- ተፈናቃዮች በሕክምና ዕጦትና በደኅንነት ሥጋት ችግር ውስጥ ገብተዋል
በሶማሌና በኦሮሚያ ክልሎች አዋሳኝ በተነሳ ግጭት እስካሁን ትክክለኛው የተፈናቃዮች ቁጥር ባይታወቅም፣ የአዳማ ከተማ አስተዳደር ከሰባት ሺሕ በላይ አባወራዎችን መቀበሉን አስታውቋል፡፡
የከተማው ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ችግሩ ከተፈጠረ ጀምሮ የከተማ አስተዳደሩ ተፈናቃዮችን በመቀበል ላይ መሆኑንና ካሉት 18 ቀበሌዎች በዘጠኙ ከግለሰብ፣ ከዕድር እንዲሁም ከማኅበራት ጋር በመተባበር መጠለያ አዘጋጅተዋል፡፡
ከተማው ተፈናቃዮችን ለማስተዳደር ከ31 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ማድረጉን በመናገርም፣ የተፈጠረውን ችግር ሆደ ሰፊና ትዕግሥተኛ ሆነው በማለፍ፣ አጥፊዎች ለሕግ ቀርበው፣ ተፈናቃዮችም ወደ ቀድሞው ሁኔታ እስኪመለሱ ከክልሉ መንግሥት በተጨማሪ ኅብረተሰቡ እያደረገ ያለውን ድጋፍ አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ይህንኑ ተከትሎ የመንፈስ ቅዱስ ዓለም አቀፍ ቤተ ክርስቲያን ለ800 ተፈናቃዮች የሚሆኑ የተለያዩ ቁሳቁሶችን በከተማው ለተጠለሉ ተፈናቃዮች እንዲውል አስረክቧል፡፡
‹‹ላቀው ግቢ››
ከአዲስ አበባ 100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘው አዳማ ከተማ በሁለቱ ክልሎች በተነሳው ግጭት ሳቢያ የተፈናቀሉ የክልሉ ተወላጆችን በከተማዋ በሚገኙ ዘጠኝ መጠለያ ጣቢያዎች እያስተናገደች ነው፡፡ በውስጡ 120 አባወራዎችን ካስጠለለው አንዱ አቶ ላቀው ግቢ ይባላል፡፡
ይህ ከግለሰብ በተገኘ መጠለያ ውስጥ ግንባታ እየተካሄደበት ነው፡፡ ሴቶችና ሕፃናት በብዛት ይታያሉ፡፡ ደስተኛ የሚመስሉ ፊቶች ቢታዩም፣ ጠጋ ብሎ ላዋራቸው ነገሩ ሌላ ነው፡፡ የሆነው ሁሉ በድንገት ግራ እንዳጋባቸው ይገልጻሉ፡፡ ቤት ንብረታቸውንና ቤተሰባቸውን ማጣታቸውን ለማመን እንዳቃታቸው ይናገራሉ፡፡
የሴቶቹ አለባበስ የሕፃናቱ በሶማሊኛ ማውራት እንዲሁም የወንዶቹ የፀጉር አቆራረጥ መጠለያውን የሶማሌ ተፈናቃዮች ያስመስላል፡፡ ተፈናቃዮቹ ቁጭ ብለው በመዋላቸው መሰላቸት ይታይባቸዋል፡፡ በፊት በጫት፣ በወርቅ፣ በሱቅና በመሳሰሉት የንግድ ሥራ ላይ በመሰማራት በቀን 16 ሰዓታትን በሥራ ያሰልፉ የነበረ በመሆኑ፣ ያለሥራ መቀመጣቸው እንደከበዳቸው ይናገራሉ፡፡ መጠለያው ግንባታ እየተካሄደበት በመሆኑም ለመኖሪያ አመቺ እንዳልሆነ ይጠቁማሉ፡፡
አቶ መሐመድ ኑሮ ይባላሉ፡፡ የተፈናቀሉት ከቶጐጫሌ 02 ቀበሌ ሲሆን፣ ወደ አዳማው መጠለያ የገቡት ነፍሰ ጡር ባለቤትቸውንና አንድ ልጃቸውን ይዘው ነው፡፡ እርጉዝዋ በወቅቱ በደረሰባት የመፈንከት አደጋ ቁስለኛ ነች፡፡ በመጠለያው ፈጣን ሕክምና ባለመኖሩ ሚስታቸው ክትትል ማቋረጧን፣ መውለጃዋ በመቅረቡ ደግሞ እንደተጨነቁ ይናገራሉ፡፡ አንዳንዴ እያመማት ወደ ግል ሆስፒታል እንደሚወስዷትና ከባጃጅ ኮንትራት ጀምሮ ከፍተኛ ወጪ በማውጣታቸው ባዶ እጃቸውን መቅረታቸውን ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
እሳቸውንና ሌሎቹን ተፈናቃዮች ሥጋት ውስጥ የከተተው ጉዳይ ደግሞ የደኅንነት ነው፡፡ በመጠለያ ጣቢያው ወጪ ገቢው አይታወቅም፡፡ ‹‹ከምናውቃቸው ሰዎች ውጭ ይገባሉ ይወጣሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ልጆቻችንን እየጠበቅን ከመውጣት ተቆጥበን እንገኛለን፡፡ የፖሊስ ጥበቃ ስለሌለን ዛሬም ችግር ይደርስብናል ብለን ሥጋት ውስጥ ነን›› በማለት አብራርተዋል፡፡
የመጠለያው አስተባባሪ አቶ አባዲ ኮራ ለተፈናቃዮች የሕክምና እጥረት እንዳለ ይጋራሉ፡፡ ኅብረተሰቡ በዕለት ተዕለት ምግብ ከማቅረብ ጀምሮ በጥሬ 34 ሺሕ ብር በማውጣት እየደገፈ ሲሆን፣ መንግሥት ነፃ ሕክምና ባለማቅረቡ ተፈናቃዮቹ ከባድ ችግር ላይ እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡ መጠለያ ጣቢያው ከአቅሙ በላይ እያስተናገደ እንደሚገኝም አክለዋል፡፡
የቤተ ክርስቲያኑ መሥራች ነብይ ታምራት ደምስስ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከ150 ሺሕ ብር በላይ የሚያወጣውን ዕርዳታ የለገሱት ሌላ ሥራ ለመሥራት ታቅዶ ከምዕመናኑ ከተሰበሰበ ገንዘብ እንደሆነ የሕዝብ ችግር እንደሚበልጥ በማሰብ ወደዚህ እንዳዞሩት ተናግረዋል፡፡
ሪፖርተር በቅርቡ በተፈናቃዮች ላይ በሠራው ዘገባ፣ የጉዳዩ ድንገተኛ መሆን የማኅበራዊ ኑሮ ቀውስ እንዳስከተለ አሳይቷል፡፡ በመጠለያ ጣቢያ ያሉትም ወደ መጡበት መመለስ እንደማይፈልጉ ይገልጻሉ፡፡ ታዲያ ለዘለቄታው እንዴት ነው ማቋቋም የሚቻለው? ምን አስባችኋል? በሚል ለከንቲባዋ ላቀረብነው ጥያቄ፣ ‹‹ወደ መኖሪያ መንደራቸው በሚመለሱበት ሁኔታ እየተሠራ ነው፡፡ ሌላው ለዘለቄታውም ነው፡፡ አንመለስም ካሉም ለዘለቄታው አሁን ያለውን ችግር እየፈታን እናመቻቻለን ብለዋል፡፡