በሚቀጥሉት 15 ዓመታት፣ በምግብ ዕጦት የሚጎዳ ሕፃን እንዳይኖር የማድረግን ግብ ላስቀመጠው የሰቆጣ ስምምነት የመጀመሪያ ዙር ትግበራ፣ የሦስት ሚሊዮን ዶላር ድጋፍ መገኘቱን ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
በአማራና በትግራይ ክልሎች አዋሳኝ ላይ በሚገኘው የተከዜ ተፋሰስ አካባቢ፣ ድርቅ ክፉኛ ባጠቃቸው 30 ወረዳዎች ውስጥ ለሚተገበረው ፕሮጀክት የመጀመሪያ ዙር ሥራ ማከናወኛ የገንዘብ ድጋፍ ያደረገው፣ እንግሊዝ የሚገኘው ቢግ ዊን ፊላንትሮፒ የተባለ ድርጅት መሆኑን የሚኒስቴሩ ከፍተኛ አማካሪው ዶ/ር ፍሬው ለማ ገልጸዋል፡፡
ስምምነቱን ተግባራዊ የሚያደርጉ ቡድኖች በፌዴራል ደረጃ እንዲሁም በአማራና በትግራይ ክልሎች እንደተቋቋሙ፣ ከእነዚህም መካከል በሁለቱ ክልሎች የተቋቋሙ ቡድኖችን የሚያንቀሳቅሱ የጤና ሙያተኞች፣ የውኃና የግብርና ፕሮግራም ማኔጀሮች፣ እንዲሁም ፕሮግራም ተንታኞች በመቀጠር ላይ መሆናቸውንም አማካሪው ተናግረዋል፡፡
በተጠቀሱት ወረዳዎች የሚካሄደው የመጀመሪያ ዙር የሥራ አፈጻጸም ከታየ በኋላ፣ ተሞክሮውን በመጠቀም በሌሎች ክልሎች ሁለተኛው ዙር ይቀጥላልም ብለዋል፡፡
የሰቆጣው ስምምነት ለአገር ውስጥና ለዓለም ኅብረተሰብ ይፋ የሆነው በ2007 ዓ.ም. ነሐሴ ላይ መሆኑን፣ በዚህም ሥነ ሥርዓት ላይ የሁሉም ክልሎች አመራሮች ተገኝተው ስምምነቱን መፈረማቸውን ወ/ሮ ፍሬዓለም ሽባባው የስምምነቱ ሐሳብ አመንጪ፣ አርቃቂና የኢትዮጵያ ስኩል ሚል ኢንሼቲቭ ዋና ዳይሬክተር ገልጸዋል፡፡
ከጽንስ ጀምሮ ሕፃናት ተወልደው ሁለት ዓመት እስኪሞላቸው ባሉት 1,000 ቀናት ውስጥ እናትየዋ፣ በኋላም ልጅ መውሰድ ስላለባቸው የተመጣጠነ ምግብ፣ ለሕፃኑ የሚያስፈልገውን የእናት ጡት ወተትና ተጨማሪ የምግብ ዓይነቶች በተመለከተ በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች እየተናኘ ያለው ማስታወቂያም የስምምነቱ አካል እንደሆነ አመልክተዋል፡፡