Monday, December 11, 2023
- Advertisment -
- Advertisment -

በባሕሩ ዘውዴ (ፕሮፌሰር) ‹‹ኅብር ሕይወቴ›› መጽሐፍ ላይ ግላዊ ዕይታ

በዳንኤል በላይነህ

ይኼንን መጽሐፍ አንብቤ ስጨርስ የተሰማኝ ነገር፣ ምናልባት ቀድሞውኑም ይህንን ልጠብቅ አይገባም ነበር የሚል ነው፡፡ ምክንያቱም የደራሲው ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ የተመሰከረላቸው የታሪክ ምሁርና ተመራማሪ እንጂ የልብ ወለድ ደራሲ ወይም የወግ ተራኪ አይደሉምና፡፡ በመጽሐፉ ላይ ያለኝ ምልከታ በምንም መንገድ የባለሙያ ግምገማ አይሆንም፣ ሊሆንም አይችልም፡፡ የእኔ ተራ አስተያየት ነው፣ ግላዊ ዕይታ እንደማለት፡፡ በዚህ መሠረት ስለዚህ መጽሐፍ የእኔ አስተያየት ስለተነሱት ነገሮች፣ ስለትረካውና ስላሳደረብኝ ስሜት በነፃነት ለማጋራት ሲሆን፣ የማነሳቸውም ነጥቦች ያየኋቸውን በሙሉ ሳይሆን፣ የመረጥኳቸውንና ጥቂቶቹን ብቻ ነው፡፡

ስጀምር በቀጥታ ለመናገር በእኔ አስተያየት መጽሐፉ ተሻምቼ ስገዛው ተስፋ አድርጌ እንደነበረው ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ ምናልባት መጀመሪያ እንዳልኩት፣ ብዙም ተስፋ ላደርግ አይገባም ነበር ይሆናል፡፡ ስለዚህ አስተያየቶቼ ማንኛዎቹም ሌሎች መጻሕፍት ላይ ሳቀርባቸው እንደነበሩት ዓይነት የመደበኛ ነፃ አንባቢ የግሌ ምልከታዎች ናቸው፡፡ ይህንን የምለው የፕሮፌሰር ባሕሩን መጽሐፍ እንደ ታሪክ ድርሳን አስተያየት ለመስጠት መሞከር ድፍረት ስለሚሆን ብቻ ሳይሆን፣ ይኼኛው መጽሐፍ የታሪክ ሰነድ ላለመምሰል የተሞከረበት (ሙከራው የተሳካ ባይመስለኝም) ቀለል ያለ የግለ ሕይወት ወግ ነው ብዬ ስላመንኩ ነው፡፡ ምክንያቱም ጥራትም፣ ክብርም፣ ውበትም፣ ዝናም ያላቸው በርካታ መጻሕፍት ሲያቀርቡልንና ሲያስቀርቡልን የኖሩት ባሕሩ ዘውዴ የተዋጣላቸው የታሪክ ምሁር ጸሐፊና ተመራማሪ እንጂ፣ አማላይ የሥነ ጽሑፍ ተራኪ የመሆን ግዴታ ስለሌለባቸው ነው፡፡ ተቆጥረው በማያልቁ ሁነቶች የጻፉልን መጻሕፍትም ስለሌሎች ሰዎች ነው፣ የተጻፉትም በአብዛኛው (ምናልባት በጠቅላላው) ሊባል በሚችል ሁኔታ በአካዴሚያዊ ከባቢ ሁኔታና በአብዛኛውም ለአካዴሚያዊ ማኅረበሰብ ይመስለኛል፡፡ የራሳቸውን ታሪክ ሲጽፉና ለተራዎቹ ሰዎች ሲያቀርቡልን የመጀመሪያቸው ነው፡፡ ይህ በመሆኑም በዚህ መጽሐፋቸው በሁለቱ አቀራረቦች (ለአካዴሚያዊውና ለመደበኛ አንባቢያን በማድረግ) መካከል የሚታየውን ግልጽ  መወላወል ማስቀረት የቻሉ አልመሰለኝም፡፡ በእኔ አስተያየት ትልቁ የመጽሐፉ ችግር ከዚህ የተነሳ ይመስለኛል፡፡ እና መጽሐፉን ያገኘሁት ለመደበኛ አንባብያን የቀረበ የግል ሕይወት ትረካ በመሆንና ለአካዴሚ የቀረበ የምርምር ወረቀት በመሆን መሀል የሚዋልል ሆኖ ነው፡፡ አንዱን ወይም ሌላውን ቢሆንም ምንም አልነበረም፡፡ ችግሩ አንዴ አንደኛውን ሌላ ጊዜ ደግሞ ሌላውን እየመሰለ የቀረበ መሆኑ ነው፡፡

ታሪኩ የራሳቸውም ቢሆን መቼም ያው ታሪክ ነውና እሳቸውም የታሪክ ምሁር ናቸውና ሆን ብለውም ይሁን በሌላ ምክንያት የራሳቸውን የልጅነት ዕድገትና የሥራ ታሪክ ምንም እንኳን ለመደበኛ አንባብያን የተዘጋጀ ሆኖም፣ አካዴሚያዊ አቀራረብ ያለው ቢመስልባቸው ለምን ማለት አይቻልም ይሆናል፡፡ ከዚህ የባሰው ግን መምሰሉ ላይቀር አካዴሚያዊ ለማድረግ የተደረገ በሚመስል ሙከራ ምክንያት ሳይደረጉ የቀሩና (ሳያስፈልጉ የተደረጉም) ነገሮች መጽሐፉን፣ ከዚህም ከዚያም ሳይሆን እንዲዋልል እንዲገደድ ያደረጉበት ሁኔታ መፈጠሩ የሚታይ መሆኑን ነው፡፡  

ለምሳሌ ገና ለጀመረውና ምዕራፎቹ የተደረደሩበትን አግባብ ለሚመለከት መደበኛ አንባቢ ‹‹ምዕራፍ 1›› ከሥር ደግሞ 1.1…፣ 1.2 የሚል አደራደር ሲያይ፣ በተለይ የባሕሩ እንደመሆኑ የጥናት ጽሑፍ እንጂ ባለቤቱ የሕይወታቸውን ታሪክ የተረኩበት ለመደበኛ አንባቢያን የተዘጋጀ አይደለም ብሎ ቢያስብ ሊፈረድበት የሚገባ አይመስለኝም፡፡ እንደዚያ ሲሆን ደግሞ መጽሐፉን ዘልቆ ለማንበብ ላይበረታታ ይችላል፡፡ ያው አካዴሚያዊ ጽሑፎች አሰልቺ ናቸው የሚል ዕሳቤ ስላለ፡፡ አካዴሚያዊነት የጎላበት ይሁን ተብሎ የነበረ ከሆነም፣ አንደኛውኑ እንደዚያ ማድረግ ይሻል ነበር ይሆናል፡፡ ያንን በማድረጋቸውም ምናልባት ቢቀሩባቸው ስልቹ አንባቢያን ነበሩ፡፡

