የዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር (አይኤኤኤፍ) በወርቅ ደረጃ ከሚመድባቸው ታላላቅ የማራቶን ውድድሮች ዱባይ ማራቶን ይጠቀሳል፡፡ ጥር 15 ቀን 2007 ዓ.ም. በተደረገው የዱባይ ማራቶን በወንዶች ኢትዮጵያውያኑ ከአንደኛ እስከ አሥረኛ ያለው ደረጃ በመያዝ ጥንካሬያቸውን ሲያስመሰክሩ፣ ለማ ብርሃኑ በወንዶች፣ አሰለፈች መርጊያ ደግሞ በሴቶች አሸናፊ ሆነዋል፡፡ ባለፈው ዓርብ በዓመታዊ የዱባይ ማራቶን በወንዶች አሸናፊው ለሚ ብርሃኑ ርቀቱን ለማጠናቀቅ 2 ሰዓት 05 ደቂቃ፣ 28 ሰኮንድ ሲወስድበት፣ ሁለተኛና ሦስተኛ በመሆን ያጠናቀቁት ሌሊት ዴሲሳና ደርቤ ሮቤ 2 ሰዓት 06 ደቂቃ፣ 24 ሰኮንድና 2 ሰዓ፣ 06 ደቂቃ 38 ሰኮንድ አጠናቅቀዋል፡፡ በሴቶች በተደረገው ተመሳሳይ የማራቶን ውድድር አሰለፈች መርጊያ 2 ሰዓት 20 ደቂቃ 02 ሰኮንድ በሆነ ጊዜ ስታጠናቅቅ፣ ሁለተኛና ሦስተኛ በመሆን የጨረሱት ኬንያውያኑ ቸሮን ኪልፕሮኖና ሉሲ ዋንጋይ ካቡ 2 ሰዓት፣ 20 ደቂቃ፣ 03 ሰኮንድና 2 ሰዓት 20 ደቂቃ 21 ሰኮንድ ነው፡፡ የአይኤኤኤፍ ድረ ገፅ እንደሚያመለክተው ከሆነ በዘንድሮው የዱባይ ማራቶን ኢትዮጵያውያኑ ፈይሳ ለማ፣ ሲሳል ለማ፣ በዙ ወርቁ፣ ቸሌ ደቻሳ፣ ግርማይ ብርሃኑ፣ አዱኛ ታከለና አንዱዓለም በላይ ከአራተኛ እስከ አሥረኛ ያለውን ደረጃ ይዘው አጠናቀዋል፡፡ ለአሸናፊነት ቅድመ ግምት ተሰጥቶት በሩጫው የተሳተፈው ቀነኒሳ በቀለ ከ30 ኪሎ ሜትር በኋላ አቋርጦ መውጣቱ ተዘግቧል፡፡ የውድድሩ አሸናፊዎች እያንዳንዳቸው 250,000 ዶላር እንደሚያገኙም መረጃው አመላክቷል፡፡