– ከ1,100 በላይ ብሔራዊና የክለብ አትሌቶች ይሳተፋሉ
በኢትዮጵያ አትለቲክስ ፌዴሬሽን አዘጋጅነት በየዓመቱ የሚካሔደው 32ኛው የጃንሜዳ ኢንተርናሽናል አገር አቋራጭ የሩጫ ውድድር ዛሬ ይደረጋል፡፡ 37 ክለቦች፣ የብሔራዊ ቡድን አትሌቶች፣ ከዘጠኝ ክልሎችና ከሁለቱ የከተማ አስተዳደሮች እንዲሁም በግል ከሚወዳደሩ የተውጣጡ ከ1,100 በላይ አትሌቶች ይሳተፋሉ፡፡ ፌዴሬሽኑ 405,000 ብር ለዝግጅቱ መመደቡም ታውቋል፡፡
ብሔራዊ ፌዴሬሽኑ ባለፈው ሐሙስ ጥር 21 ቀን 2007 ዓ.ም. በብሔራዊ ሆቴል በሰጠው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ ውድድሩ በ12 ኪሎ ሜትር አዋቂ ወንዶች፣ 8 ኪሎ ሜትር አዋቂ ሴቶችና ወጣት ወንዶች እንዲሁም፣ በ6 ኪሎ ሜትር ወጣት ሴቶች ይደረጋል፡፡ ለቡድንና ለግል አሸናፊዎች 125,000 ብር የገንዘብ ሽልማት ተዘጋጅቷል፡፡
የፌዴሬሽኑ የጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቢልልኝ መቆያና የቴክኒክ ዳይሬክተሩ አቶ ዱቤ ጅሎ በጋራ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ በሁለቱም ፆታ በአዋቂዎች ከአንደኛ እስከ አምስተኛ፣ በወጣቶች ደግሞ እስከ ስድስተኛ ደረጃ ይዘው የሚያጠናቅቁ አትሌቶች በመጪው መጋቢት መገባደጃ በቻይና በሚደረገው የዓለም አገር አቋራጭ ውድድር ላይ አገሪቱን እንደሚወክሉ ተናግረዋል፡፡ በውድድሩ ላይ ከሚሳተፉት ታላላቅ የክለብ አትሌቶች ውስጥ ቦንሳ ዳዲ፣ ገነት ያለው፣ ጎይቶም ገብረሥላሴ፣ ሙክታር እንድሪስ፣ ሕይወት አያሌውና ሐጎስ ገብረሕይወት ይገኙበታል፡፡