ፍርሃት በሰው ላይ ያለና ሁሉም የሚያውቁው ተፈጥሮአዊ ክስተት ነው፡፡ ፍርሃት በሰውነታችንና በመንፈሳችን ላይ ከፍተኛ ጫና ያመጣል፡፡
በምንፈራበት ጊዜ የተለመደውን በራስ መተማመንን እናጣለን፡፡ ዕርዳታ የሚያስፈልገን መስሎ ይታየናል፡፡ ይህም ሆኖ ከፍርሃት ለመውጣት ወዲያውኑ እንጥራለን፡፡ በፍርሃት አብረው የሚሄዱትን ስሜቶች ማለት እንደ መጨናነቅ፣ መሸበር፣ ሽሽትና ቁጣ (Aggression) ሲሰማን በሰውነት ላይም መንቀጥቀጥ፣ መገርጣት ጉሮሮ መድረቅ ሆድ መላወስና የእግር መክዳት ስሜትና ማላብ ይይዘናል፡፡
ጥያቄው ፍርሃት ሲይዝ ምን ማድረግ አለብን ላይ ነው፡፡ የሚታወቀው ዘዴ ፍርሃት ከሚፈጥረው ነገር መራቅና መረጋጋትን መፍጠር ነው፡፡ ፍርሃተኛ ሰው ሁልጊዜ በተጠንቀቅ ላይ ነው የሚገኘው፡፡ ፍርሃትን መቆጣጠር የሚቻለው መረጋጋትና ዘና ማለት ሲቻል ነው፡፡ መረጋጋትና ዘና ማለት ፍርሃትን መቆጣጠር ያስችላል እንጂ የተፈጠረውን ሁኔታ መዘንጋት ያስችላል ማለት አይደለም፡፡ በአጥቂ (አካላዊም ሆነ ሥነ ልቦናዊ) ሊፈጠር የሚችለውን ሁኔታ ማገናዘብና ፍርሃትን መቆጣጠር መቻሉ ላይ ነው ሚስጥሩ፡፡ ይህም የሚሆነው በተይም የራስን ደካማ ጎንን በወቅና በራስን መተማመንን በመገንባት ላይ ነው፡፡
(ፀጋዬ ደግነህ ጉግሳ (ዶ/ር) ጁጂትሱ፣ 2001 ዓ.ም.)