ከዚህ በተጨማሪ በተለይ ባሕሩ ዘውዴን የመሰለ ታላቅ የታሪክ ምሁር የሚጽፈው ምንም ጽሐፉ (የግል ሕይወቱ ታሪክ እንኳን ቢሆን) ከሙያው ጥላ ሊወጣ የማይችልም፣ የማይገባውም መሆኑን ታሳቢ ማድረግም የግድ ነው፡፡ ይህ ማለት ምንም ዓይነት ግለ ታሪክ ቢሆን የጸሐፊው (የባለታሪኩ) ሙያ ላይንፀባረቅበት አይችልም ማለት ነው፡፡ እንደዚያ ሲሆን የሕይወቱን ታሪክ የጻፈው የንግድ፣ የሕክምና የውትድርና፣ ወዘተ ባለሙያ ቢሆን በታሪኩ ፍሰት ውስጥ በሚነሱ ከሙያው ጋር የተያያዙ ጉዳዮች ላይ የተለየ ጥንቃቄ የሚያደርግ (ወይም እንዲያደርግ የሚጠበቅበት) ይመስለኛል፡፡ በዚህ አግባብ የጸሐፊው ሙያ የታሪክ ከሆነ ታሪክ ላይ የበለጠ ጥንቃቄ ሊያደርግ ይጠበቃል ማለት ነው፡፡ ይህኛውም መጽሐፍ ከታሪክ ባለሙያ የቀረበ በመሆኑ በዚያ ረገድ የተለየ ጥንቃቄ ያደርጋል ብሎ መጠበቅ ተፈጥሯዊ ብቻ ነው፡፡ ይልቁንም ፕሮፌሰር ባሕሩን የመሰለ እንኳን በይዘት በአርትኦትና በፊደላት ጥንቃቄም ሳይቀር ፍፁም ሊባል የሚችል ሪከርድ ያለው ሰው፣ የሕይወት ታሪኩን ሲያቀርብልን ስለተራው ሰው ታሪክ አረዳድ ግድ አልነበረውም፣ ወይም የምለው ነገር ‹‹ይታወቃል›› ብሎ አስቧል፣ ወይም ዘሎታል፣ ወይም አምልጦታል ብሎ ለማለፍ አስቸጋሪ ነው፡፡ እንደዚያ የመሰለባቸው አጋጣሚዎች ግን ከበቂ በላይ ናቸው፡፡ ጥቂቶቹን ብቻ ማንሳት ይቻላል፡፡

ለምሳሌ አማርኛ ቋንቋ የአፍ መፍቻቸው ላልሆነ ልጆች ‹‹አማርኛ ማስተማሩ ቀላል እንዳልነበረ›› ሲያትቱ፣ ‹‹በተለይ ራስ ሤላስን የመሰለ ጠጣር መጽሐፍ የምንባብ ማስተማሪያ ባደረገ ሥርዓተ ትምህርት ውስጥ!›› ይሉና፣ ‹‹ራስ ሤላስ›› ምን እንደሆነ፣  ይቅርና በግርጌ ማስታወሻ፣ በቅንፍ እንኳን ሊነግሩን አይቸገሩም፡፡ እኔ ለምሳሌ ‹‹ራስ ሤላስ›› ምን እንደሆነ አሁንም አላውቅም፡፡ ሌላ ቦታ ደግሞ ‹በአፈና የተያዝነው የኢንሹራንሱ ማትያስና እኔ ነበርን›› ይላሉ፡፡ ማትያስ ማነው? ለምን ‹‹የኢንሹራንሱ›› ተባለ? ማትያስን የሚያውቁት አንባቢያን፣ ማን እንደሆነና ለምን ‹‹የኢንሹራንሱ› እንደሚባል (ምናልባት የኢትዮጵያ መድን ድርጅት ይሠራ ስለነበር ከሆነ) መረጃው ሊኖራቸው ይሆናል? ሌሎች አንባቢያን በግርጌ ማጣቀሻ ካልተነገራቸው በምን ሊያውቁ ይችላሉ፡፡ እንዲገምቱ መተው ካልሆነ በቀር፡፡ በምርጫ 97 ቀውስ ጊዜ ሰላም ለማስፈን ከባልደረቦቻቸው ጋር ያደረጉትን ቀና (እና የሚደነቅ) ሙከራ በገለጹበት ቦታ ደግሞ፣ ‹‹የፕሮፌሰር ኤፍሬም እንቅስቃሴ [እንዴት] እንደተቋጨ ሁሉም የሚያውቀው ነው›› ይላሉ፡፡ ስለዚያ የኢትዮጵያ [ቢያንስ የቅርቧ ኢትዮጵያ] ግዙፍና አወዛጋቢ ታሪክ በጣም በአጭሩ በገለጹበት አንቀጽ ፕሮፌሰር ኤፍሬም ማን መሆናቸውን በግርጌ ማስታወሻ እንኳን አለመግለጻቸው ሳይበቃ፣ በታሪክ ምሁር የተጻፈ መጽሐፍ ውስጥ ‹‹ሁሉም የሚያውቀው ነው›› ብለው የተራ ጸሐፊ እርግጠኝነት ብቻ ሳይሆን፣ የታሪክ ጸሐፊ ያልሆነ ግዴለሽነት ያንፀባርቃሉ፡፡ አንድ የታሪክ ጸሐፊ ስለማንኛውም ታሪካዊ ሁነት በጥቂት መስመሮች እንኳን ለማብራራት ሳይቸገር፣ ‹‹ሁሉም የሚያውቀው ነው›› ብሎ ሲልፍ የሚያሳስብ ነገር አለው ማለት አይቻልም፡፡ ‹‹ሁሉም›› የተባልነው እኛ ተራ አንባቢያን ነን ወይስ ታሪክ ምሁራን? ወይስ የጸሐፊው የቅርብ ወዳጆች? ‹‹ሁሉም›› የተባሉ የዚህ ዘመን አንባቢያን ናቸው ወይስ የዛሬ 50 ዓመት የሚመጡት? የትኞቹስ ቢሆኑ (በተለይ ምሁራን ወይም የጸሐፊው ወዳጆች ያልሆኑት) ታሪክ ጸሐፊ ካልነገራቸው በምን ሊያውቁ ይችላሉ?

