የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር በጦርነቱ ወቅት የተሰው ሰዎች ቤተሰቦችን ለመደገፍ የሚረዳ ክልል አቀፍ የድጋፍ ማዕቀፍ ማዘጋጀቱን አስታወቀ፡፡ የድጋፍ ማዕቀፉ በቅርቡ ተጠናቆ ወደ ትግበራ እንደሚገባም ገልጿል፡፡
የጊዜያዊ አስተዳደሩ የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፊ አቶ ረዳኢ ሃለፎም ለሪፖርተር እንደተናገሩት የድጋፍ ማዕቀፉ ለተጎጂ ቤተሰቦች በየደረጃው መደረግ ስላለበት ድጋፉ ዝርዝር ዕቅዶችን የያዘ ነው ብለዋል፡፡
‹‹ለእያንዳንዱ የሰማዕት ቤተሰብ ምን መደረግ አለበት የሚለውን መመለስ ይቀድማል፤›› ሲሉ የተናገሩት አቶ ረዳኢ፣ ይህን ከመለሱ በኋላ ሀብት የማሰባሰብና ድጋፍ የመስጠት ሥራው እንደሚካሄድ ገልጸዋል፡፡
ትግራይ ክልል ያጋጠመው ውድመት ሰብዓዊም ሆነ ቁሳዊ ጉዳቱ ከባድ መሆኑን የጠቀሱት ኃላፊው፣ ሆኖም ግን ይህን ጉዳት ለመጠገንም ሆነ ለመካስ የሚያስችል በቂ ሀብት በክልሉ እጅ አለመኖሩን ጠቅሰዋል፡፡
የሚዘጋጀው የድጋፍ ማዕቀፍ የአካል ጉዳት የገጠማቸው ወገኖችንም ታሳቢ ያደረገ ስለመሆኑ ገልጸዋል፡፡ ማዕቀፉ የድጋፍ ሒደቱ በአግባቡና በሥርዓቱ የሚካሄድበትን መንገድ የሚያመቻች ስለመሆኑ ነው ያነሱት፡፡ ማዕቀፉ ሲጠቃለል ለድጋፉ የሚያስፈልገው የሀብት ዓይነትና መጠን በትክክል እንደሚታወቅ አክለዋል፡፡
ከዚሁ ጎን ለጎን ሰማዕታት ታስበው የዋሉበት ከጥቅምት ሦስት እስከ ጥቅምት አምስት የዘለቀ ብሔራዊ የሐዘን ቀን በክልሉ መታወጁን ኃላፊው አስታውሰዋል፡፡
ስለዚሁ ጉዳይ ብሔራዊ የሐዘን ቀን በትግራይ ክልል ብቻ ማክበሩ ለምን አስፈለገ ተብለው የተየቁት አቶ ረዳኢ፣ ጥያቄው ተገቢነት እንደሌለው ተከራክረዋል፡፡
በትግራይ አሁንም ቢሆን የጦርነት ተጎጂዎች ብቻ ሳይሆን፣ በድርቅና በረሃብ የሚቀጡ ወገኖች መኖራቸውን ገልጸዋል፡፡ ‹‹የሐዘን ቀን ለምን ታከብራላችሁ ብሎ ከመጠየቅ ይልቅ ወደ ልቦናችን የምንመለስ ከሆነ እነዚህን ተጎጂዎች መደገፍ መቅደም ይኖርበታል፤›› በማለት ገልጸዋል፡፡
የሐዘን ቀን በትግራይ የታወጀው በጦርነቱ ወገኖቻቸውን ላጡ ቤተሰቦች መርዶ ለማርዳት ብቻ ሳይሆን፣ የተጎዱ ዜጎችን መደገፍንም ታሳቢ በማድረግ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ ለዚህ ሲባል ደግሞ በክልሉ የድጋፍ ሒደቱ ወጥ በሆነ ሁኔታ የሚመራበት የድጋፍ ማዕቀፍ እያዘጋጀን ነውና በቅርቡ ተጠናቆ ወደ ሥራ ይገባል በማለት ነው ሐሳባቸውን ያጠቃለሉት፡፡