ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ፣ በትግራይ ክልል በተካሔደው ጦርነት ሕይወታቸውን ላጡ ወገኖች እየተከናወነ ያለውን የኀዘን ሥነ ሥርዓት በማስመልከት ጥቅምት 3 ቀን 2016 ዓ.ም. ባስተላለፉት አባታዊ የማጽናኛ መልዕክት ላይ ያሰመሩበት ኃይለ ቃላት። የሰው ልጅ በጠለ ሰማይ ምድርን ሊያርስ ሲገባው፣ በሰው ደም መሬትን እያጨቀየ፣ በድንጋይ ቤት ሊሠራ ሲገባው ወንድሙን መትቶ እየገደለ መኖርን የታሪኩ ዋነኛ አካል ማድረጉ እጅግ ያሳዝናል፡፡ ሰው ስህተቱን እንዲተው በቃለ እግዚአብሔር ይማራል፣ እንቢ ካለ ከመከራ ይማራል በማለት ያስታወሱት ፓትርያርኩ፣ እኛ ኢትዮጵያውያን ከቃለ እግዚአብሔርም ሆነ ካለፉት የጦርነት ታሪኮቻችን መማር ባለመቻላችን በትግራይ፣ በአማራ፣ በአፋርና በሌሎች ክልሎች ብዙ የሰው ደም መፍሰሱን፣ ይህም ሳይበቃን በዚህ ሰዓት እንኳ በተለያዩ ስፍራዎች የምንሰማው የእልቂት ዜና ሆኖ ያውከናል ብለዋል፡፡ ቅዱስነታቸው አያይዘውም፣ የፍጅት መጨረሻ ፍጅት ሁኖ አያውቅምና አንድ ቀን ለመወያየት የምንቀመጥ ከሆነ፣ ወጣቶችን ማስገበርና በሬሳ ላይ ቆሞ መደራደር አንዳች ጥቅም እንደሌለው ከወዲሁ ልንገነዘብ ያስፈልገናል በማለት አስረግጠው አሳስበዋል፡፡ ዛሬ በትግራይ እየተዘከሩ ስላሉ ወገኖች በእጅጉ ማዘናቸውን፣ ይህ እንዳይመጣም ብዙ ተማጽኖ ሲያቀርቡ እንደነበረ ያስታወሱት ፓትርያርኩ፣ በኀዘን የተጎዳችሁ አባቶችና እናቶችም ይህ ቢሆን ኖሮ እያላችሁ ራሳችሁን እንዳትጎዱ፤ የእናንተ መጎሳቆል የሞቱትን ቀና አያደርግምና ልባችሁን እንድታበረቱ እናሳስባለን፡፡ ምክንያቱም መቃብር መጨረሻችን ያልሆነ የትንሣኤ ሕዝብ ነን ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