በተመሳሳይ ስለኮሎኔል ዳንኤል አስፋው፣ ስለኢያሱ ዓለማየሁ፣ ስለፕሮፌሰር ተስፋ ጽዮን መድኃኔ፣ ስለዶ/ር ደረጀ ወልደ መድኅን፣ ወዘተ የሆነውም እንደዚያው ነው፡፡ በየትኛቸውም ረገድ እንደዚያ መደረጉ ባሕሩ (ያዊ) ነው ብዬ አላምንም፡፡ እኔ በበኩሌ፣ በሕይወት ታሪክም ሆነ በሌላ ይዘት ፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ በጻፉት መጽሐፍ ውስጥ ስለአንድ ቦታ ሲነገር ‹‹ጥቁር አንበሳ ፊት ለፊት የሚገኘው…›› የሚል የተራ ጋዜጠኛ አገላለጽ አይመጣጠንልኝም፡፡ ያውም ‹‹ጥቀር አንበሳ›› የሚለው ሐረግ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ያለውን ቦታ ካስተማረን ሰው፡፡ ፕሮፌሰር ባሕሩ ‹‹ጥቁር አንበሳ ፊት ለፊት ያለው ሐውልት፣ ስልህ ሆስፒታሉን ማለቴ እንደሆነ እንዴት ይጠፋሃል? ጥቁር አንበሳ ሲባል ከጥቁር አንበሳ ጦር ሠፈር ጎን፣ ወይም ስድስት ኪሎ ያለ የታሰረ ጥቁር ደቦል አንበሳ አጠገብ ይሆን? ብለህ ከተምታታብህ የራስህ ጉዳይ!›› ይሉኛል ብዬ አልጠብቅም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ጸሐፊ ባሕሩ ከሆኑና፣ ‹‹ጥቁር አንበሳ ፊት ለፊት…›› ካሉ፣ ሆስፒታሉ መሆኑን ብቻ ሳይሆን ‹‹ቀድሞ ልዑል መኮንን ሆስፒታል ይባል የነበረው›› ብለው ቢሆን ነበር የማልገረመው፡፡ ከታሪክ ምሁር፣ ያውም ፕሮፌሰር ባሕሩን ያህል ከገዘፈ ባለሙያ፣ የወላይታ አውራጃ ገዥ የነበሩ ደጃዝማች ወልደ ሰማዕት ገብረ ወልድ ‹‹የክፍለ አገር አስተዳደሪ›› ተብለው ሲገለጹ (በደጃዝማቹ ዘመን ‹‹ጠቅላይ ግዛት›› እንጂ ክፍለ አገር የሚባል ነገር አልነበረም፣ እሳቸውም የነበሩት፣ ‹‹የጠቅላይ ግዛት እንደራሴ›› እና ‹‹የአውራጃ ገዥ›› ነበር) ተራ ወለምታ ብዬ ለመቀበል ያቅተኛል፡፡ እንደዚህ ዕርዳታ ማስተባበሪና ማቋቋሚያ ኮሚሽንን የመሠረቱትና የመሩት አቶ ሽመልስ አዱኛ ‹‹የዕርዳታ ማስተባበሪያ ድርጅት ኃላፊ›› ተብለው ሲቀርቡ፣ ምንም አይደለም ብሎ ለማለፍ የሚያስቸግር ይመስለኛል፣ ሰውዬው ባሕሩ ስለሆኑ፡፡ በሌላ ምሳሌ ደግሞ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያምን ያነሱበት ቦታ ላይ፣ ‹‹ፕሮፌሰር መስፍን›› ብቻ ተብለው ይገልጿቸዋል፡፡ ከላይ ጸሐፊ ‹‹ይታወቃል ብሎ ወስኗል›› ያልኩት በእነዚህ ዓይነት ምክንያቶች ነው፡፡ ነገሩ ተራ ሊመስል ይችላል፣ ስለፕሮፌሰር መስፍን ወይም ስለሌሎቹ የተነገረውን ታሪክ የማወቅ ያህል ዕድሜ ያለን አንባቢያን፣ የተጠቀሱት ሰዎች እነ ማን መሆናቸውን ልንገምት/ልናውቅ እንችላለን፣ ግን መጽሐፉ ለእኛ ብቻ ተብሎ ነው ለማለት የምንችል አይመስለኝም፡፡ ይቅርና የአሁኑ እነ ኮሎኔል ዳንኤል አስፋውን ላያውቃቸው የሚችለው ወጣት ትውልድ፣ ከሃምሳና ከስልሳ ዓመታት በኋላ የሚኖሩትና ታሪክን ከባሕሩ ዘውዴ መጻሕፍት የሚያነቡት ትውልዶች መታሰብ ነበረባቸው ነው የእኔ ቅሬታ፡፡

ሌላ ጊዜ ተስፋ በየነ ኬኔዲ ስለሚባል የ11ኛ ክፍል ተማሪ ጓደኛቸው ሲያነሱ፣ ‹‹ኬኔዲ የሚለውን ስም የወሰደው ከአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆን ኬኔዲ ነው›› ይላሉ (ያውም በግርጌ ማስታወሻ)፡፡ የኬኔዲን ስም የወሰደው ኬኔዲን ስለሚመስል፣ ወይም ወላጆቹ የኬኔዲ አድናቂ ስለነበሩ፣ ወይ የተወለደው ኬኔዲ የተመረጠ (ወይም የተገደለ) ዕለት ስለሆነ፣ ወይም የአያቱ ስም ክንዴ ስለነበረ፣ ጓደኞቹ በተረብም በቁልምጫም ኬኔዲ እያሉ ስለሚጠሩት ይሁን/አይሁን አይነግሩንም፡፡ እንደዚህ ሲሆን ነገሩን ለምን በግርጌ ማስታወሻ ማስቀመጥ እንዳስፈለገም ለመረዳት ያስቸግራል፡፡ ያልተሟላ መረጃ ከሆነ ምን የግርጌ ማስታወሻ ያስፈልገዋል? አንዳንዴ ደግሞ ያልተሟሉ ብቻ ሳይሆን ስህተትም ሊሆኑ የሚችሉ መረጃዎች ይቀርባሉ፡፡ ለምሳሌ ‹‹It is the economy, stupid!›› ስለሚለው የጋዜጠኛና ተንታኝ ‹‹James Carville›› ዝነኛ አባባል ሲናገሩ፣ ነገሩን ፕሬዚዳንት ክሊንተን ለምርጫ ሲወዳደሩ የተናገሩት እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ አባባሉን፣ ሌሎች ሰዎች ክሊንተንን ጨምሮ ተጠቅመውበት ሊሆን ይችላል፣ ባለቤቱ ግን ክሊንተን የነበሩ አይመስለኝም፣ የክሊንተን ነው ማለትም ትክክል ነው ብዬ አላምንም፡፡ በሌላ ምሳሌ [የቦታው] መልክዓ ምድር ለጥ ያለ ሆኖ የሚታየው ‹‹ኤሊኖይ የሚድዌስት አካል በመሆኗ›› ነው ያሉትን ማነሳት ይቻላል፡፡ እና ያንን ያነበበ መደበኛ አንባቢ ‹‹ምንድናት ‹ኤሊኖይ›? (ሚድዌስትስ) ምን ማለት ነው ብሎ ቢጠይቅ፣ ማወቅ ነበረበት ብለን ልንፈርድበት ይገባል? በግርጌ ማስታወሻ ቢያንስ በቅንፍ ካልተነገረው በምን እንዲያውቅ ይጠበቃል? እያነበበ ያለው መደበኛ የግለ ሕይወት ታሪክ፣ አንባቢውም መደበኛ አንባቢ እንጂ የታሪክ ዲፓርትመንት ተማሪ፣ መጽሐፉም ለመደበኛ አንባብያን የተዘጋጀ እንጂ የታሪክ ዲፓርትመንት ‹‹Required Read›› አይደለምና፣ ኤሊኖይንም ሚድዌስትንም ማወቅ አለበት ብሎ መጠበቅ ልክ ነው ብዬ አላምንም፡፡ መቼም ‹‹Google Search››› ያድርጋ!›› እንደማይባል ተስፋ አለኝ፡፡

