የመንግሥት ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በክፍል ውስጥ ከሚማሩት ትምህርት ውጪ ወደ ተለያዩ ኢንዱስትሪዎች ሄደው ለሚያደርጓቸው የተግባር ላይ ልምምዶች የሚደረግ ወጪ፣ ከምርቃት በኋላ በሚከፍሉት የወጪ መጋራት ውስጥ እንዲካተት ጥናት መጀመሩ ተገለጸ፡፡
በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የወጪ መጋራት (Cost Sharing) መመርያ መሠረት ወደ መንግሥት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የተቀላቀሉ አዳዲስ ተማሪዎች፣ ከገቡበት ጊዜ ጀምሮ ተመርቀው እስኪወጡ ድረስ፣ መንግሥት ለምግብና ለመኝታ ያወጣውን ወጪ በሚገቡት ውል መሠረት ከምርቃት በኋላ ግዴታቸውን መወጣት እንዳለባቸው ተደንግጓል፡፡
ተማሪዎች በክፍል ውስጥ በንድፈ ሐሳብ ተምረው ወደ ተግባር ልምምድ ሲወጡ ለሚቆዩባቸው ጊዜያት ለሚኖራቸው የተግባር ላይ ትምህርት፣ ከምረቃ በኋላ ከወጪ መጋራት ጋር ተዳምሮ እንዲከፍሉ ለማድረግ የትምህርት ሚኒስቴር ዕቅድ መያዙንና ጥናት መጀመሩን፣ በትምህርት ሚኒስቴር የተቋማት ትስስርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ዳይሬክተር አቶ ተሾመ ዳንኤል ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
ሐሳቡ በጥናት ላይ መሆኑንና ዓላማው ወደፊት ተማሪዎች የተግባር ላይ ልምምድን ትኩረት ሰጥተው እንዲማሩ ለማድረግ ታስቦ ነው ብለዋል፡፡
ይሁን እንጂ ለክፍያው የልማት አጋር ድርጅቶች ለትምህርት ተቋማትና ኢንዱስትሪዎች ትስስር የሚመድቡት ገንዘብ ስለሚኖር፣ ከዚህ ገንዘብ ለወጪ መጋራት ሊከፈል የሚችልበት አሠራርም ሊዘረጋ እንደሚችልም አስረድተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዴሚ የመንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች ከኢንዱስትሪዎች ጋር ያላቸውን ትብብርና ትስስር የሚዳስስ የምክክር መድረክ አዘጋጅቷል፡፡ የመድረኩ መዘጋጀት የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፣ የምርምር ተቋማትና የኢንዱስትሪዎች ትስስር ፎረምን ለማቋቋም ያለመ ነበር፡፡
ፎረሙ ዩኒቨርሲቲዎችና ኢንዱስትሪዎች የጋራ ችግራቸውን በምርምር በመፍታት የቴክኖሎጂ ልውውጥ የሚያደርጉበት፣ ተማሪዎች የተግባር ልምምድ የሚያደርጉበትና ተቋማት የኢንዱስትሪውን ፍላጎት መሠረት በማድረግ ሥልጠና እንዲሰጡ የሚያደርግ መሆኑን፣ ከመላ አገሪቱ 15 ዩኒቨርሲቲዎች እንደሚሳተፉ ታውቋል፡፡ እነዚህ ዩኒቨርሲቲዎች ለአገልግሎት ሰጪውም ሆነ ለአምራች ኢንዱስትሪው አስፈላጊውን ባለሙያ ማቅረብ የሚችሉ መሆናቸውን፣ በትስስሩ ከዚህ በፊት ከተለመደው በዩኒቨርሲቲ መምህር ብቻ የማስተማር አሠራር በተጨማሪ በኢንዱስትሪ ውስጥ ልምድ ያካበቱ ባለሙያዎች እንዲያስተምሩ የሚያደርግ የትብብር ፎረም ስለመሆኑ ተገልጿል፡፡
ፎረሙን የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዴሚ በዋናነት በማስተባበርና ምክረ ሐሳብ በማቅረብ፣ ትብብሩ የሚጠናከርበትን መንገድ ከትምህርት ሚኒስቴር ጋር በመሆን የሚሠራበት መሆኑን አቶ ተሾመ ተናግረዋል፡፡