- አብዛኛው ማኅበረሰብ የሳይበር ደኅንነት ዕውቀቱ ዝቅተኛ ነው ተባለ
የኢንፎርሜሽን መረብ ደኅንነት አስተዳደር (ኢንሳ) በተለያዩ ጊዜያት የግንዛቤ ማስጨበጫ ፕሮግራሞች ቢያካሂድም፣ በተገልጋዮች ዘንድ ትኩረት እንዳልተሰጠው የአስተዳደሩ ኃላፊዎች ገለጹ፡፡
ኢንሳ በቅርቡ ባጠናው ጥናት መሠረት በኢትዮጵያ 35 በመቶ የማኅበረሰቡ ክፍል ብቻ የሳይበር ደኅንነት ግንዛቤ አለው፡፡ ውጤቱን አስመልክቶ የተቋሙ ዋና ዳይሬክተር አቶ ሰለሞን ሶካ ለጋዜጠኞች እንደገለጹት፣ በሳይበር ደኅንነት ምኅዳር ላይ የማኅበረሰቡ ግንዛቤ ማነስ ስላለ የተቋሙ ጥረቶች ትኩረት አልተሰጣቸውም፡፡
ሰኞ ጥቅምት 19 ቀን 2016 ዓ.ም. ኢንሳ በግዮን ሆቴል ይፋ ያደረገውና ‹‹ብሔራዊ የሳይበር ደኅንነት ንቃተ ህሊና›› በሚል ያዘጋጀው የጥናት ውጤት እንደሚያሳየው፣ በኢትዮጵያ ካሉት 33.9 ሚሊዮን የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ውስጥ፣ 65 በመቶ ያህሉ የሳይበር ደኅንነት ዕውቀታቸው ዝቅተኛ ነው፡፡
የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ቁጥር እየጨመረ የመጣ ቢሆንም፣ ጥናቱ ይፋ እንዳደረገው፣ የተጠቃሚዎች ንቃተ ህሊና አነስተኛ እንደሆነና ‹‹በጣም ብዙ ሥራ›› እንደሚጠይቅ ነው፡፡
በሁሉም ክልሎች ከሚገኙና በርካታ ሰዎች ከሚኖሩባቸው ከተሞች ናሙናዎችን በመምረጥ ጥናቱ መካሄዱን የገለጹት የኢንሳ የሳይበር ደኅንነት ባለሙያ አቶ አየለ ሙሴ፣ ከፍተኛው መረጃ የተሰበሰበው ከትምህርት ተቋማት መሆኑን፣ በመቀጠልም ከንግድ ሥፍራዎች፣ ከመዝናኛ ሥፍራዎች፣ ከተቋማት ቢሮዎችና ከመኖሪያ አካባቢዎች መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ጥናቱ አጠቃላይ የሳይበር ደኅንነት ንቃተ ህሊና ዕውቀትን በደረጃ ሲተነትን፣ 29.23 በመቶው የማኅበረሰቡ ክፍሎች ምንም ዕውቀት የሌላቸው ሲሆኑ፣ 35.60 በመቶ ደግሞ ዝቅተኛ ዕውቀት እንዳላቸው ነው ያስቀመጠው፡፡ በአንፃሩ ደግሞ 11.75 በመቶ መካከለኛ ዕውቀት ሲኖራቸው፣ 23.40 በመቶ ደግሞ ከፍተኛ ዕውቀት እንዳላቸው አሥፍሯል፡፡ ጥናቱ በድምሩ 65 በመቶ የሚሆኑትን ዕውቀት ከሌላቸውና 35 በመቶ ከሚሆኑት ዕውቀት ካላቸው ጎራ መድቧል፡፡
የዘንድሮው በጀት ዓመት የመጀመርያው ሩብ ዓመት በአገሪቱ ተሞክረው ስለነበሩት የሳይበር ጥቃቶችም አኃዛዊ መረጃ ይፋ ሆኗል፡፡
የድረ ገጾ ጥቃት፣ የመሠረተ ልማት ማቋረጥ፣ ሰርጎ የመግባት ሙከራና የተቋማትን የማኅበራዊ ገጽና ኢሜይሎች ነጠቃ ዓይነት በርካታ የሳይበር ጥቃቶች በሩብ ዓመቱ ተከስተው እንደነበሩ፣ በአጠቃላይ 2,556 ጥቃቶች በሩብ ዓመቱ ማጋጠማቸውን፣ ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ላይ የተከሰቱት ጥቃቶች 1,613 እንደነበሩ ተገልጿል፡፡
ዘንድሮ በርካታ ጥቃቶችና ሙከራዎች ለመከሰታቸው ምክንያት ብለው ዋና ዳይሬክተሩ አቶ ሰለሞን ያስረዱት፣ ኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ እየገነባች በመሆኑና የቴክኖሎጂ አጠቃቀም እያደገ መምጣቱ አንደኛው ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡ ሌላኛው ምክንያትም የኢንሳ የመከላከል ዕድገትና ሽፋን በመስፋቱ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡
‹‹ከዚህ በፊት ቁልፍ የመሠረተ ልማቶች ላይ ብቻ ነበር ትኩረት የምናደርገው፡፡ በዚህኛው ዓመት የመከላከል ሽፋናችን ሰፋ ብሎ በርካታ ተቋማት የዲጂታል ሀብቶቻቸውን እኛ ዘንድ እያስጠበቁ ነው፤›› ሲሉ አቶ ሰለሞን ገልጸዋል፡፡
ተቋሙ በመጀመሪያው ሩብ ዓመት ላይ የተከላከለው የሳይበር ጥቃት ውጤት 97.7 በመቶ ሲሆን፣ እያንዳንዱ ጥቃት ቢደርስ ኖሮ ኢትዮጵያን ምን ያህል ያሳጣታል የሚለውን ዝርዝር የባለሙያ ሥሌት በቀጣይ ይፋ እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡
በባለፈው በጀት ዓመት የተከሰቱት የሳይበር ጥቃቶች ኢትዮጵያን 23.2 ቢሊዮን ብር ሊያሳጧት ይችሉ እንደነበር በባለሙያዎች ተተንትኖ መታወቁን አቶ ሰለሞን አስታውቋል፡፡
ኢንሳ አራተኛውን የሳይበር ደኅንነት ወር በጥቅምት ወር እያከበረ ሲሆን፣ ከወሩ ክንውኖች አንደኛው ሰኞ ዕለት ይፋ የሆነው የጥናቱ ውጤት ነው፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይም የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን አገልግሎት ሚኒስቴር ለገሰ ቱሉ (ዶ/ር) እና የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር አቶ መሐመድ ኢድሪስ ተገኝተዋል፡፡