እና በአጠቃላይ ወይ ለምሁራን መጻፍ ነው ወይም ለተራ አንባቢያን ማዘጋጀት ነው እንጂ፣ ሁለቱንም ማድረግ መሞከር አስፈላጊ ሳንካ ፈጥሯል ነው የእኔ አስተያየት፡፡ መጽሐፉ ዓብይ ችግር እንዲፈጠርበት የሆነው፣ አንባቢያንን ‹ያውቃሉ› ወይም ‹ላያውቁ አይችሉም› ከሚል ምሁራዊ ከሆነ ነገር ግን ያልተባ ‹‹Assumption›› የሚነሳ መምሰሉ፣ አለበለዚያም ‹‹ማወቅ አለባቸው! ካላወቁ የራሳቸው ጉዳይ!›› የሚል የአንዳንድ አስተማሪዎች ድርቅና ሳይታሰብ ተንፀባርቆበት ሊሆን ይችላል፡፡ በየትኛውም ቢሆን ግን መሠረታዊ ችግሩ ማለትም ሁለቱንም (ለእኛ ለተራዎቹ በመሆንና ለአካዴሚያኑ በመሆን) መሀል የመዋለሉ ነገር መታየቱ እነዚያን በመሳሰሉት ክፍተቶች ምክንያት ነው የሚል አስተያየት አለኝ፡፡ እንግዲህ ይህ መጽሐፍ ግለ ታሪክም ቢሆን፣ በተለይ በባሕሩ ዘውዴ የተጻፈ ስለሆነ የአገር ታሪክም አለመሆን አይችልም፡፡ ስለዚህ እንደ ሁሉም ሌሎቹ የፕሮፌሰር ባሕሩ መጻሕፍት ባይሟላም እንኳን የታሪክ ሰነድም ነው፡፡ በመሆኑም ትንሽ ጊዜ ተወስዶበት እንደ ሁሉም በምንም ረገድ እንኳን በይዘት፣ በፊደላት እንኳን ቅንጣት ኅፀፅ እንደሌለባቸው መጻሕፍቶቻቸው ተደርጎ ተዘጋጅቶልን ቢሆን ጥሩ ነበር የሚል አስተያየት አለኝ፡፡

ከዚህ ሌላ በአንድ ወይም በሌላ መንገድ መጽሐፉ ታሪክ እንደመሆኑ የተደረገን ነገርና የተነገረን ቃል ሲያቀርብ፣ አድራጊዎቹንና ተናጋሪዎቹን እየመረጠ መግለጽ ወይም ማስቀረት የነበረበትም አይመስለኝም፡፡ እንደ እኔ እምነት ‹‹ስሙን መጥቀስ አያስፈልግም››፣ ‹‹ቦታው የት እንደሆነ እንለፈው›› ዓይነት ነገሮችን የሚናገሩ ሰዎች ተራ ወግ ተራኪና ምናልባትም ሐሜተኞች ይመስሉኛል፡፡ መቼም በእርግጠኝነት ባሕሩ የትኛውንም አይደሉም፡፡ ግን ደግሞ መመዘኛው ግልጽ ባልሆነ መንገድ በታሪካቸው ላይ የሚያነሷቸውን ሰዎች አንዳንዴ ማንነታቸውን የሚገልጹበት፣ አንዳንዴ ደግሞ የሚደብቁበትን ምክንያት ለመረዳት አልቻልኩም፡፡ ጁነዲን ሳዶ፣ ደሴ ዳልኬ፣ በረከት ስምዖን፣ ወዘተ… የመሳሰሉ ሰዎች በቀጥታ ይጠቀሳሉ፡፡ ሌላ ጊዜ ደግሞ ‹‹ያናገርኩት አንድ የወቅቱ ባለሥልጣን›› ፈቃደኛ ስላልሆነ፣ ‹‹ያናገርነው አንድ ታዋቂ ሠዓሊ›› እንቢ ስላለን፣ ‹‹በወቅቱ የከተማው ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ የነበረ አንድ ሰው›› የሚሉ፣ የተወሰኑ ሰዎችን ብቻ ማንነት ለመግለጽ ለመፈለግ ነገር ያሳያሉ፡፡ ለምን እንደዚያ ሆነ ማለቴ አይደለም፡፡ ግን ቢያንስ ምክንያቱን ወይም መመዘኛዎቹን ቢነግሩን ጥሩ ነበር ብዬ አስባለሁ፡፡ በተመሳሳይ ጄሪ ሳሎል ስለተባለ አንድ ባልደረባቸው ሲናገሩ፣ ‹‹የኅብረት ማንነት ተምሳሌት የሆነው ጄሪ›› ይሉና ለምን እንደዚያ እንዳሉት ምንም መግለጫ አይሰጡንም፡፡ ጭራሹን ከሦስት ሰዎች ጋር ተቀምጠው በሚታዩበት ፎቶግራፍ ሥር ‹‹በጉባዔ ላይ ከጄሪ ሳሎን ጋር›› የሚል ጸሑፍ ብቻ እንጂ፣ እንደዚያ ያደነቁት ጄሪ ሳሎል ከሦስቱ የትኛው እንደሆነ እንኳን አይጠቁሙም፡፡ በነገራችን ላይ የፎቶግራፍ ነገር ከተነሳ፣ መጽሐፉ ውስጥ የተካተተው ተቋማቸው ያስገነባው ሕንፃ ፎቶግራፍ፣ ግቢ ውስጥ ከሕንፃው ፊት ለፊት የተደረደሩትን የተወላገዱ ዛኒጋባ የቆርቆሮ ቤቶችን አብሮ የሚሳይ መሆኑ አላስገረመኝም አልልም (የዓይን ቁስል ይላል ፈረንጅ)፡፡ በዛጉ ቆርቆዎች የተለጣጠፉትን ዛኒጋባዎች ወይ ከፎቶግራፉ ወይ (ይልቁንም ከጅምሩ ከግቢ) በማስወጣት ዓይንንም ከማቁሰል፣ ያልሆኑትን ግድ የለሽ ከማስመሰልም መዳን ይቻል የነበረ ይመስለኛል፡፡

