አገር በቀል የኤሌክትሪክ አምራቾችን፣ አስመጭዎችንና አከፋፋዮችን ሚያገናኝና አሁናዊ መረጃዎችን ለመለዋወጥ የሚያስችል መድረክ ሊዘጋጅ ነው፡፡
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪካል መሐንዲሶች ማኅበር ኮሪኢ ኤቨንትስ ጋር በመተባበር በመጭው በየካቲት ወር ለሦስት ተከታታይ ቀናት በሚያካሂደው መድረክ፣ ከ300 በላይ በኤሌክትሪክ ዘርፍ የተሰማሩ አምራቾች፣ አስመጭዎችና አቅራቢዎች ይሳተፋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
መድረኩ ባለሙያዎች ወቅታዊ ዓለም አቀፍ የኤሌክትሪክ ቴክኖሎጂ መረጃዎች የሚለዋውጡበትና በቀጣይ የተጠናከረ የሥራ ዕድል የሚፈጥሩበት እንደሚሆን የኮሪኦ ኤቨንትስ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ አብዱልፈታህ ዓሊ ተናግረዋል፡፡
ከ2002 ዓ.ም. ጀምሮ ተመሳሳይ መድረኮች ሲካሄዱ እንደነበር የተናገሩት ደግሞ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪካል መሐንዲሶች ማኅበር የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አቶ አስተራይ ጽጌ ናቸው፡፡
በየዓመቱ በርካታ መሐንዲሶች ይመረቃሉ፣ ነገር ግን ብዙዎቹ የሥራ ዕድል አያገኙም ያሉት አቶ አስተራይ፣ በሚካሄደው ኤግዚቢሽን ላይ የሚሳተፉ የማኅበሩ አባላት የሥራ ዕድልን ከመፍጠር፣ አቅማቸውን ከማጎልበትና የልምድ ልውውጥ ከማድረግ አንፃር ያግዛል ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ የኤሌክትሪካል ምህንድስና ትምህርት ክፍል በኤሌክትሮኒክስና በመሳሰሉት ዘርፎች የተመረቁ፣ በማኅበሩ ጥላ ሥር ሆነው አስተዋጽኦ እንዲያደርጉና የጋራ ችግሮችን በጋራ እንዲቀርፉም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
በአብዛኛው የሲቪል ማሐንዲሶች ሥራ ከወሰዱ ባኋላ የኤሌክትሪክ ሥራውን ብቃት ለሌላቸው ባለሙያዎች አሳልፈው ይሰጣሉ ያሉት አቶ አስተራይ፣ ከኤሌክትሪክ በሚነሳ አደጋ ብዙ ንብረትና የሰው ሕይወትም ጭምር እንዲጠፋ ምክንያት እንደሚሆን ጠቁመዋል፡፡
ችግሩ ከብቃት ማነስ የሚፈጠር በመሆኑ በተለይ በሕንፃ ላይ የሚዘረጉ የኤሌክትሪክ ገመዶች አግባብ ባለው ባለሙያ እንዲዘረጉ በሚል ሲታገሉ መቆየታቸውን፣ ከዚህ በመነሳትም የኤሌክትሪክ ሥራ ለኤሌክትሪክ ተቋራጮች ብቻ እንዲሰጥ የሚያስችል የሕግ ማዕቀፍ እንዲዘጋጅ መደረጉን አቶ አስተራይ አብራርተዋል፡፡
በኤሌክትሪክ ዘርፍ የተሰማሩ አምራቾች፣ አስመጭዎችና አቅራቢዎችን ከተጠቃሚዎችና ከባለድርሻ አካላት ጋር ያገናኛል ተብሎ የሚጠበቀው የኤግዚቢሽን መድረክ ከየካቲት 13 እስከ 16 ቀን 2016 ዓ.ም. ድረስ የሚካሄድ ይሆናል፡፡
በዝግጅቱ ላይ የተለያዩ ሲምፖዚየሞችና ሲሚናሮች የሚቀርቡና ከዘርፉ ጋር ግንኙነት አላቸው የተባሉ በኤሌክትሪሲቲ ሥር የሚገኙ እንደ ኤሌክትሪክ፣ ኤሌክትሮኒክስ፣ ኤሌክትሮ ሜካኒካል፣ ታዳሽ ኢነርጂ የመንገድ መብራት ቁጥጥር አገልግሎት ሥርዓትና የእሳት አደጋና መከላከል እንደሚገኙ አቶ አብዱልፈታህ አስታውቀዋል፡፡