– በዓመት ከ125 ብር እስከ 2,500 ብር ይከፈላል
በአገሪቱ በሥራ ላይ ያሉ ተሽከርካሪዎች ለሚጠቀሙበት መንገድ ማደሻ ወይም መጠገኛ የሚውል ክፍያ ከሐምሌ 1 ቀን 2007 ዓ.ም. ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚሆን፣ የሚኒስትሮች ምክር ቤት በደንብ ቁጥር 340/2007 መደንገጉን ትራንስፖርት ባለሥልጣንና የመንገድ ፈንድ ጽሕፈት ቤት በጋራ ይፋ አደረጉ፡፡
ባለሥልጣኑና ጽሕፈት ቤቱ በጋራ ይፋ ባደረጉት መግለጫ እንዳስታወቁት፣ ተሽከርካሪዎቹ እንደ ክብደት መጠናቸው ክፍያ ይፈጽማሉ፡፡ እስከ አምስት ሰዎች የሚጭን ተሽከርካሪ 125 ብር በዓመት ሲከፍል፣ 180 ኩንታል የሚጭን ተሽከርካሪ ደግሞ 2,500 ብር በዓመት ይከፍላል፡፡ ሌሎች ተሽከርካሪዎችም እንደ ክብደት መጠናቸው ክፍያ ይፈጽማሉ፡፡
የትራንስፖርት ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ ካሳሁን ኃይለ ማርያምና የመንገድ ፈንድ ጽሕፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር አቶ ረሽድ መሐመድ በጋራ በሰጡት መግለጫ እንዳስታወቁት፣ ተሽከርካሪዎቹ ክፍያውን የሚፈጽሙት ዓመታዊ የቴክኒክ ምርመራ በሚያደርጉበት ወቅት ነው፡፡
ለመንገድ ጥገና በዓመት ከ2.5 ቢሊዮን እስከ ሦስት ቢሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ የጠቆሙት አቶ ረሽድ፣ እስካሁን ባለው አሠራር ከ1.5 ቢሊዮን እስከ 1.6 ቢሊዮን ብር ብቻ በጀት ስለሚያዝ፣ የተፈለገውን ያህል መሥራት እንዳልተቻለ ጠቁመዋል፡፡
በአዲሱ አሠራር በዓመት ከ100 ሚሊዮን እስከ 150 ሚሊዮን ብር ለመሰብሰብ መታቀዱንም ጠቁመዋል፡፡ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ደንቡን ያፀደቀው የካቲት 16 ቀን 2007 ዓ.ም. ቢሆንም፣ ቀደም ሲል ይደረጉ የነበሩ ዝግጅትና ተጠናቀው ወደ ትግበራ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡ ክፍያውን ያልፈጸመ አሽከርካሪ ቦሎ ስለማይሰጠው፣ ሳይከፍል ማሽከርከር እንደማይችልም አስረድተዋል፡፡