ሌላው ዋና ጉዳይ አርትኦት ነው፡፡ ስለፊደላትና ቋንቋ ጥራትና የአርትኦት ጥንቃቄን አስመልክቶ መቼም ባሕሩ ደጃፍ የሚደርስ ሌላ ጸሐፊ አለ ብዬ አላምንም፡፡ ይህንንም በተለያዩ የመጻሕፍት ግምገማ መድረኮች ላይ የጥራት መለኪያ ሚዛን ሊሆኑ የሚገባቸው ናቸው እያልኩ እናገራለሁ፡፡ ባሕሩ ከማስበውም በላይ የአርትኦት አበጋዝ መሆናቸውንና ዓይኖቻቸውም ለግድፈት ዝንፍ እንደማይሉ፣ ለታላላቅ ሰነዶች ቁጥር የሌላቸው የአርትኦት ሥራዎችን በአገርም በዓለም አቀፍም ደረጃ እንዳከናወኑ የተረዳሁት ይህንን ግለ ታሪካቸውን ካነበብኩ በኋላ ነው፡፡ ያም ሆኖ የዚህኛውም መጽሐፍ በአብዛኛው በጥንቃቄ የተሠራ፣ ኅትመትና ጥረዛውም ግሩም ቢሆን በተለይ በአርትኦት ረገድ እንደ ሌሎቹ መጻሕፍቶቻቸው በበቂ የተጠነቀቁበት ሆኖ ግን አላገኘሁትም፡፡ መቼም ባሕሩን በሚያህል የአገር ታሪክ ዝግባና ምሕረት የለሽ አርታዒ የተጻፈ መጽሐፍ ውስጥ ስለሱዳንና ኢትዮጵያ ድንበር መካከል ጥናቶቻቸው ሒደት ሲነገር፣ በወቅቱ ‹‹የ1994ቱ (የሱዳንና ኢትዮጵያ) የድንበር ውል መቶኛ ዓመቱን እያከበረ ነበር›› የሚል ነገር ማየት ስለአርትኦት ጥንቃቄ ለመመስከር አያስችልም፡፡ የዘንድሮ ልጆች (የስፖርት ጋዜጠኞችን ጨምሮ) ስለ ‹‹Wayne Rooney›› ሲያወሩ፣ በኩራት ‹‹ዋይኔ ሩኒ›› ይላሉ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ የባሕሩ ዘውዴ መጽሐፍ ውስጥ ‹‹Hebrew›› ‹‹ሂብሪው›፣ ‹‹ሳዲዝም›› (Sadism)፣ ‹‹ኒሎልሰን›› (Nicholson)፣ ‹‹ኪርክ›› (Kirk)፣ ‹‹ብሩክላይን›› (Brookly) ተብሎ ተጽፎ ስመለከት ቢጎረብጠኝ ግን የሚፈረድብኝ አይመስለኝም፡፡ ወይም ደግሞ ‹‹Philanthropy›› የሚለው ቃል ‹‹ፊላንትሮፊ›› ተብሎ ሳነብ፣ ምንም አይደለም ለማለት ያስቸግረኛል፣ ምክንያቱም መጽሐፉ የባሕሩ ስለሆነ፡፡ አንድ የከተማችን ቁንጮ ባለሀብት የበጎ አድራጎትን ክንፍ ራሱን ‹‹ሰንሻይን ፊላንትሮፊ›› ብሎ በየአደባባዩ ጽፎ ስመለከት ያናድደኝ ነበር፡፡ አሁን ትክክል አይደለም ቢባሉ ዝም በል እንኳን እኛ ባሕሩ ዘውዴም እንደዚያ ነው የሚጽፈው ቢሉ ምን ሊባል ነው?

ሌላው ብዙም ያልተመቸኝ ነገር በየቦታው ያሏቸውና በእኔ አስተያየት የምገምተውን የባሕሩን ‹‹Stature›› የማይመጥኑ አባባሎች ናቸው፡፡ አስፈላጊነታቸውም ሊታየኝ አልቻለም፡፡ አንደንዶቹ እንዲያውም አስተዛዛቢ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ምናልባት እንደ ብዙዎቹ (እንደ ሁሉም) ሌሎች መጻሕፍቶቻቸው የታሪክ ጥናትና ምርምር ድርሳን ሳይሆን ቀለል ያለ የሕይወታቸው ታሪክ ስለሆነ ብለው ያምናሉ፡፡ ወይም ለምሁራን ሳይሆን ለመደበኛ አንባብያን የተዘጋጀ በመሆኑ ነው ሊባል ይቻልም ይሆናል፡፡ ነገር ግን ከላይ እንዳልኩት የሕይወት ታሪኩ የባሕሩ ዘውዴ ስለሆነ የአገር ታሪክም ነው፡፡ እንደ አገር ታሪክ በጽሑፍም እያንዳንዷ ቃል ዋጋ አላት፣ ያለበቂ ምክንያትም መባልም አለመባልም ያለባት አይመስለኝም፡፡ ታሪኩን ከደረቅነት ለማዳንና ለማዋዛት በሚመስሉ ሙከራዎች የሚሏቸው ነገሮች የጠቀሙ አይመስለኝም፡፡ ለምሳሌ መኪናቸውን ከኒውዮርክ ወደብ ላይ ማስጫናቸውን ሲናገሩ፣ ‹‹ማርያም ትከተልሽ ብዬ ሸኘኋት›› የሚል አባባል ምን እንዳመጣው ለማየት አስቸግሮኛል፡፡ ስለልጅነታቸው የግርዛት ወቅት ሲናገሩ ደግሞ፣ ‹‹ሞት ይዘገያል እንጂ አይቀርም እንደሚባለው፣ ለዕርድ ቀረብኩ›› ሲሉ የተረቱም አስፈላጊነት ‹‹Relevance›› ግርዛትም ዕርድ የመባሉ ነገር ሊገባኝ አልቻለም፡፡ ወይም ጣሊያኑ መኪናው ከጭቃ አልወጣ ሲለው ‹‹ማርያምን ከእነ ልጇ ይረግም ጀመር፡፡ እሱ ሲንቀለቀል ላደረሰው ጥፋት አማልክትን ተጠያቂ አደረገ›› የመሳሰሉ ተራ አባባሎች ባሕሩ (ያዊ) ሆነው አላገኘኋቸውም፡፡ ከዚህ በባሰ በጉራጌ ባህል ስለነበረው የሠርግ ልማድ ሲናገሩ፣ ‹‹ኋላቀር ከነበረው ከሙሽራይቱ ጥፍር መቆረጥ ጀምሮ› ያሉትን ነገር መጥቀስ ይቻላል፡፡ ስለጉዳዩ ከዚያ በፊት አላውቅም ነበር፡፡ ግን እሱን ሳነብ ጥፍር መቁረጥ በምን መለኪያ ነው ኋላቀር የሚባለው? ይልቁንም ሥልጣኔ አይደለም እንዴ? ብዬ ነበር፡፡ ኋላ ላይ አንድ ማገቦ የሚባል ኮበሌ ወዳጄን (ጉራጌ ነው) ጠይቄው፣ ‹‹ጥፍር መቁረጥ አይደለም እጆቿን ዘፍዝፎ አሳድሮ ጥፍሮቿን ከሥራቸው መንቀስ ነበር እኮ! በጣም አሰቃቂ ነበር፡፡ አሁን ቀርቷል፡፡ እኔ የሠርጋችን ቀን ሚስቴን እንኳን ጥፍሯን ፀጉሯን እንኳን አላስነካኋትም›› ብሎ ነገረኝ፡፡ ባሕሩ ለምን ጥፍር መነቀልን የመሰለ ዘግናኝ ነገር ‹‹ጥፍር መቆረጥ›› ብለው ለመግለጽ እንደመረጡ መገመት አልቻልኩም፡፡

