– ከ17 ዓመታት እስከ ዕድሜ ልክ እስራት ተፈረደባቸው
ሃና ላላንጎ የተባለችውንና 16 ዓመቷ እንደሆነ የተነገረውን ታዳጊ፣ አስገድደውና ተፈራርቀው በመድፈር ለሞት መዳረጋቸው ተረጋግጦ ጥፋተኛ የተባሉት የታክሲ ሾፌሮችና ረዳቶቻቸው፣ ግንቦት 14 ቀን 2007 ዓ.ም. ከ17 ዓመታት እስከ ዕድሜ ልክ ጽኑ እስራት ተፈረደባቸው፡፡
የክስ ሒደቱን በዝግ ችሎት ሲሰማና ሲመረምር የከረመው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሦስተኛ ወንጀል ችሎት በአብላጫ ድምፅ በዕድሜ ልክ ጽኑ እስራት እንዲቀጡ የፈረደባቸው፣ አንደኛ ተከሳሽ ሳምሶን ስለሺና ሁለተኛ ተከሳሽ በዛብህ ገብረ ማርያም ናቸው፡፡
እንዳልተማረና ነገሮችን ማገናዘብ እንደማይችል የቅጣት ማቅለያ ቢያቀርብም፣ በማስረጃ የተደገፈ ባለመሆኑ ፍርድ ቤቱ ያልተቀበለው ሦስተኛ ተከሳሽ በቃሉ ገብረ መድኅን በ17 ዓመታት ጽኑ እስራት እንዲቀጣ ተፈርዶበታል፡፡ አራተኛው ተከሳሽ ኤፍሬም አየለ በ20 ዓመታት ጽኑ እስራት፣ አምስተኛው ተከሳሽ ተመስገን ፀጋዬ በ18 ዓመታት ጽኑ እስራት እንዲቀጡ ፍርድ ቤቱ በልዩነት ፍርድ ሰጥቷል፡፡
ፍርደኞቹ ከዚህ በፊትም የተለያዩ ወንጀሎችን ፈጽመው የተቀጡ መሆናቸውን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡ ዓቃቤ ሕግ ለቅጣት ማክበጃ ባቀረበው ሰነድ ላይ እንደተረጋገጠው አንደኛ ተከሳሽ በቅሚያ፣ ሁለተኛ ተከሳሽ አስገድዶ በመድፈር፣ ሦስተኛ ተከሳሽ ደግሞ በስርቆት ተፈርዶባቸው የነበረ ሲሆን፣ ሁሉም ፍርደኞች ቀደም ብሎ የተፈረደባቸውን ቅጣት ፈጽመው ከወጡ አምስት ዓመታት እንኳን ሳይቆዩ፣ በሃና ላይ ሌላ የወንጀል ድርጊት በመፈጸማቸው ቅጣቱን ከፍ እንዳደረገባቸውም ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡
18 ዓመት ያልሞላትንና ልዩ ጥበቃ የምትፈልግን ታዳጊ፣ ጭካኔ በተሞላበትና ለሕሊና (ሞራል) ተቃራኒ በሆነ መንገድ ተፈራርቀው በመድፈርና ከፍተኛ ደም እየፈሰሳት መንገድ ላይ አውጥተው በመጣል ከባድ ወንጀል መፈጸማቸውን፣ ዓቃቤ ሕግ ባቀረበባቸው የሰውና የሰነድ ማስረጃዎች መረጋገጡን ፍርድ ቤቱ በአብላጫ ድምፅ አስረድቷል፡፡
ፍርድ ቤቱ ክስ ከመስማት እስከ ውሳኔ (ጥፋተኛ እስከተባሉበት) ድረስ ችሎቱን ዝግ አድርጎ የነበረ ቢሆንም፣ ፍርዱን ግን በግልጽ ችሎት ወስኗል፡፡
ሃና ላላንጎ በመስከረም ወር 2007 ዓ.ም. ትምህርት ቤት ውላ ስትመለስ፣ በኮልፌ ቀራኒዮ ክፍለ ከተማ አየር ጤና አካባቢ ስትደርስ፣ አንድ ሚኒባስ የያዘ ወጣት “እንሸኝሽ” ብሎ ካስገባት በኋላ፣ ከረዳቱ ጋር በመሆን ወደ ጦር ኃይሎች አካባቢ ይዘዋት ይሄዳሉ፡፡ አንድ ቤት ውስጥ ይዘዋት ካመሻሹ በኋላ፣ በዚያው ክፍለ ከተማ ከቀራኒዮ መድኃኒዓለም ከፍ ብሎ ታጠቅ መንገድ ላይ ይዘዋት በመሄድ፣ ጓደኛቸው በተከራየበት አንድ ትልቅ ግቢ ውስጥ ባለ አንድ ክፍል ቤት ይዘዋት እንደገቡ፣ ፖሊስ በጊዜ ቀጠሮው ወቅት በግቢው የነበሩ እማኞች በመጥቀስ አስረድቷል፡፡
እንደ ፖሊስ የምርመራ ውጤት፣ ሃናን ከወሰዷት ሾፌርና ረዳቱ በተጨማሪ ሌሎች ሦስት ሰዎች እዚያው ስለነበሩ ሌሊቱን ለአምስት እየተፈራረቁ እንደደፈሯት፣ ሃና በመጨረሻዎቹ ቀናት እንደተናገረችም አመልክቷል፡፡ ለአምስት ተከታታይ ቀናት ባደረሱባት የመድፈር ጥቃት ደም ሲፈሳት፣ ጦር ኃይሎች አካባቢ ሙሉ ወንጌል ቤተ ክርስቲያን አጥር ሥር ተጥላ መገኘቷም በወቅቱ ተነግሯል፡፡
እህትና ወንድሟ ጦር ኃይሎች አካባቢ እንዳገኟት ወደ አለርት ሆስፒታል የወሰዷት ቢሆንም፣ በቂ ሕክምና ሳታገኝ ቆይታ ወደ ጥቁር አንበሳ ስፔሻላይዝድ ሪፈራል ሆስፒታል ሪፈር ብትደረግም፣ በተመሳሳይ ሁኔታ ያለምንም ሕክምና ወደ ጋንዲ መታሰቢያ ሆስፒታል ሪፈር መደረጓን መዘገቡ ይታወሳል፡፡ ጋንዲ ሆስፒታልም ወደ ዘውዲቱ መታሰቢያ ሆስፒታል ሪፈር አድርጓት፣ ዘውዲቱ ሆስፒታል የቻለውን ዕርዳታ እንዳደረገላት ተገልጿል፡፡ ሐና በደረሰባት ጉዳት አፋጣኝ የሕክምና ዕርዳታ ባለማግኘቷ፣ ብዙ ደም ፈሷት ስለነበርና ጉዳቱም ወደ ኢንፌክሽን ተቀይሮ ስለነበር ሕይወቷ ሊተርፍ አልቻለም፡፡ መስከረም 22 ቀን 2007 ዓ.ም. ከዚህ ዓለም በሞት ተለይታለች፡፡