- ብሔራዊ የሠራተኞች ፍልሰት አስተዳደር የቴክኒክ ቡድን በሰባት አገሮች መቋቋሙ ተገልጿል
የውጭ አገር የሥራ ሥምሪት የሚፈልጉ ዜጎች ባሉበት ቦታ ሆነው አገልግሎት እንዲያገኙ የሚያስችል አሠራር በክልል ደረጃ ሊተገበር መሆኑን፣ የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ሚኒስቴሩ ይህንን የገለጸው ሰኞ መስክረም 28 ቀን 2016 ዓ.ም. የሠራተኞች የሥራ ሥምሪት በቴክኖሎጂ የታገዘ እንዲሆን፣ ብሔራዊ የሠራተኞች ፍልሰት አስተዳደር የቴክኒክ ቡድን መቋቋሙን ባስታወቀበት ወቅት ነው፡፡
የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር የአሠሪና ሠራተኛ ጉዳይ ዘርፍ ሚኒስትር ደኤታ አሰግድ ጌታቸው (ዶ/ር)፣ የውጭ አገር የሥራ ሥምሪት የሚፈልጉ ዜጎች ምንም ዓይነት እንግልት ሳይደርስባቸው አገልግሎት እንዲያገኙ እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡
በሕጋዊ መንገድ ወደ ተለያዩ አገሮች የሄዱ ዜጎች በመዳረሻ አገር የሚገጥሟቸውን ችግሮችና የሰብዓዊ መብት ጥሰት ለመግታት ብሔራዊ የሠራተኞች ፍልሰት አስተዳደር የቴክኒክ ቡድን መቋቋሙን አስረድተዋል፡፡
የቴክኒክ ቡድኑ የአሠሪና ሠራተኛ ፌዴሬሽንን ጨምሮ የተለያዩ ተቋማት መሠረት በማድረግ የተቋቋመ መሆኑን፣ የቴክኒክ ቡድኑ በውጭ አገር የሥራ ሥምሪት ላይ ያሉትን ተግዳሮቶች ለመቅረፍ እንደሚሠራ አስረድተዋል፡፡
ከዚህ በፊት የውጭ አገር ሥምሪት የሚፈልጉ ዜጎች አዲስ አበባ ድረስ መጥተው አገልግሎት ሲያገኙ ከፍተኛ ወጪ በማውጣት፣ ለተለያዩ እንግልቶች ይዳረጉ እንደነበረ አክለው ገልጸዋል፡፡
በዚህም መሠረት የውጭ አገር የሥራ ሥምሪት የሚፈልጉ ዜጎች ባሉበት ቦታ ሆነው አገልግሎቱን በማግኘት ተጠቃሚ እንዲሆኑ፣ በክልል ደረጃ መዋቅር ተዘርግቶ አሠራሩ ተግባራዊ ሊደረግ መሆኑን አብራተዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የውጭ አገር የሥራ ሥምሪታቸውን ጨርሰው ወደ አዲስ አበባ የሚመጡት ሙሉ የጤና ምርመራ ለማድረግ ብቻ መሆኑን ጠቅሰው፣ ሙሉ የጤና ምርመራን በክልል ደረጃ ለማዳረስ ከቀጣሪ አገሮች ጋር ሚኒስቴሩ ንግግር እያደረገ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
የውጭ አገር ሥምሪት በዚህ ደረጃ ተግባራዊ ከሆነ ዜጎች በደላሎች የሚፈጸምባቸው ያልተገባ እንግልትን ማስቀረት እንደሚቻል፣ እስካሁንም ከመቶ ሺሕ በላይ ሰዎች ወደ ተለያዩ አገሮች መላካቸውን ሚኒስቴር ደኤታው ተናግረዋል፡፡
የውጭ አገር የሥራ ሥምሪትን በተቀላጠፈ መንገድ ለማስኬድ ኢትዮጵያን ጨምሮ በሰባት አገሮች ብሔራዊ የሠራተኞች ፍልሰት አስተዳደር የቴክኒክ ቡድን መቋቋሙን፣ የዓለም የሥራ ድርጅት ከፍተኛ የቴክኒክ አማካሪ ወ/ሮ አይዳ አወል ገልጸዋል፡፡
በተለይ በሕገወጥ መንገድ የሚጓዙ ስደተኞችን ለማስቀረትና በዘርፉ ያሉትን ችግሮች ለመፍታት፣ ተቋሙ ከሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ጋር በቅንጅት እየሠራ መሆኑን አስረድተዋል፡፡