እንዲሁ ሌሎች አለቅጥ የተጋነኑ ወይም የባሕሩ ዘውዴን የማይመስሉ ብዙ አገላለጾችም ይታያሉ፡፡ ለምሳሌ የራስ መኮንን አዳራሽን ጥቅም ላይ ስለማዋላቸው ሲናገሩ፣ ‹‹የማንም መፈንጫ የነበረውን›› ማለትም የባሕሩን ጨዋነት የሚመጥን አይመስለኝም፡፡ ጣሊያን በነበሩበት አንድ ጊዜም፣ ‹‹ቆይታዬ አንድ ቀን ወደ ጥልቅ ትራጄዲ ሊቀየር ነበር›› ያሉትን አለማንሳት አይቻልም፡፡ ያንን ሲሉ ያነበበ ሰው ሳይደርባቸው የቀረው ‹‹ጥልቅ ትራጄዲ›› በሰዓቱ ባለመድረሳቸው ሳይሳፈሩ የቀሩበት አውሮፕላን ተከስክሶ መሆን አለበት ብሎ ሊገምት ይችላል፡፡ አስቂኙ ነገር ግን ‹‹ጥልቅ ትራጄዲው›› የኪስ ቦርሳቸው የጠፋባቸው መስሏቸው በኋላ ማግኘታቸው መሆኑን ሲነግሩን ነው፡፡ ዘወር ሲሉ የኪስ ቦርሳን ማጣት (ጠፍቶ ቢቀር እንኳን) ‹‹ጥልቅ ትራጄዲ›› ሊባል ይችላል? እንዴ ደግሞ በልጅነታቸው ‹‹ከምሳ ጋር በተያያዘ ሁለት መጥፎ ትዝታዎች አሉኝ›› ብለው አንዱ የሆነ ‹‹ቦታ ሄደን ስንመለስ ልጆች ምሳችንን በልተው የጠበቁን ዕለት›› ነው ይላሉ፡፡ እንዴት ነው አንድ ቀን ሕፃናት ተማሪዎች ባለምሳው በሌለበት ሳህኑን ከፍተው መብላታቸው ‹‹መጥፎ ትዝታ›› ሊሆን የሚችለው? ትዝታ ጠፍቶ ነው? ‹‹ቾምቤ ከረሜላዬን ነጥቆ የሮጠ ዕለት›› ብለው ቢሆን ኖሮስ፣ ከዚህ ያንሳል (ወይስ ይብሳል) አይመስለኝም፡፡ እንዲህ ዓይነት ተራ ነገሮችን ‹‹አስገራሚ›› ነገር አድርጎ የማቅረብን አዝማሚያ ምንም አይደለም ተብሎ ሊታለፍ ይቻላል? አላውቅም፡፡ እኔ ግን ልክ አይመስለኝም፡፡ ምክንያቱም ማንም ሰው በተለይም የአገር የታሪክ መጽሐፍትን የሚጽፍ ባለሙያ ተራ የዕለት ተዕለት አጋጣሚዎችን እንደዚያ በማጋነን ቃና አጅቦ የማቅረብ ነገር ካሳየ፣ መቼም የተጻፈ ታሪክ ከጸሐፊው ዕይታና አገላለጽ ሊያመልጥ አይችልምና የሚጽፋቸውም አገራዊ ታሪኮች የተጋነኑ ሊሆኑ ይችላሉ ብለው ሰዎች እንዲገምቱ የማድረግ አደጋ ሊያመጣ ስለሚችል፡፡

በሌላ ጉዳይ በልጅነታቸው ትምህርት ቤት እያሉ መምህራቸው የነበሩት ፊታውራሪ መኮንን ዶሪ፣ ‹‹ለኢትዮጵያ በነበራቸው ጥልቅ ፍቅር፣ የባንዲራውን ትርጉም ሲያስረዱን›› ይሉና፣ ‹‹አረንጓዴው ልምላሜን፣ ቢጫው ሃይማኖትን፣ ቀዩ ደም መስዋዕትነትን አመላካች ነው ይሉን ነበር›› ይላሉ፡፡ እኔም ከዚያ ዘመን ብዙም ባልራቀ ዘመን ነበር ትምህርት ቤት የነበርኩት፡፡ የእኔ መምህር ይነግሩን የነበረው ብቻ ሳይሆን ሁላችንንም በነበረን የ‹‹ታሪክና ምሳሌ›› መጽሐፍ ጀርባ ስለባንዲራው ቀለማት ትርጉም ተጽፎ የነበረው፣ ‹‹አረንጓዴው ተስፋ ልምላሜና ሀብት፣ ቢጫው ሃይማኖት አበባና ፍሬ፣ ቀዩ ፍቅር መስዋዕትነትና ጀግንነት›› ነበር፡፡ እነዚህ የባንዲራውን ቃላት ትርጓሜ በተሟላ መልክ በተለይ በዚህ አገራዊ ስሜት በቆሰለበት ወቅት በፕሮፌሴር ባሕሩ ቢነገሩ ደስ ይለኝ ነበር፡፡ መቼም መኮንን ዶሪ ባሕሩ እንዳሉት፣ ‹‹ለኢትዮጵያ ትልቅ ፍቅር የነበራቸው›› ከነበሩ፣ የባንዲራውን ትርጓሜ እንደዚያ ባልተሟላ መልክ ይነግሯቸዋል ብዬ አልገምትም፡፡ እንደዚያ ነግረዋቸው የነበረ ቢሆንም እንኳን፣ ፕሮፌሰር ባሕሩ አሟልተው ቢጽፉልን ነበር የምወደው፡፡ ይህንን ዓይነት ነገር ከሌላ ከማንም ሳይሆን ከባሕሩ ቢነገረን ነበር የሚያምርበት ብቻ ሳይሆን የላቀ ትርጉምም የሚኖረው፡፡ 

