ንጉሡ ጥላሁን ናቸው፡፡
በፖሊስ ተጣርቶና ፍርድ ቤቱ በምስክሮች አረጋግጦ ተገቢ ነው ያለውን ቅጣት መወሰኑን የገለጹት ኃላፊው፣ አንዳንድ ወገኖችና የፓርቲው አመራሮች ግድያውን ከፖለቲካ ጋር ለማገናኘት የሚያደርጉት ጥረት ተገቢነት እንደሌለው አስታውቀዋል፡፡
ጉዳዩን ከምርጫ ጋር ለማያያዝ ቢሞከርም ሁሉም ነገር ከተጠናቀቀ በኋላ የተፈጸመ መሆኑን የጠቆሙት አቶ ንጉሡ፣ ሰማያዊ ፓርቲ በምርጫው ያጣውን የኅብረተሰቡን ውሳኔ (ድምፅ) ወደጎን በመተው ሰበብ እየፈለገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ ሰላማዊውን ሕዝብ ሰላም ለመንሳትና የእርስ በርስ ቅራኔ ለመፍጠር ካልሆነ በስተቀር፣ ወንጀሉን የፈጸመው አካል በምስክር ተረጋግጦበት ቅጣቱን ማግኘቱን አስረድተዋል፡፡ ገዳይ በደብረ ማርቆስ ከተማ ቤት ተከራይቶ የቀን ሥራ በመሥራት ወንድሞቹን እንደሚያስተዳድር አቶ ንጉሡም አረጋግጠዋል፡፡
የደብረ ማርቆስ ከፍተኛ ፍርድ ቤት በሰጠው የጽኑ እሥራት ቅጣት ላይ አስተያየት የሰጡ ደግሞ፣ ድርጊቱ በተፈጸመ በ17 ቀናት ውስጥ የቅጣት ውሳኔ መሰጠቱ ጥሩ ቢሆንም፣ ተመሳሳይ ወንጀል ፈጽመው ለዓመታት ውሳኔ ሳይሰጥባቸው በየማረሚያ ቤቱ ያሉትን ተጠርጣሪዎች ሲያስቡ ግን፣ ጥርጣሬ እንደፈጠረባቸው ተናግረዋል፡፡ አንድ ሰው በወንጀል ተጠርጥሮ ሲታሰር፣ ፖሊስ ተጨማሪ ምርመራ ለማድረግ ዝቅተኛ የሚጠይቀው የምርመራ ጊዜ 14 ቀናት በተለመደበት ሁኔታ፣ ይኼኛው የክስ ሒደት በ17 ቀናት ውስጥ መፈጸሙ ግራ እንዳጋባቸው ተናግረዋል፡፡ አቶ ንጉሡ ግን ወንጀለኛው እጅ ከፍንጅ የተያዘና ሁሉም ማስረጃ በአንድ ጊዜ በአጭር ቀናት በመሟላቱ፣ ተገቢ ውሳኔ መሰጠቱን ገልጸው አስተያየት ሰጪዎቹን ተቃውመዋል፡፡