ከአገር ታሪክ ጋር በተያያዘ ሁልጊዜ ሳስብ የድሮ የኢትዮጵያ ታሪኮች በበጎም ይሁን በክፉ ተጽፈዋል፡፡ እንደዚያው የኖርንበትና እየኖርንበት ያለው ዘመን ታሪኩ እየተጻፈ ይሆን? የሚል ነገር ራሴን እጠይቃለሁ፡፡ የእነ አፄ ቴዎድሮስን፣ ዮሐንስን፣ ምኒልክን፣ ወዘተ ታሪክ ያወቅነው ተክለ ጻድቅ መኩሪያ ስለጻፉልን ነው፡፡ እሳቸው ባይኖሩና ከ500 ዓመታት በፊት ስለነበረ ታሪክ 850 ገጽ መጽሐፍ ባይጽፉልን ኖሮ፣ ሦስት ሜትር ቁመት ያለው ሰው ያልሆነ ግድንግድ ፍጥረት ወደ ሰማይ አጉኖ የተከላቸው ቋጥኞች እያልን አፈ ታሪክ ከመቀባበል አልፈን ስለግራኝ አህመድ ዘመንና ታሪክ ምን እናውቅ ነበር? ሁልጊዜም የኖርንበትና እየኖርንበት ያለው ዘመን ታሪኩ እየተጻፈ ይሆን? የሚለው ጥያቄ በመጣብኝ ቁጥር ራሴን የማፅናናው እርግጠኛ ነን ባሕሩ ዘውዴ እየከተበው ነው በሚል መልስ ነበር፡፡ አሁንም ተስፋ የማደርገው እንደ እሱ ነው፡፡ ፕሮፌሰር ባሕሩ ያላለቀና ያልታተመ የኢትዮጵያ የቅርብ ዘመናት ታሪክ ድርሳናቸውን በየጊዜው እያወጡ የየዘመኑን ሁነት እየከተቡበት ነው የሚል ተስፋም የየዋህ የሚመስል ግን ቅን የሆነ ተስፋ አሁንም አለኝ፡፡

እንዲህ ሆኖም ይህንን መጽሐፍ አንብቤ ስጨርስ ያንን ተስፋዬን ጨርሶ ባያስቆርጠኝ ያለመለመልኝን ነገር ማየት ግን አልቻልኩም፡፡ በመጽሐፉ ካነበብኳቸው የኢትዮጵያ ታሪክ መጻሕፍት አካላት ሊሆኑ የሚችሉ ነገሮች ስለዓድዋ መቶኛ ዓመት አከባበር ስንክሳር፣ የአዲስ አበባ ታሪካዊ ቅርሶችንና የታሪክ ትምህርትን ስለማዳን የተሠሩን ሥራዎችን አስመልክቶ የቀረቡት ነገሮችን ብቻ ይመስሉኛል፡፡፡ ለምሳሌ ወያኔ አዲስ አበባ ሲገባ ስለነበረው ሁኔታ የሚገልጹባቸው ቦታዎች ላይ (ያውም ‹‹የመጀመሪያዎቹን 15 ቀናት ዜና መዋዕል እየከተብኩ ነበር›› ብለው ነግረውንም)፣ የንግድና ትራንስፖርት እንቅስቃሴ በመቋረጡ ‹‹ቢራ ማግኘት ስላለመቻሉ›› ስለመንገድ መዘጋትና ነዳጅ መጥፋት ካልሆነ በስተቀር፣ ያንን ወቅት እንደ አገር ታሪክ ገልጸውልናል ብዬ ለመቀበል ይቸግረኛል፡፡ ይባስ ብሎ ግንቦት 20 ወያኔ የአዲስ አበባን ሬዲዮ ጣቢያ ስለተቆጣጠረበት ሁነት ሲነግሩን፣ በዕለቱ ‹‹የተለያዩ ማስታወቂያዎችና ማስጠንቀቂያዎች በአብዛኛው በትግርኛ ዘፈኖች እየታጀቡ ተላለፉ›› ያሉት ነገር የበለጠ ግራ አጋብቶኛል፡፡ ተሳስቼ ካልሆነ በዕለቱ ‹‹ያው በዕድሜ ነውና ዕድሜ ይስጠው ለዕድሜ›› የሚል ዘፈን ቋቅ እስኪል ይደጋገም እንደነበረ እንጂ የትግርኛ ዘፈኖች (ያውም ‹‹ብቻ›› ሆነው) ሲተላለፉ አላስታውስም፡፡ ስለበቅሎ ቤቱ የመሣሪያ ግምጃ ቤት ፍንዳታም በአለፍ ገደም የጠቀሱት ከመሆን አልፎ ምንም ለአገር ታሪክ የሚበቃ ዝርዝር አልቀረበበትም፡፡ ሌላው ቀርቶ የዘመናችን ኢትዮጵያ ታሪክ በትልቅ መጽሐፍ ሲጻፍ (ከተጻፈ) ከታላላቅ ዓምዶቹ መካከል አንዱ ምናልባትም ዋነኛው ሊሆን ስለሚችለው ኢትዮጵያውያንን በዘርና በጎሳ የመከፋፈል ሴራ፣ ‹‹ዘረኝነትን የማይደግፉ›› መሆኑን በገለጹበትና ስለጉራጌነትና ኢትዮጵያዊነት ያላቸውን እምነት ከተናገሩበት ግማሽ ገጽ የማይሞላ ትርክት በስተቀር ምንም ለታሪክ መጽሐፍ በተገባ ዝርዝር አላቀረቡልንም፡፡ ይልቁንም ከዚህ (ከጉራጌነትና ከኢትዮጵያዊነት) ጋር በተያያዘ ‹‹ከደመወዝ ውጪ ሌላ ሥራ›› አስበው እንደማያውቁ ሲያስረዱ፣ ‹‹በዚህ ረገድ የእኔ የጉራጌ ዲኤንኤ ፈዘዝ ያለው ነው›› ብለው ክው! የሚያደርግ ነገር ይናገራሉ፡፡ ክው የሚያደርገው አባባሉ የሰው ባህርያት (Attributes) በዲኤንኤ ከብሔር ማንነት ጋር አብረው የሚፈጠሩ እንደሆኑ የሚያስመስል ስለሆነ ብቻ ሳይሆን፣ እውነት ለመናገር አደገኛ ሆኖ ስለተሰማኝም ነው፡፡ እንዲህ ያለ ንግግር ቀላል ድንቅፍም አይደለም፣ በተለይ ከባሕሩ ሲመጣ፡፡ ከጓደኞች ጋር ሲወራ እንደ ዋዛ እንደ ቀልድ ሊወሰድ ይችል ይሆናል፡፡ በመጽሐፍ ያውም በታሪክ ምሁር መጽሐፍ ውስጥ ሲከተብ ግን የአገሬ ልጆች በስማቸው፣ በተወለዱበት ቦታና በቋንቋቸው መከፋፈላቸው (እነዚህን ዓይነት ልዩነቶቻቸውን ማስታረቅም ማቻቻልም ያቃታቸው) ሳይበቃ ጭራሽ የእኔ ብሔር ዲኤንኤ እንዲህ ነው፣ የአንተ ብሔር ዲኤንኤ እንዲህ ነው እያሉ እንዲናቆሩ ከመጋበዝ አይተናነስም፣ ሆን ተብሎም ባይሆን፡፡

ይህ እንዳለ ሆኖ እዚህ መጸሐፍ ላይ ስለፕሮፌሰሩ ባሕሩ ሰብዕና በተለይም ስለዘርፈ ብዙ ብዙ ችሎታና ብቃታቸው ማወቅ የሚያስችሉ በርካታ ማሳያዎች ሆነው በእኔ በኩል የተለያዩ ቋንቋዎች ብዛት እጅግ አስገርመውኛል፣ እውነት እስከማይመስል ድረስ፡፡ ቅርሶችን ለማዳን (ለአገርን መታደግ ጨምሮ) የታሪክ ትምህርትን እንደገና ለማስጀመር፣ ወዘተ የከፈሏቸው መስዋዕትነቶች ሲታዩ ብሔራዊ ጀግና መባል የሚያንሳቸው አይሆንም፡፡ ከልጅነታቸው ጀምሮ ጠቅላላ ሰብዕናቸው በፅናት፣ በቁርጠኝነትና በውጤት ጉጉትና በሚመሰከርለት ስኬት የሚገለጽ መሆኑን አለማየት ብቻ ሳይሆን መከራከረም አይቻልም፡፡ በነገራችን ላይ ስለ‹‹ሰው››ነታቸው ሳስብ እልኸኝነታቸው ዕድሜያቸው በጨመረ ቁጥር እየለዘበ እንደሄደ መናገራቸው በጎ ነገር ሆኖ፣ እንግሊዝ አገር እያሉ ልጃቸው ‹‹ስኳርና ጣፋጭ አብዝቶ እየተቅበጠበጠ ሲያስቸግረኝ ገረፍኩት” ያሉት ነገር እንዳስደነገጠኝ ሳልናገር ማለፍ አልፈልግም፡፡ የአምስት ዓመት ልጅ ያውም እንግሊዝ አገር ሲገርፉ ቢገኙ ሊደርስ የሚችለውን ነገር (መቼም አያውቁትም ብዬ አልጠረጥርም) ሳስበው ድንግጥ አድርጎኛል፡፡ ደግነቱ መጀመሪያም መጨረሻም ጊዜ [የገረፍኩት] ያኔ ነው›› ብለዋል፡፡ ቢሆንም ግን፣ ‹‹ልጅን መግረፍ›› ያውም በአምስት ዓመቱ፣ ያውም ‹አይስክሬም በልቶ ተቅበጠበጠ› በሚል ምክንያት ብቻ፣ ዕሳቤው ብቻውን እንኳን በሐሳቤ ከሳልኩት ባሕሩ ጋር ተቃራኒ ሆኖብኛል፡፡

ለማጠቃለል ይኼ መጽሐፍ ግለ ታሪክም ቢሆን፣ የአገር ታሪክም ሊሆን የሚችል ስለመሆኑ ግድ ያልተሰጠ የመሰለበትና ከዚያም የጎደለበት ምክንያት (ከተስማማን ማለት ነው) ምኞታዊ ተስፋ ያደረግኩበት፣ እየተጻፈ ያለውና የሚታተምበት ጊዜም ያልተወሰነ ነው፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ ታሪክ ከ1950 እስከ___ በፕሮፌሰር ባሕሩ ዘውዴ›› የሚለው ግዙፍ የታሪክ ድርሳን ውስጥ በዚህ መጽሐፋቸው አስቀሩብን የምላቸው ነገሮች ከእነ ምክንያትና ቅደም ተከተላቸው ተዘርዝረው ስለሚገኙ፣ አሁን በዚህ ቀለል ባለ የሕይወት ታሪኬ መጽሐፍ ውስጥ ሊቀመጡ አያስፈልግም ተብሎ ይሆናል የሚል ነው፡፡ በዚህ መጽሐፍ በድለውናል ብዬ ስለጠቃቀስኳቸውም ‹ችግሮች›፣ ተሳስቼም ከሆነ ‹ተሳስተሃል› ይሉኛል፣ ወይም ‹ማስተካከያ ይደረጋል› ይሉኝ ይሆናል እንጂ መቼም ይገርፉኛል ብዬ አልሠጋም (ትቻለሁ ስላሉ)፡፡

በመጨረሻም አንድ ነገር ማለት ካለብኝ፣ ይህ መጽሐፍ ዋና ምክንያት በኮቪድ-19 ወረርሽኝ ወቅት በተረፈ ጊዜና በወዳጅ ዘመድ ውትወታ ‹‹ምናልባት በይድረስ ተጽፍ ይሆን?›› የሚል ምክንያት ለራሴ መስጠቴን ነው፡፡ ‹‹መቼም የሚወዱት ሲበድል፣ ለበደሉ ምክንያት ማግኘት ቀላል ነው›› ይላሉ ሐዲስ ዓለማየሁ፡፡

ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን፣ በኢሜይል አድራሻቸው danielbelayneh@gmail.com. ማግኘት ይቻላል፡፡

spot_imgspot_img
- Advertisment -

በብዛት የተነበቡ ፅሁፎች

Related Articles